ትምህርተ፡ጤና

ከውክፔዲያ

የህብረተሰብ ጤና [ለማስተካከል | ኮድ አርም]

[[]] የአለም ጤና ጥበቃ ድርጅት ጤንነትን እንደሚከተለው ይተነትነዋል፡፡ ጤንነት ማለት ሙሉ የሆነ የአካል፡ የስነልቦናዊ፡ እንዲሁም የማህበረሰብአዊ ደህንነት ነው፡፡ ይህም ሲባል የበሽታ አለመኖር ብቻ ጤነኝነትን አይገልፅም፡፡ http://www.who.int/about/definition/en/

ስለዚህም በሽታ ማለት የማንኛውንም ግለሰብ የአካል፡ የስነልቦናዊ፡ ወይም የማህበረሰብአዊ ደህንነትን የሚያቃውስ ሁኔታ ነው፡፡ === የበሽታዎች የወባና ===

በሽታ በተለያየ ጠንቅ መንገድ ሊነሳ ይችላል፡፡

  • 1. በተፈጥሮ የሚከሰት አካላዊ/ ይዘታዊ ጉድለት ወይም መዛባት
  • 2. በዘር የሚወረስ ለተወሰኑ በሽታዎች ተጠቂነት (ለምሳሌ፡ የደም አለመርጋት ችግሮች)
  • 3. ከወሊድ ችግሮች ጋር በተያያዘ (ለምሳሌ፡ የነርቭ ጉዳት)
  • 4. በጥቃቅን ህዋሳት ምክንያት
    • a. ቫይረሶች፡ (ለምሳሌ፡ ኩፍኝ፤ ጉድፍ፤ ጆሮ ደግፍ፤ ጉንፋን፤ የህፃናት ተቅማጥ፤ ኤድስ
    • b. ባክቴሪያዎች (ለምሳሌ፡ የሳምባ ምች፤ ተስቦ፤ የደም ተቅማጥ፤ የሳምባ ነቀርሳ፤ ቁምጥና፤ ቂጥኝ
    • c. ጥገኞች፤ ፓራሳይቶች (ለምሳሌ፡ ግርሻ፤ ወባ፤ ሻህኝ፤ እንዲሁም ዝሆኔ፤ የውሻ ኮሶ፤ ወስፋት እና ሌሎች ጥገኛ የአንጀት ትላትሎች)
    • d. ፈንገሶች (ለምሳሌ ጭርት እና መሰል የቆዳ በሽታዎች)
  • 5. በምግብ ወይም አስፈላጊ የምግብ ንጥረ ነገሮች ጉድለት (ለምሳሌ፡ የደም ማነስ፤ ክዋሾርኮር)
  • 6. በአካል ላይ በሚደርስ ቀጥተኛ አደጋ፡ (ለምሳሌ፡ ቃጠሎ፡ የመኪና አደጋ፡ ድብደባ)
  • 7. በኬሚካሎች መመረዝ
  • 8. የሆርሞኖች ምርት መዛባት (ለምሳሌ፡ እንቅርት፤ የስኳር በሸታ)
  • 9. ከቁጥጥር ውጪ የሆነ የሴሎች መባዛት (ቲዩሞር ወይም ካንሰር)
  • 10. የማይታወቅ መንስኤ

ተላላፊ በሽታዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አፍሪካ እና በሌሎችም ታዳጊ ሀገሮች ውስጥ አብዛኛውን ህብረተሰብ የሚያጠቁት በሽታዎች በጥቃቅን ህዋሳት አማካኝነት የሚተላለፉ እና በምግብ እጥረት ምክንያት የሚመጡት ናቸው፡፡ የአለም ጤና ጥበቃ ድርጅት የ2004 ዓ.ም. መረጃ እንደሚያሳየው በተለይም ወባ፡ የሳምባ ነቀርሳ፡ ኤድስ እንዲሁም የህጻናት ጠቅማጥ እና የሳማባ ምች ለብዙ የምርት እና የትምህርት ሰዐታት መባከን ምክንያት ናቸው፤ እንዲሁም በየአመቱ ብዙ ህይወት ይቀጥፋሉ፡፡

በህዋሳት ምክንያት የሚመጡት በሽታዎች እንደ ህዋሳቱ እይነት የተለያየ የመተላለፊያ መንገድ ያላቸው ሲሆን ባጠቃላይ ግን እኒህ መተላለፊያ መንገዶች እንደሚከተለው ይመደባሉ፡

  • 1. በምግብ የሚተላለፉ፡- (ለምሳሌ ኮሶ፤ የምግብ መመረዝ፤ ተስቦ፤ የህፃናት ተቅማጥ)
  • 2. ውሃ ወለድ፡ (ለምሳሌ ኮሌራ፡ ተስቦ፤ )
  • 3. ከሰገራ ጋር በሚኖር ንክኪ (ማለትም በእጅ፡ በዝንቦች ወይም ከመጠጥና ምግብ ጋር በሚኖር ንክኪ) የሚተላለፉ (ለምሳሌ ወስፋት፤ አሜባ፤ የህፃናት ተቅማጥ)
  • 4. በነፍሳት (የተለያዩ ትንኞች/ መዥገር/ ቅማል) የሚተላለፉ (ለምሳሌ ወባ፡ ቢጫ ወባ፤ ሻህኝ፤ ግርሻ)
  • 5. በቀጥተኛ ንክኪ የሚተላለፉ (ለምሳሌ፡ የቁስል ማመርቀዝ፡ የአይን ማዝ፤ የተለያዩ የቆዳ በሽታዎች፤ የእብድ ውሻ በሽታ)
  • 6. በወሲብ የሚተላለፉ (ለምሳሌ ኤይች አይቪ/ኤድስ፤ የተለያዩ የአባላዘር በሽታዎች፤ ቂጥኝ)
  • 7. ከደምና ከሌሎች የሰውነት ፈሳሾች ጋር በሚደረግ ንክኪ የሚተላለፉ (ለምሳሌ ኤይች አይቪ/ኤድስ፤ የተለያየ አይነት የጉበት ልክፍት)
  • 8. በትንፋሽ/ በአየር የሚተላለፉ (ለምሳሌ ማጅራት ገትር፤ ኩፍኝ፤ ጉድፍ፤ ጉንፋን፤ የሳምባ ነቀርሳ)

ከበሽተኛው አገላለፅ እና የአካል ምርመራ በተጨማሪ አንድን በሽታ በተላላፊ ህዋሳት ነው የሚመጣው ለማለት የሚያበቁ መረጃዎች ያስፈልጋሉ፤ እነዚህም መረጃዎች የተላላፊው ህዋስ ወይንም ሰውነታችን ህዋሱን በተለይ ለመከላከል የሚያመነጨው የተለየ ፀረ-ህዋስ ኬሚካል በበሽተኛው ሰውነት ውስጥ መገኘትን ያጠቃልላል፡፡ በዚህም ምክንያት በሽታውን ለመለየት የሚደረጉ ምርመራዎች ደም ወይንም ሌላ ከሰውነት የመነጨ ፈሳሽ (ሽንት፤ አክታ፤ ሰገራ፤ መግል፤ የሳምባ ልባስ ፈሳሽ፤ ወዘተ) ሊያካትቱ ይችላል፡፡

በተለያዩ በሽታዎች ምክንያት የሚመጡ የተለየ ምልክት የሚሰጡ ጉልህ የሆኑ የአካላት ላይ የቅርፅ ለውጦችን በማየትም በሽታው ምን እንደሆነ ለመለየት የሚቻል ሲሆን፤ እነኚህን ለውጦች ለማየት በመሳሪያ የታገዘ ቀጥተኛ የሆነ የውስጥ አካል እይታ (ኤንዶስኮፒ)፤ በድምፅ-መሰል ሞገዶች የታገዘ የአልትራሳውንድ ምርመራ፤ ወይንም ኤክስ ሬይ (ራጅ) እና ሌሎች ጠልቆ ለማየት የሚያስችሉ ምርመራዎች ይታዘዛሉ፡፡

በበሽታዎች የሚመጡ በአይን ለማየት የሚያዳግቱ የተለዩ የቅርፅ ለውጦችን ለማየት አንዳንድ ጊዜ የተጠቃውን አካል ክፍል በትንሹ ቆንጥሮ በመውሰድ የሚደረግ የረቂቅ ማይክሮስኮፕ ምርመራ ውጤት ፍንጭ ሊሰጥ ይችላል፡፡

የተላላፊ በሽታዎችን መከላከል[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል መሰረታዊ የሆኑ መርሆዎች አሉ። እነኚህም፡

  • 1. ከአስተማማኝ ምንጭ ያልተገኘን የመጠጥ ውኃ ሁልጊዜ ካፈሉ በኋላ አቀዝቅዞ መጠጣት
  • 2. በጥሬነታቸው የሚበሉ ምግቦችን በሚገባ አጥቦ መመገብ
  • 3. ሌሎች ምግቦችን በደንብ አብስሎ መመገብ። ያልተመርመረ ጥሬ ስጋ ኣለመብላት
  • 4. አንዴ የበሰለን ምግብ ህዋሳት እንዳይራቡበት አቀዝቅዞ ማስቀመጥና ለመብላት ሲያስፈልግ በሚገባ ማሞቅ
  • 5. የተመጣጠነ የምግብ አወሳሰድ
  • 6. ሕፃናትን በተቻለ መጠን ቢያንስ 6 ወራት ለብቻው ከዚያ በኋላ ደግሞ ከተጨማሪ ምግብ ጋር እስከ አንድ አመት ድረስ የእናት ጡት ወተት ማጥባት
  • 7. ማንኛውንም አይነት ፍሳሽ (የህፃናት ሰገራን ጨምሮ) በአግባቡ ማስወገድ
  • 8. ከመፀዳዳት በኋላ ሁልጊዜ እጅን በደንብ በሳሙና መታጠብ
  • 9. የግል ንፅህናን መጠበቅ፤ ገላን፤ ጸጉርን እንዲሁም ጥርስን በየጊዜው መታጠብ
  • 10. ቢያንስ ጠዋት ጠዋት ፊትን መታጠብ
  • 11. በትዳር አንድ ለአንድ መወሰን
  • 12. ይህ ባይሆን በወሲብ ጊዜ በጭንብል (ኮንዶም) መጠቀም
  • 13. ደረቅ ቆሻሻን ማቃጠል ወይንም መቅበር
  • 14. ዝንቦችን ማስወገድ
  • 15. በተቻለ መጠን የትንኞች መራቢያ የሆነ የውሃ ጥርቅምን ማጥፋት/ ማጽዳት
  • 16. በትንኞች ላለመነከስ በተለይ ማታ በመከላከያ አጎበር (ዛንዚራ) ተከልሎ መተኛት
  • 17. መኖሪያ ቤት እና ሌሎች ክፍሎች በቂ የንጹህ አየር ዝውውር እንዲኖራቸው ማድረግ
  • 18. በሽታ ሳይጀምር የመከላከያ ክትባት በወቅቱ መውሰድ

ክትባት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በአሁኑ ወቅት በክትባት አማካይነት ልንከላከላቸው የምንችላቸው በሽታዎች ጥቂት ብቻ አይደሉም። ከእነዚህም መካከል፡

  • 1. የሳምባ ነቀርሳ
  • 2. ኩፍኝ
  • 3. የልጅነት ልምሻ (ፖሊዮ)
  • 4. ትክትክ
  • 5. ዘጊ አነዳ
  • 6. መንጋጋ ቆልፍ

ከእነዚህ በተጨማሪ በለሙ ሀገሮች ሌሎች በሽታዎችን መከላከል የሚያስችሉ ክትባቶቸ አሉ። እነዚህኞቹ በተለያየ ምክንያት (ዋጋቸው ከፍተኛ መሆኑን ጨምሮ) በታዳጊ ሀገሮች በብዛት ጥቅም ላይ አልዋሉም። ከእነዚህ መሀል የመንጋጋ ቆልፍ፤ የጆሮ ደግፍ፤ የቢጫ ወባ፤ የተስቦ፤ የጉበት ልክፍት በሽታ መከላከያ ክትባቶች ይገኙበታል።

የክትባት ንጥረ ነገር የሚሰራው ከራሱ በሽታ አምጭ ከሆኑት ህዋሳት ሲሆን እነዚህን ህዋሳት በኬሚካል እና በሌላም ዘዴ በማዳከም በሽታ እንዳያሰከትሉ ግን በክትባት መልክ ቢሰጡ ሰውነታችን ለይቷቸው የበሽታ መከላከያ እንዲያዘጋጅ በማድረግ ነው። አብዛኛዎቹ ክትባቶች የሚሰጡት በመርፌ መልክ ሲሆን በአሁኑ ወቅት በብዛት በስራ ላይ የዋለው የፖሊዮ ክትባት ግን በአፍ በሚሰጥ ጠብታ መልክ የተዘጋጀ ነው።

የውጭ መያያዣዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]