ተረችነት

ከውክፔዲያ
በህይወታችን ሁልግዜ ነጭ ዳክየዎች ብቻ ቢገጥሙን፣ "ሁሉ ዳክየዎች ነጭ ናቸው" የሚል መላምት ልናቀርብ እንችላለን። በድሮው የሳይንስ ፍልስፍና መሰረት የቀረበው መላምት እውነት እንደሆነ ማረጋገጥ ተገቢ ነበረ። ሆኖም ግን ይሄ የማይቻል ነው ምክንያቱም ከተወሰነ ተመክሮ ተነስትን ወደ አልተወሰነ እውነታ ነውና የዘለልነው። ማለት፣ በአለም ሁሉ እየዞርን ነጭ ዳክዮዎችን ብናይ እንኳ ያላየነው ሌላ ቀለም ዳክየ ሊኖር ይችላልና። ስለሆነም በከንቱ እውነትነቱን ለማረጋገጥ ከመሞክር ይልቅ ውሽት መሆኑን መፈተን ተገቢ ነው ምክንያቱም አንዲት ነጭ ያልሆነች ዳክየ እንኳ ከተገኘች የቀረበው መላምት ውሸት መሆኑ ነውና። ስለሆነም ተረችነት የአንድን ሃሳብ እውነትነት ከማረጋገጥ ይልቅ በሃሳቡ ላይ ጥያቄ ማንሳትን፣ መጻረርንና መርታትን ይደግፋል

ተረችነት በሳይንስና ሳይንሳዊ ዘዴ ውስጥ ቁልፍ ቦታ ያለው ጽንሰ ሐሳብ ነው። አንድ የታመነ እውቀት በተሞክሮ ወይንም በአሰተውሎት ውሸትነቱ ሊደረስበት ከተቻለ ያ እውቀት ተረችነት አለው እንላለን። እዚህ ላይ እምነት የተጣለበት እውቀት የግዴታ ውሸት ሆኖ መገኘት የለበትም። ዋናው ቁም ነገር ውሸት ቢሆን በተመክሮ ተፈትኖ ውሸት መሆኑ ሊደረስበት ይችላል ወይ? ለሚለው ጥያቄ አዎ ውሸት መሆኑ ሊደረስበት ይቻላል የሚል መልስ መገኘቱ ነው።

ለምሳሌ፡

«ሁሉም ሰው ለዘላለም ይኖራል።» የሚለው አረፍተ ነገር ተረችነት አለው። ለዚህ ምክንያቱ አንድ ሰው እንኳ ከሞተ፣ ውሸትነቱ ይረጋገጣልና።
«ሁሉም ሰው ሟች ነው።» የሚለው አረፍተ ነገር ተረችነት የለውም። ለዚህ ምክንያቱ እስካሁን ያጋጠሙን ሰዎች በሙሉ ቢሞቱ እንኳ ለወደፊቱ የማይሞት ሰው ሊያጋጥም ይችላልና።

ተረችነት በመርህ ደረጃ ኖሯቸው በተግባር ግን የሌላቸው አረፍተ ነገሮችም አሉ። ለምሳሌ «የአፍሪቃ ቀንድ በ3ሚሊዮን አመት ውስጥ ከሁለት ይከፈላል። » እርግጥ ነው በተሰጠው ዘመን ውስጥ የአፍሪቃ ቀንድ ከሁለት ላይከፈል ይችል ይሆናል፣ ስለሆነም ሊረታ ይችላል። ግን ያን ዘመን ሁሉ ተጠባብቆ ውሽትነቱን ማረጋገጥ ስለማይቻል በመርህ ደረጃ ተረችነት ኖሮት በተግባር የለውም ይባላል።

አንድ አንድ አረፈተ ነገሮች መረታት የማይችሉ ሆነው ሳለ ግን ከተረቺ አረፍተ ነገሮች የሚመዘዙ ስለሆኑ በሳይንስ ዘንድ ተጠቃሚነትን ያገኛሉ። ለምሳሌ "ሁሉም ሰው ሟች ነው" የሚለው በራሱ ተረችነት የለውም፤ ነገር ግን "ሁሉም ሰው ዕድሜው 150 ከመሙላቱ በፊት ይሞታል" የሚለው መላምት ተረችነት አለው። ስለሆነም የመጀመሪያው አረፍተ ነገር ከሁለተኛው አረፍተነገር ስለሚመነጭ ምንም እንኳ ተረችነት በራሱ ባይኖረውም እንደ ሳይንሳዊ እውቀት ሊወሰድ ይችላል።

ባጠቃላይ መልኩ ተረችነት ለሳይንስ ጥናት እጅግ አስፈላጊ ጽንሰ ሐሳብ ነው። አንድ አረፍተ ነገር/ጽሑፍ ሳይንሳዊ መሆኑና አለመሆኑ ብዙን ጊዜ በተረችነቱ ይወሰናል። በሌላ አነጋገር አንድ ጽሑፍ ሳይንሳዊ ነው እሚባለው ተረችነት ሲኖረው ወይንም ተርችነት ከአላቸው ጽንሰ ሐሳቦች በምክንየት ሲመዘዝ ነው።

እንደ ፈላስፋው ካርል ፖፐር፣ ተረችነት ያላቸው ዕውቀቶች፣ ሳይንሳዊ ዕውቀቶች ሊባሉ ይችላሉ። ነገር ግን የዚህ ዓ/ነገር ዙር የግዴታ እውነት አይደለም። ማለት ሳይንሳዊ እውቀቶች የግዴታ ተረችነት ሊኖራቸው አይገባም።

ትችት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አንድ አንድ ዘመናዊ ፈላስፎች ተረችነት ለሳይንሳዊ እውቀት መሰረት መሆኑን ይክዳሉ። በተለይ ተረችነትን የሚነቅፉበት ዋና ምክንያት ተረችነት ምንም ዕውቀትን ከማረጋገጥ ይልቅ በመንቀፍ ላይ የተመሰረተ ነው የሚል ነው። እኒህ ፈላስፎች ዘመናዊ የሳይንስ እውቀት በዕድል ጥናት ላይ መሰረቱ እንዲጣል አስተዋፅኦ አድርገዋል።