አንኮበር
| አንኮበር | |
![]() |
|
| የንጉሥ ሣህለ ሥላሴ ግቢ | |
| ከፍታ | ፪ሺ፬፻፷፭ ሜትር (፰ሺ፰፯ ጫማ) |
| ሌላ ስም | ጎሮቤላ |
| አገር | ኢትዮጵያ |
| ክፍለ ሐገር | ሰሜን ሸዋ |
| የሕዝብ ቁጥር | ፪ሺህ ፪፻፹፰ |
አንኮበር በ፲፯፻፴፫ ዓ/ም በሸዋው ነጋሲ በመርዕድ አዝማች አምኀ ኢየሱስ የተመሠረተች የሰሜን ሸዋ ከተማ ስትሆን ከደብረ ብርሃን ምስራቃዊ አቅጣጫ ፵፪ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች፡፡
አንኮበር ከዓጼ ይኵኖ አምላክ ዘመን ጀምሮ ለኢትዮጰያ ነገሥታት በማረፊያነት አገልግላለች፡፡ ዓፄ አምደ ጽዮን የድንኳን ከተማቸውን እንደተከሉባት ይነገራል፡፡ ዓፄ ልብነ ድንግል ደግሞ በተሻለ ሁኔታ የባለወልድን ቤተ ክርስቲያን ለማነጽ ጀምረው እንደነበር የሚጠቁሙ መረጃዎች አሉ፡፡ የከተማነት ታሪኳ የጐላው ግን የሸዋ ስርወ መንግሥት በመንዝ በማንሰራራት /ከ፲፮፻፷፭ ዓ/ም -፲፰፻፹፩ ዓ.ም/ የመስፋፋት እንቅስቃሴ በጀመረበት ወቅት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ወደ እንጦጦ እስከዞረበትና በኋላም አዲስ አበባ እስከተቆረቆረችበት ጊዜ ድረስ በቀዝቃዛ አየሯ የምትታወቀው አንኮበር ለስድስት የሸዋ ነገሥታት በማእከልነት አገልግላለች፡፡
አንኮበር የሸዋ ነገሥታት ቋሚ መናኸሪያ ለመሆን የበቃችው በ፲፱ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሥልጣን በያዙት ንጉስ ሣህለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት ነበር፡፡ ንጉሡ የእጅ ባለሙያዎችን በከፍተኛ ደረጃ ያበረታቱ ስለነበር፣ በርካታ የእደ ጥበብ ሥራዎች ይከናወኑባት ነበር፡፡ በቤተ መንግሥት የሚተዳደሩ ከሺ በላይ አናጺዎችና ግንበኞች በተለይም ባሩድ ቀማሚዎች፣ የጦር መሣሪያ ሠራተኞችና አንጥረኞች በወቅቱ ነበሩባት፡፡
የንጉሥ ሣህለ ሥላሴ ወራሽ ንጉሥ ኃይለ መለኮት ዘውድ በጫኑበት ዘመን አንኮበር በዓፄ ቴዎድሮስ ሠራዊት ከመወረሯ በፊት ሹማምንቱ ቤተ መንግሥቱን አቃጥለውታል፡፡ ዓፄ ቴዎድሮስም በቦታው ድንኳን ጥለው ጥቂት ቀናት ቆይተዋል፡፡ በተካሄደው ጦርነት አንኮበር ክፉኛ መጐዳቷን መረጃዎች ይገልፃሉ፡፡ ዳግማዊ ምኒልክ በዓፄ ቴዎድሮስ እጅ በእስራት ከነበሩበት አምልጠው ሲመለሱ አንኮበር እንደገና ተቋቁማ የጥንት ማዕረጓ ተመልሷል፡፡
ዛሬ በአንኮበር ከዓፄ ምኒሊክ ቤተ መንግሥት ፍርስራሽ በተጨማሪ በተለያዩ ዘመናት የተሠሩ አምስት አብያተ ክርስቲያናትና ዘመናዊ የጎብኚዎች መቀበያ ይገኛሉ፡፡ እነሱም፦
- በ፲፯፻፴፫ ዓ/ም በአምሀ ኢየሱስ የተሠራው አንኮበር ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን
- በ፲፯፻፷፯ ዓ/ም በአስፋ ወሰን የታነጸው አንኮበር ማርያም ቤተ ክርስቲያን
- ንጉሥ ሣህለ ሥላሴ በ፲፰፻፲፯ ዓ/ም ያሠሩትአንኮበር ሚካኤል እና በ፲፰፻፳፩ ዓ/ም ያሠሩት አፈር ባይኔ ተክለ ኃይማኖት
ንጉሥ ምኒልክ እና ወይዘሮ ጣይቱ ብጡል የፋሲካ ዕለት ሚያዝያ ፳፭ ቀን ፲፰፻፸፭ ዓ/ም የጋብቻ ሥነ ስርዓታቸውን ሲፈጽሙ ቅዱስ ቁርባን የተቀበሉበት የአንኮበር መድኀኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን። ይህ ቤተ ክርስቲያን በ፲፯፻፸፪ ዓ/ም ሥራው ቢጀመርም የተፈጸመው በንጉሥ ኃይለ መለኮት በ፲፰፻፵፮ ዓ/ም ነው።
