ርቀት

ከውክፔዲያ

ርቀት በነጥቦች ወይንም በነገሮች መካከል ያለ ክፍተት መጠንን መለኪያ ነው። በለት ትለት ንግግር እንዲሁም በሒሳብ እና በየተፈጥሮ ህግጋት ጥናት ውስጥ ተጠቃሚነት አለው።

ርዝመታዊ ርቀት እና አቀማመጣዊ ርቀት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የርቀት ሐሳብ ሁለት ዓይነት ስሜት አለው። በምሳሌ ለማየት፦

ሰለሞን ጠዋት ከቤቱ ተነስቶ 3 ኪሎ ሜትር ወደ ሥራ ቦታው ቢጓዝ እና ከሰዓት በኋላ ወደ ቤቱ ቢመለስ ፣ የተጓዘው ርቀት ስንት ነው?  

አንዱ መልስ፣ ሦስት ወደ ፊት፣ ሦስት ወደ ኋላ፤ በአጠቃላይ ስድስት ኪሎ ሜትር ነው። ይህ ዓይነት የርቀት ትርጓሜ «ርዝመታዊ ርቀት» ሲባል፣ ለዕለት ተለት ንግግር ጠቃሚ ቢሆንም በሥነ እንቅስቃሴ ጥናት ውስጥ ተጠቃሚነት አያገኝም።

ሌላኛው ትርጓሜ፣ «አቀማመጥዊ ርቀት» ሲባል፣ የሰለሞንን አቀማመጥ በመመርመር መልስ ይሰጣል። ሰለሞን ጠዋት በነበረበት ነጥብ ተመልሶ ስለተገኘ፣ የተጓዘው ርቀት ዜሮ ነው። ማለት አቀማመጡ አልተለወጠም።

አቀማመጣዊ ርቀት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

«አቀማመጣዊ ርቀት» በሁለት ነጥቦች መካከል ያለውን ክፍተት በቀጥታ መስመር ይለካል። ለዚህ ምክንያቱ፣ በሁለት ነጥቦች መካከል ያለው ክፍተት በተፈለገ መንገድ ከተለካ፣ ርቀቱ አስተማማኝ መሆኑ ያቆማል። ለምሳሌ፣ ከአዲስ አበባ እስከ ካርቱም 991 ኪሎ ሜትር ነው ቢባል፣ ይህ እርቀት በኬኒያ ተደርጎ ይለካ፣ ወይንም በግብጽ ወይንም በቀጥታ ለይቶ ለማዎቅ ስለማይቻል ዋጋ የለሽ ይሆናል ማለት ነው።

የቀጥተኛ ርቀት ምሳሌ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የሰሎሞን ቤት በቀኝ በኩል ካለው ሾጣጣ ጫፍ ላይ ይገኛል፣ ኳስ ሜዳው በበኩሉ በላይ በኩል ባለው ጫፍ
 ከጎን ባለው ስዕል ፣   ሰለሞን ከቤቱ (ማለት በቀኝ በኩል ካለው ሾጣጣ ጫፍ) ተነስቶ ወደ ግራ፣ በቀጥታ መስመር 4 ኪሎ ሜትር ቢጓዝ፤ ከዚያ ትንሽ ካረፈ በኋላ ወደ ላይ 3 ኪሎ ሜትር ተጉዞ  ከኳስ ሜዳው ቢደርስ፣ ከቤቱ እስከ ኳስ ሜዳው ያልው ርቀት ስንት ነው?

ይሄ ጥያቄ ሊያምታታ ይችላል፣ በተለይ የርቀት ትርጉም ጥርት ባለ መልኩ ካልተሰጠና እንደተፈለገ ከተተርጎም ብዙ አይነት መልስ ሊገኝ ይችላል። ለምሳሌ 3+4 =7 ኪሎ ሜትር ሊባል ይችላል። ይሁንና፣ በሳይንስ ዘንድ የሚሰራበት ትርጓሜ ፣ ከላይ እንደተገለጸው፣ «አቀማመጣዊ ርቀት» ነው። የሚለካውም ከቤቱ እስከ ኳስ ሜዳው የተዘረጋውን ቀጥተኛ መስመር በመያዝ ነው። ከስዕሉ መቁጠር እንደሚቻል፣ ርቀቱ 5ኪሎ ሜትር ሆኖ ይገኛል።

አለባብሰው ቢያርሱ ባረም ይመለሱ እንዲባል፣ የቃላት ትርጉም ጥርት ብሎ ባልተተርጎመበት ሁኔታ «አስተማማኝ ዕውቀትን» ለመመስረት አይቻልም።፡ ስለሆነም የተፈጥሮ ህግጋጋት ጥናት ፣ የነጥቦችን አቀማመጥ በትክክል ለይቶ ለመረዳት እንዲቻል፣ ርቀትን በቀጥታ መስመር ይተረጉማል። ይሁንና ይህም የራሱ ችግር አለበት ምክንያቱም አበበ ከሰለሞን 5 ሜትር ርቆ ይገኛል ቢባል፣ በአምስት ሜትር ርቀት ከኋላው ይሁን፣ ከግራው ይሁን፣ ከፊቱ፣ ወዘተ.... ስለማይለይ የራሱ ድክመት አለው። ሥለሆነም የአንድን ነጥብ አንጻራዊ አቀማመጥ በትክክል ለመውቀክ፣ ርቀት እና አቅጣጫ ያስፈልጋሉ። ርቀት እና አቅጣጫ ያለው አንድ መጠን ፣ ምዕራፍ ይሰኛል፤ ለሳይንስ ጥናት ከፍተኛ ፋይዳ ያለው ጽንሰ ሐሳብ ነው።

ርቀት እንደ መለኪያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በሁለት ነጥቦች ወይም ቦታዎች መካከል ያለ ቀጥተኛ መንገድ ክፍተት በብዙ መንገድ ሊለካ ይችላል። ለምሳሌ የገጠር ሰዎች እንደሚለኩ፣ የሁለት ስፍራዎች ክፍተት በጊዜ ሊለካ ይችላል። ምንም እንኳ እንደዚህ አይነት አለካክ የብርሃን ፍጥነትን በመጠቀም በከፍተኛ ጥናቶች ቢካሄድም፣ ባብዛኛው ሳይንስ ግን ጥቅም ላይ አይውልም። በምሳሌ ለማየት፣ «ከደሴ እስከ ወልደያ ሁለት ቀን ነው» ሊባል ይችላል። ይሁንና ርቀትን በጊዜ መለካት አስተማማኝ አይሆንም፣ ምክንያቱም አንድ ሰው በእግሩ ሁለት ቀን የሚውስድበትን ርቀት ሌላው በፈረስ በግማሽ ቀን ሊሄደው ይችላል። አንዱ ፈጣን ሌላው ዘገምተኛ ከሆነ፣ አንዱ ርቀት ብዙ ልኬት ሊኖረው ነው ማለት ነው።

በሂደት ሰዎች አስተማማኝ ሆነው ያገኙት መለኪያ ውድር ሲሆን፣ ይሄውም አንድ ቋሚ ነገርን ወስዶ፣ ርቀቶችን ከዚህ ቋሚ ነገር ዝመት ጋር በማዎዳደር በመለካት ነው። ለምሳሌ፣ አንድ ብጣሽ ብረት በስምምነት 1ሜትር ነው ከተባለ በኋላ፣ ማንኛውንም ርቀት ከዚህ ብጣሽ አንጻር በማዎዳደር አስተማማኝ ርቀት ሊለካ ይቻላል ምክንያቱም ውድሩ ምንጊዜም ቋሚ ስለሆነ። ለምሳሌ፣ ከደሴ ውልደያ ያለው ርቀት የዚህ ብጣሽ ብረት 120ሺህ ጊዜ እጥፍ ስለሆነ፣ በከተሞቹ መካከል ያለው ርቀት መቶ ሃያ ሺህ ሜትር ነው ይባላል።

ማጠቃለያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ርቀት በሁለት ነጥቦች ያለን ክፍተት በቀጥታ መስመር ይለካል። አለካኩም ይህን ክፍተት ካንድ ቋሚ ክፍተት ጋር በማዎዳደር ነው።