ደስታ ተክለወልድ

ከውክፔዲያ

አለቃ ደስታ ተክለወልድኢትዮጵያ ዕውቅ የቤተ ክርስቲያን ሊቅ፣ የመዝገበ ቃላት አዘጋጅና ደራሲ ነበሩ።

ሐምሌ 19 ቀን 1893 ዓ.ም. በሸዋ ጠቅላይ ግዛት በተጉለትና ቡልጋ አውራጃ ላይ ወግዳ ጎሽ ውኃ ቀበሌ የተወለዱት አለቃ ደስታ፣ ያረፉት ጳጉሜን 2 ቀን 1977 ዓ.ም. ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ትምህርትን ከአጥቢያቸው ዠምሮ እስከ ደብረ ሊባኖስ የቅኔና የዜማ ትምህርታቸውን አጠናቀዋል፡፡

ቀለምን ፈጥኖ በመቀበልና በማስተዋል ችሎታቸው የተመሰከረላቸው አለቃ ደስታ የመጻሕፍት አንድምታ ትርጓሜን አደላድለዋል፡፡ በብርሃንና ሰላም ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ማተሚያ ቤት ቅዱሳት መጻሕፍትን በማረምና በማስተካከል ከ1916 እስከ 1920 ዓ.ም. ድረስ የሠሩ ሲሆን፣ በእርሳቸው አረጋጋጭነት በርካታ መጸሕፍት ለሕትመት በቅተዋል፡፡

በሀገረ ጀርመን በታተመው ኢንሳይክሎፔዲያ ኢትዮፒካ እንደተዘገበው፣ ወደ ድሬዳዋ በመሄድ በአልዓዛር ማተሚያ ቤት ሥራቸውን የቀጠሉበት አጋጣሚ የተፈጠረው ከሊቁ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መተዋወቃቸው ነበር፡፡ ከ30 ዓመት በፊት በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ምን እየሠሩ ዐምድ አጋጣሚውን እንዲህ ያስታውሰዋል፡፡

‹‹አለቃ ኪዳነ ወልድ ብርሃንና ሰላምን ሲጎበኙ ደስታ ተክለ ወልድ የግእዙን መጽሐፍ ከፍ ባለ ድምፅ ሲያነብቡና ሲያናብቡ ሰምተው ‘ከኔ ጋር ሥራ’ ብለው ጠይቀዋቸው ነው ይባላል፡፡ ከዚህም የተነሣ በድሬዳዋ አልአዛር ማተሚያ ቤት 16 ዓመት ያህል ሠርተዋል፡፡ እንደገና ከድሬዳዋ ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በብርሃንና ሰላምና በአርቲስቲክ ማተሚያ ቤቶች አገልግለዋል፡፡

‹‹አስተማሪዬ መምህር ክፍለ ጊዮርጊስ የጀመሩትን ግእዝ ዐማርኛ ግስ እንድጨርስ አዘውኝ ነበር፡፡ እነሆ እስከ ዛሬ ደክሜበታለሁ፤ አልተጠናቀቀልኝምና አንተ ተረክበኸኝ ሥራውን ቀጥል፡፡ ዘርሁን፤ ዘር ይውጣልህ›› ብለው አለቃ ኪዳነ ወልድ ለአለቃ ደስታ አደራ ሰጥተው ነበር፡፡ አለቃም አደራውን ጠብቀው በ1948 ዓ.ም. ከመደበኛ ሥራቸው ውጭ ሌት ከቀን በመሥራት ‹‹መጽሐፍ ሰዋሰው ወግስ፤ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ›› የተባለውን የመጀመሪያ ታላቅ መዝገበ ቃላት አሳትመዋል፡፡

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የነበሩት የታሪክ ምሁሩ ነፍስ ኄር ዶ/ር ብርሃኑ አበበ ስለ አለቃ ክፍሌና ስለ አለቃ ኪዳነ ወልድ ለ‹‹ምን እየሠሩ ነው?›› አዘጋጅ ሲገልጹ እንዲህ ብለዋል፤ ‹‹አለቃ ክፍሌ በወቅቱ የአገሪቱ የቀለም ሰዎች ከተባሉት አንዱ ነበሩ፡፡ ዘመኑም የአፄ ዮሐንስ ነበር፡፡ የሃይማኖት ክርክሩ ቦሩ ሜዳ ላይ ተነሥቶ አለቃ ክፍሌ በኋላቀር ካህናት ከሃዲ መስለው በመታየታቸውና በዐፄ ዮሐንስ ዘንድ እጅግ ፊት በማጣታቸው የሸዋ ንጉሥ የነበሩት ምኒልክ አገር ጥለው እንዲሰደዱ ይመክሩዋቸዋል፡፡ ከዚያም በምድረ ሱዳን አድርገው ግብፅ ቀጥለውም ወደ ኢጣልያ ይሻገራሉ፡፡ እነ አግናጥዮስ ጒይዲንና ሌሎችንም ግእዝ ካማርኛ ያስተምራሉ፡፡ ቀጥሎም እርጅና ሲመጣባቸው ወደ ኢየሩሳሌም ጉዞ ያደርጋሉ፡፡ ከዚያም አለቃ ኪዳነ ወልድን ያገኛሉ፡፡ ያላቸውን ዕውቀት ከውድ መጻሕፍታቸው ጋር ለኪዳነ ወልድ ያስረክባሉ፡፡ በተለይም የግእዝና የአማርኛ መዝገበ ቃላት በውል ተሰናድቶ እንዲታተም ለኪዳነ ወልድ አደራ ይሰጣሉ፡፡ በአገሪቱ ዘመናዊ ማተሚያ ሲቋቋም አለቃ ኪዳነ ወልድ ለመጻሕፍት ትርጓሜ ሥራ ወደ አገራቸው ይጠራሉ፡፡ እሳቸው ከአለቃ ክፍሌ የተቀበሉትን አደራ ለአለቃ ደስታ ተክለ ወልድ ያስረክባሉ፡፡ የዚህ ዐቢይ መዝገበ ቃላት ሥራ መነሻው ይህ ነው፤›› በማለት ስለሦስቱም ሊቃውንት ያላቸው ግምት ከፍተኛ መሆኑን አንፀባርቀዋል፡፡ ዶ/ር ብርሃኑ የሦስቱንም የቀለም ሰዎች ታሪክ በፈረንሣይኛ ቋንቋ አዘጋጅተው ‹‹ሃይማኖተ አበው ቀደምት ወዘደኃርት›› ከተባለው የአለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መጽሐፍ ጋር አዳብለው በ1978 ዓ.ም. በጀርመን ማሳተማቸው ይታወቃል፡፡

አለቃ ደስታ ለኢትዮጵያ ባህል፣ ቋንቋና ታሪክ ካበረከቷቸው ሥነ ጽሑፋዊ ትሩፋቶች መካከል የግእዝ መማርያ ‹‹ርባሐ ስም ወአንቀጽ›› (1946 ዓ.ም.) እና ‹‹ገበታ ሐዋርያት›› (1928 ዓ.ም.) ይገኙበታል፡፡

‹‹አንባቢ ሆይ ያማርኛ ቋንቋ ይህ ብቻ እንዳይመስልህ ከዚህ የቀረውን የእንስሳትንና የአራዊትን የአዕዋፍን፣ የዓሣትን፣ የዕፅዋትን፣ ያገርንና የሰውን ስም አምልተን፣ አስፍተን፣ ከነትርጓሜው ለማሳየት ሐሳብ አለን፤ ለዚሁም ያምላካችን ፈቃዱ ይኹን፤›› ብለው በመዝገበ ቃላቱ ላይ ጽፈው ነበር፡፡ ያልታተሙትን ሥራዎቻቸውን ኹለተኛውን እትም ያሳተሙት ልጆቻቸውና ወራሾቻቸው ለንባብ እንደሚያበቁት ይጠበቃል፡፡

የውጭ ማያያዣዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]