ማኑስ
ማኑስ ወይም ማን በጥንታዊ ጀርመን ነገዶች አፈ ታሪክ የቱዊስኮን ልጅና የጀርመኖች ወላጅ ነበር።
የማኑስ ስም ከሮሜ ጸሐፊው ታኪቱስ ታሪክ ገርማኒያ (90 ዓ.ም. የተጻፈ) ተጠቅሶ ይታወቃል። ታኪቱስ እንደ ገለጸው፣ በጀርመናውያን «ጥንታዊ ዘፈኖች» ውስጥ ይህ ማኑስ ሶስት ልጆች ነበሩት። እነኚህም 3 ልጆች ሦስት ንዑስ-ብሔሮች ወለዱ፦
የስሙ «ማኑስ» ትርጉም በጀርመንኛ «የሰው ልጅ» ነው።
በ1490 ዓ.ም. አኒዩስ ዴ ቪቴርቦ የተባለ ጣልያናዊ መነኮሴ ባሳተመው ጽሑፍ ዘንድ፣ የባቢሎን ታሪክ ጸሓፊ ቤሮሶስ (290 ዓክልበ.) ስለ አውሮፓ ጥንታዊ ነገሥታት ብዙ መዝገቦች አቅርቦ ነበር። በዚህ በኩል፣ የቱዊስኮን ልጅ ማኑስ የሳርማትያ እና የጀርመን አገሮች ሁለተኛው ንጉሥ ነበር። (ግዛቱ ከራይን ወንዝ እስከ ዶን ወንዝ ያለው ሁሉ ያጠቀልል ነበር።) ኢንጋይዎን በዙፋን ላይ ተከተለው ይላል።
በ1513 ዓ.ም. ግድም ጀርመናዊው መምህር ዮሐንስ አቬንቲኑስ የጀርመን ዜና መዋዕል ጻፈ፤ በዚህ ውስጥ ስለ ጀርመን መጀመርያ ነገሥታት ዘመን ብዙ ተጨማሪ ልማዶች አቀረበ። አቬንቲኑስ እንዳለው፣ ማኑስ የነገሠው ለ66 ዓመት (2256-2190 ዓክልበ.) ነበር፤ ሦስት ልጆቹም ትሬቬር፣ ኔሩስና ኢንጋይዎን ነበሩ (ኢስታይዎንን የኢንጋይዎን ልጅ ያደርገዋል)። በ2213 ዓክልበ. ያህል ትሬቬር (ትሬቤታ) የተባለው አለቃ ትሪር፣ ጀርመን ከተማ ከራይን ወንዝ ምዕራብ በሞዘል ወንዝ ላይ መሠረተ። እንዲሁም ትሬቬር ሌሎችን ከተሞች መትዝ፣ ማይንጽ፣ ባዝል፣ ስትራዝቡርግ፣ ስፓየርና ቩርምዝ እንደ መሠረተ ይለናል። የቤልጅግ ብሔር ከዚህ ትሬቬርና ከወንድሙ ኔሩስ እንደ መጡ አቬንቲኑስ ይላል። (ሆኖም ሌሎች መምህሮች የማኑስ ልጅ ሳይሆን የኒኑስ ልጅ ትሬቤታ ከእናቱ ከሴሚራሚስ ወደ ማኑስ ግዛት ሸሽቶ ትሪርን እንደ መሠረተ ብለው ይጠቅሳቸዋል።) በተጨማሪ ማኑስ ማንሃይም፣ ጀርመን በራይን ምሥራቅ እንደ ሠራ ተብሏል። ከአዕምሮው ጽናት የተነሣ በነገዶቹ በኩል እንደ አምላክ መቆጠሩን ይጨምራል።