ቡና

ከውክፔዲያ
ቡና አቅራቢዋ - 1849 ዓ.ም. ተሳለ።

ቡና የተክል አይነትና ከዚህ ተክል ቡን የሚባል መጠጥ የሚወጣው ነው። መጀመርያ የታወቀው በኢትዮጵያ ሲሆን ምናልባት በዚህ የተነሳ ቡና በተለያዩ የዓለም ቋንቋዎች ከፋ ከሚለው ስም ጋር ተቀራራቢ የሆነ ስሞች ተስጥተውት ይገኛል (ለምሳሌ እንግሊዝኛcoffee /ኮፊ/ በፈረንሳይኛ ካፌ (café)በዳች ኮፊ (koffie) በእብራይስጥኛ ካፈ (ka-feh) በስዊድንኛ ካፈ (kaffe) ወዘተ ) ምናልባት ከድሮው የከፋ መንግሥት በተዛመደ መልኩ ሊሆን ይችላል። በአንድ ትውፊት መሠረት በመጀመርያ ያገኘው ሰው ካልዲ የተባለ አንድ ኢትዮጵያዊ እረኛ ፍየሎቹ ፍሬውን በልተው ሲጨፍሩ ስለተመለከተ ነበር።

የቡና የስነ ፍጥረት ስሙ Coffea arabica (ኮፊ ኣራቢካ) ሲሆን የዚህ የኢትዮጵያ ቡና ዘር በጣዕሙ ጥሩነት የተነሳ በጣም ተወዳጅ ነው።

በደራሲው ዊሊያም ኡከርስ መጽሐፍ 'ኦል አባውት ኮፊ' (ስለ ቡና ኅልዮ/ምንነት) እንደተገለጸው ቡና ወደ የመን የገባው በአክሱም ዘመነመንግሥት በ517 ዓ.ም. አካባቢ ነበር። የፋርስ ሃኪም አል-ራዚ (857-917 ዓ.ም. የኖሩ) ተክሉን «ቡንቹም» ብሎ ምናልባት በታሪክ አንደኛው ስለ ቡና መግለጫ የመዘገበው ጸሐፊ ይሆናል። ሌላ እብን-ሲና(972-1029 ዓ.ም.)የተባለ ፋርስ ሀኪም ደግሞ ስለ «ቡንቹም» ጥቅም ጽፏል። የሞሮኮ ደርቡሽ ሼክ አቡል-ሀሳን አሽ-ሻዲሊ (1167-1250 ዓ.ም.) በአሰብ ዙሪያ ሲጓዝ ኗሪዎች ስለ ቡና መጠጥ እንደገለጹለት ይነገራል። የአደን ሙፍቲ ሼክ ጃማል-አል-ዲን አል-ዳባኒ በ1446 ዓ.ም. ገደማ ለመጀመሪያ ጊዜ መጠጡን እንዳስገባ ተመዝግቧል። በ1449 ዓ.ም. መጀመርያው ቡና ቤት «ኪቫ ሃን» በኢስታንቡል ቱርክ ተከፈተ።

ቡና አፈላል ስነ ስርዓት በኢትዮጵያ

ሆኖም በ1503 ዓ.ም. የማካህ ይማሞች ቡና ቤት ስላልወደዱ መጠጡን ሃራም (እርም) አሉት[1]። ነገር ግን የኦቶማን ቱርክ ሡልጣን 1 ሰሊም1509 ዓ.ም. ማካህን በ1516 ዓ.ም. ይህን ድንጋጌ ገልብጦ የተቀደሰ መጠጥ አደረገው። ከዚያ በኋላ እስላሞች ቡናን በተለይ በጣም ወደዱት። ለኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እስከ 1881 ዓ.ም. ድረስ ቡና እንደ ተከለከለ ዛሬ በሰፊ አይታወቅም። ከ1872 እስከ 1878 ድረስ ቡና በመጠጥነት በኢትዮጵያ በጣም ስለ ተስፋፋ አጼ ምኒልክ ከጠጡት በኃላ በ1881 ምኒልክ ንጉሠ ነገሥት ሆነው አቡነ ማቴዎስ 10ኛ ቡናን አጸደቁት።

ቡና ወደ አውሮፓ ለመጀመርያ ጊዜ በ16ኛ ክፍለ ዘመን ያስገቡት ነጋዴዎች ከቬኒዝ ጣልያን ነበሩ። በ1592 ዓ.ም. የሮማ ጳጳስ 8 ቄሌምንጦስ ስላጸደቁት በፍጥነት ዘመናዊ መጠጥ ሊሆን በቃ ። የመጀመርያው ቡና ቤት በአውሮፓ በጣልያን1637 ዓ.ም. ተከፈተ።

አረቦች ግን በጣም አጥብቀው ለምለሙ ተክል ከአረብ ዓለም እንዲወጣ ምንም ባይፈቅዱም፣ በ1600-1650 ዓ.ም. ገደማ አንድ ስሙ ሃጂ ባባ ቡዳን የሚባል ህንዳዊ እስላም ከሞቃ የመን በስውር የቡና ዘር ይዞ ወደ ሚሶር ሕንድ አገር ተመለሰና ተክሉን እዚያ አበቀለው። በ1608 ዓ.ም. የሆላንድ ሰዎች ለ አደን መጥተው ለምለም የቡና ዘር ይዘው ወደ አገራቸው ተመለሱ። በ1690ዎቹ በሆላንድ ቅኝ አገሮች በጃቫ (ዛሬ ኢንዶኔዥያ) እና በሱሪናም (ደቡብ አሜሪካ) በብዛት እንዲስፋፋ አደረጉት።

በአሁኑ ጊዜ ቡና በዓለም ላይ ከሚጠጡ መጠጦች አንደኛን ስፍራ ይዟል። በተጨማሪም የቡና ቅጠል በወተት ተፈልቶ ቁጢ እንዲሁም የቡና ዘር ሽፋኑ/ቅርፊቱ ተፈልቶ የሚጠጣው አሻራ ተወዳጆች ናቸው። ቁጢና አሻራ ከኢትዮጵያ ውጪ እንደሚታውቁ መረጃ የለም።

ተመልከት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ http://www.hoboes.com/Politics/Prohibition/Notes/Coffee/

የኢትዮጵያ የቡና አፈላል ስርአት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  • 1,የቡና እቃ አጥበን እናቀራርባለን፦ረከቦት፣ሲኒ፣ብረት ምጣድ ወ.ዘ.ተ....
  • 2,ከሰል እናቀጣጥላለን
  • 3,ቡናችንን ለቅመን እናጥብና ወደ ብረት ምጣድ አድርገን ምድጃዉ ላይ ይጣዳል
  • 4,በመቀጠል ቡናዉ እንዳያር በመቁያ እናማስላለን
  • 5,ቡናዉ አጋም ሲመስል ከእሳት ላይ እናወርዳለን
  • 6,ከዛም በመቀጠል ቡናውን በሙቀጫ እስኪደቅ ድረስ እንወቅጣለን
  • 7,ዉሀ በጀበና ምድጃዉ ላይ እንጥዳለን
  • 8,ዉሀዉ ሲፈላ ደቀቀዉን ቡና ወደ ጀበናዉ ጨምረን በድጋሚ እንጥዳለን
  • 9,ቡናዉ ሲንተከተክ ጀበናዉን ከእሳት ላይ አዉርደን እስኪሰክን ድረስ 5 ደቄቃ ድረስ እንቆያለን
  • 10,በምድጃዉ ላይ በብረት ጀበና ዉሀ እንጥዳለን
  • 11,ከዛ በእርጋታ ጀበናዉን ይዘን ወደ ሲኒዋቹ ላይ እንቀዳለን
  • 12,ቡናዉ ሲያልቅ በብረት ጀበናዉ ላይ የጣድነውን ዉሀ ወደ ጀበናዉ ገልብጠን እንጥዳለን
  • 13,እንደዛዉ እየተባለ እሰከ 3ተኛ(በረካ)ድረስ ይጠጣል።
   ለጠቅላላ እዉቀት፦1ኛ(አቦል)
               2ተኛ(ሲና/ቶና)
               3ተኛ(በረካ)

የውጭ መያያዣ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]