ገለዓድ

ከውክፔዲያ
የገለዓድ ተራሮች

ገለዓድ (ዕብራይስጥ፦ גִּלְעָד /ጊልዓድ/) በብሉይ ኪዳን መሠረት ከዮርዳኖስ ወንዝ ምሥራቅ፣ አሁን በዮርዳኖስ አገር የሆነ ተራራማ አገር ነበር።

ገለዓድ መጀመርያ በኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ 31 ይጠቀሳል። ያዕቆብላባንፓዳን-አራም (የካራን ዙሪያ ወይም «ሁለት ወንዞች ምካከል») በሸሸ ጊዜ ወደ ገለዓድ ተራራ መጣ። በቅርቡ ላባንም እዚያ አገኘውና አብረው አንድ ሐውልትና የጠረፋቸውን ምስክር ድንጋይ ክምችት ሠርተው ስምምነት ተዋዋሉ። ቦታው በዕብራይስጥ ጊልዓድ «የምስክር ክምችት» ሲባል፣ በአራማይስጥይጋርሠሀዱታ «የምስክር ክምችት» ተባለ።

በኋላ ዘመን ሙሴ ዕብራውያንን ከሲና ልሳነ ምድር ሲመራቸው በዚያ አገር አሞራውያን፣ ነጉሥ ሴዎንና የባሳን ንጉሥ ዐግ፣ ይገዙበት ነበር። ዕብራውያን እንዲያልፉ ስላልፈቀዱ በሙሴ መሪነት አሸነፏቸውና አገሩን ያዙ። ከዚህ ተነሥተው በኢያሱ ወልደ ነዌ መሪነት ዮርዳኖስን ተሻግረው ከነዓንን ወረሩ።

ከዚያ በኋላ በእስራኤል ዘመነ መሳፍንት እስራኤላውያን አንዳንድ ጊዜ ወደ ጣኦታት ዞረው በባዕድ ገዦች ሲወድቁ መሬታቸውን ሁሉ አጡ። ከ1226-1204 ዓክልበ. ገደማ የፈረደባቸው ኢያዕርና ልጆቹ በገለዓድ 30 ከተሞች እንደ ገዙ በመጽሐፈ መሳፍንት 10 ይዘገባል። (በ፩ መጽሐፈ ዜና መዋዕል 2:22 ደግሞ ኢያዕር 23 ከተሞች በገለዓድ እንደ ገዛ ይጠቅሳል።) ከርሱ በኋላ ግን የአሞን ሕዝብ አገራቸውን ከ1204-1186 ዓክልበ. ያህል ያዙት። ዮፍታሔ ግን ከገለዓድ ተነሥቶ አሞናውያንን አሸነፋቸው። (የዮፍታሐም አባት ደግሞ ገለዓድ ተባለ።) እሱም የእስራኤልም ፈራጅ 1186-1180 ሆነ፤ በዘመኑም ከገለዓድና ከኤፍሬም ወገኖች መካከል እርስ በርስ ጦርነት እንደ ሆነ በመሳፍንት 12 ይዘገባል።

በ870 ዓክልበ. ግድም ነቢዩ ኤልያስ ከገለዓድ እንደ ተነሣ በመጽሐፈ ነገሥታት ፩ 17:1 ይጻፋል። በ740 ዓክልበ. የአሦር ንጉሥ 3 ቴልጌልቴልፌልሶር ይዞት የአሦር «ጋልዓዙ ክፍላገር» ሆነ።