2 አመነምሃት

ከውክፔዲያ
2 አመነምሃት
የኑብካውሬ ምስል
የኑብካውሬ ምስል
የግብጽ ፈርዖን
ግዛት 1938–1905 ዓክልበ.?
ቀዳሚ 1 ሰኑስረት
ተከታይ 2 ሰኑስረት
ሥርወ-መንግሥት 12ኛው ሥርወ መንግሥት
አባት 1 ሰኑስረት


ኑብካውሬ 2 አመነምሃት ግብጽን በመካከለኛ መንግሥት (12ኛው ሥርወ መንግሥት) ከ1938 እስከ 1905 ዓክልበ. ግድም ድረስ የገዛ ፈርዖን ነበረ። የአባቱ 1 ሰኑስረት ተከታይ ነበር።

በሰኑስረት ዘመነ መንግሥት በ፵፫ኛው ዓመት (1940 ዓክልበ. ግድም) ልጁን ኑብካውሬን ከእርሱ ጋር በጋርዮሽ ወደ ዙፋኑ አስነሣው። ከዚህ ሁለት ዓመት በኋላ በ1938 ዓክልበ. ግድም ሰኑስረት ዓረፈና ፪ አመነምሃት ለብቻው ፈርዖን ሆነ ይመስላል።

ድርጊቶቹ ሁሉ አይታወቅም፣ አንድ የዜና መዋዕል ጽላት ለኑብካውሬ ዘመን ተገኝቶ የአመቶች ቁጥር ግን አይሰጠም። ከተመዘገቡ ሥራዎቹ መካከል፦ ወደ ሊባኖስ የንግድ ጉዞ ላከ፤ «ኢዋይ» (?) በሶርያ ለማጥፋት ሠራዊት ላከ፤ የኩሽ መንግሥት ተልእኮዎች ምርት ወደ ግቢው አመጡ፤ የሶርያ ተልእኮዎች ምርት ወደ ግቢው አመጡ፤ «ኢዋይ»ና «ያሲ» በሶርያ ለማጥፋት የተላከው ሥራዊት ተመለሠ፤ ወዘተ።[1]

ከዚህ በቀር እንደ ቀድሞ ዘመናት ፈርዖኖች በመምሰል «ነጭ ሀረም» የሚባል መቃብር አሠራ። ከጨቲዎቹ (አማካሪዎቹ ወይም ጠቅላይ ሚኒስትሮቹ) ሰኑስረት እና አመኒ ይታወቃሉ። ሁለት በጅሮንዶች ሳእሰት እና መሪካው በስም ይታወቃሉ፤ አንድ መኮንን ኸንቲኸቲወር ደግሞ ወደ ፑንት ምድር ጉዞ እንደ መራ በጽላት ላይ አስቀረጸ።

በኑብካውሬ ዘመነ መንግሥት በ፴፫ኛው ዓመት (1907 ዓክልበ. ግድም) ልጁን 2 ሰኑስረት ከእርሱ ጋር በጋርዮሽ ወደ ዙፋኑ አስነሣው። ከዚህ ሁለት ዓመት በኋላ በ1905 ዓክልበ. ግድም ኑብካውሬ ዓረፈና ፪ ሰኑስረት ለብቻው ፈርዖን ሆነ ይመስላል።

ቀዳሚው
1 ሰኑስረት
ግብፅ ፈርዖን
1938-1905 ዓክልበ. ግድም
ተከታይ
2 ሰኑስረት
  1. ^ የአመነምሃት ዜና መዋዕል (እንግሊዝኛ)