ፍሬምናጦስ

ከውክፔዲያ
ቅዱስ ፍሬምናጦስ
የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ጳጳስ
አቡነ ሰላማ ክሳቴ ብርሃን
ስም መጀመሪያ ፍሬምናጦስ በኋላ አቡነ ሰላማ ክሳቴ ብርሃን
የተወለዱት በ፬ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ
የትውልድ ቦታ ሶርያ
ኖረው ያረፉት በአክሱም አክሱም ኢትዮጵያ በ፫፻፸፭ ዓ.ም.
ዓመታዊ በዓላቸው የሚከበረው

ታኅሣሥ ፲፰ ቀን በኢትዮጵያ አቆጣጠር

ዲሴምበር 14 በጁሊያን ካላንደር

ኦክቶበር 27 በጌሬጎሪያን አቆጣጠር

የሚከበሩት

ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን

በኮፕት ቤተ ክርስቲያን

በኦርየንታል ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን


ፍሬምናጦስ በእንግሊዘኛ Frumentius የተወለዱት ታይር በምትባል ቦታ በምሥራቃዊ የሮማ ነገሥት በ፬ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያዎቹ ሲሆን ማንም መርምሮ ሊደርስበት በማይችለው በእግዚአብሔር ሀሳብ ወደ ኢትዮጵያ መተው ክርስትናን ከመሠረቱት ዋነኛው አባት ሆኖ በመቆጠር ፣ አገራችንን ከሌሎች ክርስቲያን አገሮች ጋር ያስተዋወቁ ፣ ያስተካከሉ ፣ በአክሱም ዘመነ መንግሥትና መንግሥት የተወደዱና የተከበሩ ፣ በመላው ኢትዮጵያ የክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች የተከበሩ ታላቅ አባት ናቸው ።

አባታችን ፍሬምናጦስ የ፲፪ ዓመት ልጅ እያለ ሜሮጵዮስ የተባለ ነጋዴ ፈላስፋም የነበረ መርከበኛ ይዞት ወደ አገራችን መጣ ። ከእርሱም ጋር ወንድሙ ኤድስዮስ የተባለም አብሮት እንደነበረ ይታወቃል ። እነዚህን ሁለት ወጣቶች አስከትሎ የመጣው ሜሮጵዮስ በቀይ ባሕር አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች በጣሉለት አደጋ በዚሁ እንደ ሞተ ታሪክ ይነግረናል ። ይህም በንጉሥ ዒዛና ዘመነ መንግሥት ሆነ ።

በአክሱም መንግሥት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ፍሬምናጦስና ኤድስዮስ ግን በወቅቱ የአክሱም ንጉሥ የነበረው ንጉሥ ታዜር ጋር አድገዋል ። ንጉሡ በአእምሮ መብሰላቸውን ተመልክቶ ፍሬምናጦስ በጅሮንድ ኤድስዮስም ጋሻ ጃግሬው አድርጎ ሾማቸው ። ከዚያ በኋላ ንጉሥ ታዜር ሲያርፍ ወደ ፈለጉበት እንድሄዱ ነፃ ስለተለቀቁ ኤድስዮስ ወደ አገሩ ተመልሶ ሄዷል ። አባታችን አቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ግን ወንድሙን ሸኝቶ "በጨለማ የሚኖረውን ሕዝብ ትቼ ወደ አገሬ አልመለስም" በማለት የኢትዮጵያን ሕዝብ በማፍቀር እንደቀረ ታሪክ ያስረዳናል ። የቅዱሳን ፍቅራቸው እውነትም ልብ ይነካል ።

ጳጳስ የሆኑበት ምክኒያት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በዚያን ዘመን በአገራችን ኢትዮጵያ ክርስትና ነገሥታቱ የታወቀ ቢሆንምኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ስርዓተ ንስሐ ፣ ስርዓተ ጥምቀት ፣ ስርዓተ ቅዳሴ ፣ ስርዓተ ቅዱስ ቁርባን የሚያከናውን ጳጳስ ስላልነበረ ይህን የተመለከቱ ነገስታት ኢዛናና ሳይዛና ጵጵስና እንዲያመጣ አባታችን አቡነ ሰላማን ወደ ግብጽ ላኩት ። አባታችንም ወደ ግብጽ በመሄድ ስርዓቶቹን በመማር በቅዱስ አትናትዮስ አንብሮተ እድ "ኤጲስ ቆጶስ ዘአክሱም ወዘኩላ ኢትዮጵያ" ተብሎ ጵጵስና ተቀበለ።

አስተዋዕጾዋቸው[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ወደ አገራችን ከተመለሰ በኋላ መጀመሪያ ነገስታት ኢዛናና ሳይዛናን አጥምቆና አቁርቦ አብርሃወ አፅበሃ በማለት ስመ ክርስትና ሰጣቸው ። በመቀጠልም በመላው አገራችን እየተዘዋወረ በማስተማር ስርዓቱን ፈጽሟል ። ከዚህም የተነሳ ጨለማን አስወግዶ ብርሃንን የገለጠ ቀዳሚ የምድረ ሐበሻ ታላቅ ሐዋርያ ነው ። የቀናች ሃይማኖትን በማስተማር ጨለማውን ብርሃን በማድረጉ "ብርሃን ገላጭ ሰላማ" ተብሏል። የሓምሌ ወር ስንክሳር አባታችን አቡነ ሰላማ በኢትዮጵያና ኤርትራ በመላው ምድረ ሓበሻ በኪደተ እግሩ ተመላለሶ ወንጌል እንዳስተማረና ስፍር ቁጥር የሌላቸው ድውያንን ፈውሶ ሙታንን እንዳስነሳ ገድሉ ያስረዳናል ። በተለያዩ ባዕድ አምልኮ ያመልክ የነበረ ሕዝብም በጣፋጭ ስብከቱ እግዚአብሔርን ወደ ማመን መልሶታል ። በጸሎቱ አጋንንትን ጠራርጎ ከአገራችን በማስወጣት ሰላም የሰጠን የሰላም አባት ነው ። "ሰላማ" ማለት "ሰውና እግዚአብሔርን የሚያስታርቅ" ማለት ነው ። አባታችን አቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን በ ፫፻፶ ዓ.ም. ክርስትና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሃይማኖት ሆኖ እንዲታወጅ አድርጓል ። "አቡነ" ወይም "አባታችን" የሚለውን ማዕረግ ለመጀመሪያ የተሰጠው ለርሱ ነው ። ጻድቁ አባታችን በዕድሜም በጸጋም ትልቅ አባት በመሆኑ ከኋላው ለመጡት ብዙዎች ቅዱሳን መምህራቸውና አባታቸው ነው ። ለዚህም ነው አባታችን ቅዱስ ያሬድ "ዝንቱ ብእሲ መምህርነ ዘተፈነወ ውስተ ምድርነ ይከሰተ ብርሃነ" በማለት አመስግኖታል ። ብርሃንን ለመግለጥ ወደ አገራችን የተላከ መምህራችን ማለቱ ነው ። በልጅነቱ የመጣው አባታችን አቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን የአገራችን ፍቅር አስገድዶት እስከ ዕለተ ዕረፍቱ በአገራችን የኖረ ሲሆን በእነዚህ ጊዜያቶች ውስጥ ከሰራቸው የተለያዩ ድንቅ ሥራዎች ውስጥ በጥቂቱ እንደሚከተለው ይሆናል።

ድንቅ ሥራዎቻቸው[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  • ወንጌል የሚያስተምሩና የሚያጠምቁ የሚያቆርቡ ካህናትና ዲያቆናት ሾመ።
  • ለምእመናን መካሪ የንስሐ አባት እንዲኖራቸው አድርጓል።
  • ከአብርሃ ወአጽብሃ ጋር በመሆን አብያተ ክርስቲያን አንጸዋል።
  • ቅዱሳት መጻሕፍት ከሱርስት፣ እብራይስጥና ከግሪክ ወደ ግእዝ ቋንቋ እንዲተረጎሙ አድርጓል።
  • የሳባውያን ፊደል አቀማመጥ በማስተካከል ከግራ ወደ ቀኝ የመጻፍንና የማንበብን ዘዴ በማስተማር በተጨማሪ ፊደላችን የተለያየ ድምፅ ኢንዲኖረው (ቯዬል፡voyelle) በመጨመር ብዙ ውለታ የዋሉልን ታላቅ አባት ናቸው ።