መሬት
መሬት በሥርዓተ ፀሐይ ውስጥ ከፀሐይ ባላት ርቀት ሶስተኛ (3ኛ) በግዝፈት ደግሞ ከፕላኔቶች ሁሉ አምስተኛ ግዙፍ የሆነች ፈለክ (ፕላኔት) ናት። በግዝፈት እና በይዘት ቋጥኛዊ ይዘት ካላቸው ወይንም በእንግሊዝኛው ተሬስትሪያል ፕላኔቶች ከሚባሉት የመጀመሪያውን ደረጃ ትይዛለች። በተለምዶ ዓለም ወይም ምድር እየተባለች ትጠራለች። በሳይንሳዊ የተለምዶ ስም ደግሞ «ሰማያዊዋ ፕላኔት» እየተባለች ትጠራለች። ይህች ፕላኔት የሰው ልጅን ጨምሮ ለብዙ ሚሊዮን ዝርያዎች መኖሪያ ናት። ከምድር ብዛት (ከላይ አፈር) አትክልት ሁሉ እየበቀሉ ሲሆን ለሰው ልጅና ለእንስሳ ያስፈለጉት እህል፣ ፍራፍሬ፣ መድኃኒቶችና ሌሎችም ሁሉ ታስገኛለች። ይህም የታወቀች ብቸኛዋ ህይወት ያለው ነገር መኖሪያ ያደርጋታል። ስለዚህ ነው በተለያዩ እምነቶች ዘንድ ምድራዊት እማማችን የተባለች።
«አብርሃማዊ» በተባሉት ሃይማኖቶች (በተለይ ክርስትና፣ እስልምናና አይሁድና) ቅዱሳን መጻሕፍት እንደሚሊት፣ የመሬት እድሜ (ወይም ቢያንስ የተገኙባት ሕያዋን እድሜ) ከ7 ሺህ አመታት በላይ ብዙ አይሆንም። ከተፈጠረች ያስቆጠረችው ዓመት በውል ባይታወቅም ግን በጊዜያችን ባሉት ሳይንሳዊ ዘዴዎች ባኩል የመሬት አማካይ እድሜ ወደ 4.6 ቢሊዮን ዓመታት ገደማ ይጠጋል። ከዚያን ግዜ ወዲህ በ1 ቢሊዮን ዓመት ውስጥ ህይወት ያለው ነገር መኖር ጀመረ።
ማውጫ |
የመሬት ውስጣዊ ክፍል [ለማስተካከል]
መሬት በመዋቅሯ ከእንቁላል ጋር ተመሳሳይ መዋቅር አላት። ውስጣዊ እና ውጫዊ ይዘቷ ባጠቃላይ በሶስት ይከፈላል። ይህም በእንቁላል አካል የውጨኛው ቅርፊት፣ የመካከለኛው ፈሳሽ እና የውስጠኛው አስኳል ብለን እንደምንከፍለው በመሬትም ተመሳሳይ አቀማመጥ ያላቸው ክፍሎች አሉ።
ውጫዊ የመሬት ክፍል [ለማስተካከል]
የመጀመሪያው ውጫዊው የመሬት ክፍል ወይም በእንግሊዝኛው ክረስት የሚባለው ሲሆን የመሬት ቅርፊት ልንለው እንችላለን። በአብዛኛው ከተለያዩ የቋጥኝ አይነቶች የተገነባ ሲሆን ህይወት ያላቸው ነገሮች በሙሉ የሚኖሩት በዚህኛው የመሬት ክፍል ላይ ነው። ይህ ክፍል ውፍረቱን በሁለት ከፍሎ ማየት ይቻላል። ምክንያቱ ደግሞ በውቅያኖሶች ስር ያለው የውፍረቱ መጠን እና በአህጉራት ላይ ያለው መጠን ስለሚለያይ ነው። የመሬት ቅርፊት በውቅያኖሶች ስር ያለው ውፍረት ከአምስት ሺህ ሜትር ( 3 ማይል) እስከ አስር ሽህ ሜትር ( 6 ማይል) ነው። ይህ ውፍረት በአህጉሮች ላይ ከሰላሳ ኪ.ሜ. (20 ማይል) እስከ ሃምሳ ኪ.ሜ. (30 ማይል) ነው።
መካከለኛው የመሬት ክፍል [ለማስተካከል]
ሁለተኛው የመሬት ክፍል መካከለኛው የመሬት ክፍል ወይም በእንግሊዝኛው ማንትል በመባል ይጠራል። ይህ የመሬት ክፍል ፈሳሻማ ይዘት አለው። ውፍረቱ እስከ 2890 ኪ.ሜ. (1800 ማይል) ይደርሳል። የመሬትን 84 በመቶ (84%) መጠን ይሆናል። በአብዛኛው በቅልጥ አለት ወይም ማግማ የተሞላ ነው። ይህም በእንቁላል የመካከለኛው ነጭ ፈሳሽ ይወከላል።
ውስጠኛው የመሬት ክፍል [ለማስተካከል]
የመጨረሻው እና ሶስተኛው ደግሞ ውስጠኛው የመሬት ክፍል ወይም በእንግሊዝኛው ኮር የሚባለው ነው። በእንቁላል የውስጠኛው አስኳል መወከል ይቻላል። እጅግ በጣም ሞቃት ሲሆን የፀሐይን የውጨኛ ክፍል መጠነ ሙቀት ይኖርዋል። ይህ ክፍል መጠኑ አነስተኛ ሲሆን በራዲየስ እስከ 1220 ኪ. ሜ. ብቻ ነው። በዚህም የጨረቃን መጠን 70 በመቶ (70%) ጋር ይነጻጸራል።
የመሬት ታሪክ [ለማስተካከል]
የመሬትን ታሪክ ለማወቅ የተፈጥሮ ሳይንስ የበኩሉን ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል። በዚህም የመሬት እድሜ ከ4.6 ቢሊዮን አመት ወዲህ ያሉትን አመታት በሙሉ የሚያጠቃልል ይሆናል። ይህም የጠቅላላ ሰማያዊ አካላት ወይም ዩኒቨርስን ሲሶ (አንድ ሶስተኛ) እድሜ ይሸፍናል። በዚህ ዘመን ነው እንግዲህ መልከዓ-ምድራዊም ሆነ ፍጥረታዊ ለውጦች የተከናወኑት። በአጠቃላይ የመሬትን ታሪክ ሳይንሳዊ በሆነ ወይም ሃይማኖታዊ በሆነ መልኩ ማየት ይቻላል። ሁለቱም በአሁኑ ጊዜ ተቀባይነት ያላቸው መላምቶች ናቸው።
ሃይማኖታዊ [ለማስተካከል]
የመጀመሪያው እና ከተመሰረተ ከሁለት ሺህ አመታት በላይ ያስቆጠሩት ሃይማኖታዊ እምነቶች አሉ። በነዚህ መሰረት መሬት የተፈጠረችው የአለም ፈጣሪና ጌታ በሆነው በእግዚአብሔር ወይም በአላህ ለሰው ልጆች መኖሪያ ተብሎ ነው የሚል እምነት አለው። ይህ እምነት በአብዛሃኛው የአለም ሃይማኖታዊ ህዝቦች ተቀባይነት ያለው ነው። ይዘቱም በተለያዩ የእምነት አይነቶች የተለያየ ፈጣሪ እንደመኖሩ የሚለያይ ነው። ለዚህ አስተሳሰብ ከሚወክሉት መሃል አንዱ የቅብጥ ተዋሕዶ ቄስ አባ ታድሮስ ማላቲ እንደሚሉት፣ በትምህርተ ሂሳብ ረገድ የመሬቲቱ ስፋት ለአንድ ሚልዮን አመታት የሰው ልጅ ትውልድ መበዛት በቂ ሊሆን ከቶ አይችልም። እያንዳንዱ ቤተሠብ በአማካኝ 3 ልጆች ብቻ ቢወልዱ በሚልዮን አመታት የመሬት ስፋት አንድ ሺህ እጥፍ ቢሆንም እንኳ አይበቃም ይላሉ። ስለዚህ የምድር እድሜ ስፍር ቁጥር የሌለው ረጅም ጊዜ ቢሆንም፣ የስው ልጅ ትውልድ ግን ከ6000 ሺህ አመታት በላይ ብዙ ሊሆን አይችልም ይላሉ።[1]
ሳይንሳዊ [ለማስተካከል]
ይህ ቲዎሪ የተመሰረተው ሳይንስ ካገኛቸው የመሬት ላይ መረጃዎች ጥናት ላይ ነው። በአለማችን ረጅም እድሜ ያስቆጠረው አለት 4.0 ቢሊዮን አመት ነው።
ዘመናት [ለማስተካከል]
የመሬትን ታሪክ በመሬት ጥናት ወይም ጂኦሎጂ በተለያዩ ዘመናት ወይም በእንግሊዝኛው ኢራ ከፋፍሎ ማየት ይቻላል። ይህም ሁሉ የሚታሰበው ከሳይንሳዊ ሊቃውንት ሃልዮ ምርመራ ዘንድ ነው። እነዚህ ዘመናት በቢሊዮን እና ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አመታት እድሜ ያላቸው ሲሆኑ በተለያዩ አነስተኛ ዘመናት ወይም ፔሬድስ ይከፋፈላሉ። ጂኦሎጂ የመሬትን ታሪክ በአራት ዋና ዘመናት ወይም ኢራስ ከፍሎ ያያል። እነዚህም፦
- የመጀመሪያው ዘመን ወይም በእንግሊዝኛው Precambrian Era
- ቅድመ ዘመን ወይም በእንግሊዝኛው Paleozoic Era
- መካከለኛው ዘመን ወይም በእንግሊዝኛው Mesozoic Era እና
- አሁን ያለንበት ዘመን ወይም በእንግሊዝኛው Cenozoic Era ናቸው።
የመጀመሪያው ዘመን ወይም በእንግሊዝኛው Precambrian Era [ለማስተካከል]
ይህ ዘመን ከ4500 ሚሊዮን አመታት በፊት ያለው የመሬት እድሜ ነው። የመሬትን ሰባት ስምንተኛ እድሜ የሚያጠቃልል ነው። ነገር ግን ስለዚህ ዘመን ዘመናዊው ሳይንስ ማወቅ የቻለው ጥቂት ነገር ብቻ ነው። በዚህ ዘመን ህይወት ያለው ነገር ለመፈጠሩ የተገኙ መረጃዎች አነስተኛ ቢሆኑም በምዕራብ አውስትራሊያ 3.46 ቢሊዮን አመታት ያስቆጠረ ህዋስ ወይም ባክቴሪያ ተገኝቷል።
ቅድመ ዘመን ወይም በእንግሊዝኛው Paleozoic Era [ለማስተካከል]
ይህ ዘመን የሚሸፍነው ከ 542 ሚሊዮን እስከ 251 ሚሊዮን አመታት በፊት ያለውን የመሬት እድሜ ነው። የተለያዩ የዓሳ ዝርያዎችን ጨምሮ ትላልቅ የእንሽላሊት ዘሮች ወይም ዳይኖሰሮች በዘመኑ መገባደጃ አካባቢ ተከስተዋል።
መካከለኛው ዘመን ወይም በእንግሊዝኛው Mesozoic Era [ለማስተካከል]
ከ251 ሚሊዮን አመት እስከ 65.5 ሚሊዮን አመት በፊት ያለው ጊዜ በዚህ ዘመን የሚጠቃለል ነው።
አሁን ያለንበት ዘመን ወይም በእንግሊዝኛው Cenozoic Era [ለማስተካከል]
ከ65.5 ሚሊዮን አመታት በፊት ጀምሮ አሁን እስካለንበት ያለውን ጊዜ የሚሸፍነው ይህ ዘመን አብዛሃኛው የመሬት ለውጦች ተከናውነውበታል።
የመሬት ከባቢ አየር [ለማስተካከል]
የመሬት የከባቢ አየር በተለያዩ ግዜያት የተለያዩ ይዘቶች ነበሩት። በውስጡ የሚገኙት ህይወት ላላችው ነገሮች አስፈላጊ የሆኑ ነገርችም ( የኦዞን ንጣፍን ጨምሮ) በየግዜው ተለዋውዋል።ከባቢ አየራችን በውስጡ 78 በመቶ ናይትሮጅን፣ 21 በመቶ ኦክስጅን፣ 0.93 በመቶ አርገን፣ 0.038 በመቶ ካርቦን ክልቶኦክሳይድ የተባሉ ንጥረ ነገሮችን (ጋዞችን) በውስጡ ይዟል። አሁን ያለው ሁኔታ መሬት ለተጨማሪ 1.5 ቢሊዮን አመታት ህይወት ያላቸው ነገሮች እንዲኖሩባት ያስችላል ተብሎ ይታመናል።
ይዩ [ለማስተካከል]
የውጭ ማያያዣዎች [ለማስተካከል]
- USGS Geomagnetism Program|ዩ ኤስ ጂ ኤስ የጂኦማግኔቲዝም ፕሮግራም
- NASA Earth Observatory|በናሳ የመሬት ቅኝት
- Earth Profile በ NASA's Solar System Exploration
- Climate changes cause Earth's shape to change – NASA|የአየር ንብረት ለውጥ የመሬትን ቅርፅ ለውጦታል - ናሳ
- The Gateway to Astronaut Photography of Earth|የመሬት ልዩ ልዩ ጠፈራዊ ምሥሎች