ቶማስ ሆብስ

ከውክፔዲያ
ቶማስ ሆብስ

ቶማስ ሆብስ ከሚያዚያ5፣ 1588 - ታህሳስ 4 1679 ዓ.ም (እ.ኤ.አ) የነበረ የእንግሊዝ ፈላስፋ ነበር። ከጻፋቸው መጻህፍቶቹ ሌቪያታን (1651) ከሁሉ ይታወቃል።

የሆብስ ዋና ትኩረት መንግስት እና ህግ ነበር፣ ስለሆነ የፖለቲካ ፈላስፋ ይሰኛል። ፍጽምና ያለው አንድ መሪ አገርን ማስተዳደሩ ከሁሉ አይነት የመንግስት አወቃቀር የተሻለ እንደሆነ በጽሁፎቹ ለማሳየት ሞክሯል። በአሁኑ ዘመን ሆብስ የሚታወቀው ስለዚህ አስተሳሰቡ ሳይሆን ይህን አስተሳሰቡን ሊደርስበት የወሰደው መንገድ ነበር።

የሆብስ መነሻ ሃሳብ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ያለው ጽንስ ነበር። የሰው ልጅ በተፈጥሮው ራስ ወዳድና ጥቅም እስካስከኘለት ድረስ ሌሎችን ከመጉዳት ወደኋላ የማይል እንደሆነ የሆብስ እምነት ነበር። በተጨማሪ፣ የሰው ልጅ ሁሉ እኩል ነው ምክንያቱም ሁሉም ሌላውን ለመግደል እኩል አቅም አለውና፣ ህጻናት ሳይቀሩ የተኛን ጠንካራ ሰው መግደል ይችላሉና። ከዚህ በመነሳት ሰወች ያለ መንግስት ምን አይነት ኑሮ እንደሚመሩ በአይነ ህሊናው ለመዳሰስ ሞክሯል። ያለ መንግስት፣ ሰወች የጦርነት ሁናቴ ባለው ሁሉ በሁሉ ጦርነት አለም ውስጥ ሊኖሩ እንደሚገደዱ ጽፏል። በአለም ላይ ያለው ምጣኔ ሃብት ውሱን ስለሆነ፣ ለኔ ይገባኛል በሚል ፉክክር አንድ አንዶች እርስ በርስ ሲዋጉ የተቀረው ህዝብ ደግሞ ለደህንነቱ በመጨነቅ የሽብር ኑሮ ይፈጠራል። ማንም ማንንም ማመን ያቅተውና ሁሉም ለወደፊቱ እቅድ ማውጣት ያቆማል። ሕይወት «ብቸኛ፣ ችጋር የተመላበት፣ መጥፎ፣ ጭካኔ የተመላበትና አጭር» ይሆናል ሲል ጽፏል።

ስለሆነም ሰዎች መዋጋታቸውን አቁመው መሪ (ልዑል) መምረጥ እንደሚገባቸው አስፍሯል። ሁሉም ሰው ይህን መሪ እንዲታዘዝና ያላቸውን ማንኛውንም ኃይል ለርሱ እንዲያሰርክቡ ይመክራል። መሪው እንግዲህ የሁሉንም ደህንነት በሚጠብቅ መልኩ ህግ እንዲያወጣና መሪውን የሚቃወሙ ሁሉ ለመሪው እንዲታዘዙ ይመክራል። ለዚህ ምክንያቱን ሲያስረዳ ሁሉም መሪውን ሊታዘዙ መጀመሪያውን ቃል ገብተዋልና። ይህ አይነት ሃይልን ሁሉ ለአንድ ሰው ማስረከብ አደገኛ ቢሆንም፣ በሆብስ ግምት በፍጽም መሪ ስር ደህንነትን ማግኘት ከሁሉ በሁሉ ጦርነት የተሻለ ነው የሚል ነበር፡

የሆብስ መጽሃፍ ልክ እንደሒሳብ መፅህፍት በጥንቃቄ የተመከነየ ይሁን እንጂ ብዙወች በርሱ መሰረታዊ ሃሳቦች ላይ አይስማሙም፡፡ አንድ አንዶች "ሁሉም ሰው እኩል ነው" የሚለው ሃሳብ ለአመጽ ይገፋፋል የሚል ተቃውሞ ሲያቀርቡ፣ ሌሎች ደግሞ የሰው ልጅ ሆብስ ባስቀመጠው ደረጃ ራስ ወዳድ አይደለም የሚሉ አሉ። በአሁኑ ዘመን፣ የፍጽምና መንግስት አስተሳሰቡ በብዙወች ዘንድ የተጠላ ነው። የሆኖ ሆኖ የሆብስ ምክንየት በጣም ጠቃሚ ከመሆኑ የተነሳ ስለመንግስት የሚያጠኑ ፈላስፋወች የሆብስን መጻህፍት እስካሁን ድረስ በጥንቃቄ ይመረምራሉ።