ሠርፀ ድንግል
| ዓፄ ሠርፀ ድንግል | |
|---|---|
| በእምፍራዝ፣ ጎንደር በ1571 ዓፄ ሠርፀ ድንግል የገነቡት የጉዛራ ቤተ መንግስት | |
| ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ | |
| ግዛት | ከ1563 እስከ 1597 እ.ኤ.አ. |
| ቀዳሚ | ዓፄ ሚናስ |
| ተከታይ | ዓፄ ያዕቆብ |
| ባለቤት | ንግሥት ማርያም ሰና |
| ሙሉ ስም | መልአክ ሰገድ (የዙፋን ስም) |
| ሥርወ-መንግሥት | ሰሎሞን |
| አባት | ዓፄ ሚናስ |
| እናት | አድማስ ሞገሴ |
| የተወለዱት | 1550 እ.ኤ.አ. |
| የሞቱት | 1597 እ.ኤ.አ. |
| የተቀበሩት | መድሀኒ ዓለም ቤተ ክርስቲያን፤ ሪማ ደሴት |
| ሀይማኖት | የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ክርስትና |
አፄ ሠርጸ ድንግል ( 1550 - 4 ጥቅምት 1597 እ.ኤ.አ) ) በዙፋን ስማቸው "መልአክ ሰገድ" የኢትዮጵያ ንጉስ ሲሆኑ የነገሱበትም ዘመን ክ (1563 - 1597 እ.ኤ.አ ) ነበር። የኒህ ንጉስ አባት አጼ ሚናስ ሲሆኑ እናታቸው ደግሞ አድማስ ሞገሴ በመባል ይታወቃሉ። አድማስ ሞገሴ ህጻኑን ሱስኒዮስንም ተንከባክበው በማሳደግ በታሪክ ተመዝግበዋል። የሰርጸ ድንግል ዘመን የሚታወቀው ሁለት ፈተናወችን በማለፍ ነው እነሱም ከሰሜን የተቃጣው የቱርኮች ወረራና ከደቡብ ደግሞ የኦሮሞ ቡድኖች ወደሰሜን ወረራ በማክሸፍ ነበር።
ሚስታቸው ንግስት ማርያም ሰናም ለቀጣዮቹ ነገስታት መነሳትም ሆነ መውደቅ ባበረክተችው አስተዋጽኦ በታሪክ ትታወሳለች።
ማውጫ |
[ለማስተካከል] የዘመኑ ግርግር
በህጻንነቱ አገሪቱ የብጥብጥ አገርና በየጊዜው የሚቀያየር ደምበር ያላት፣ የማያቋርጥ ዘመቻ የሚካሄድባት ነበረች። በዚህ ምክንያት ቋሚ ዋና ከተማ ያልነበራት እና በበጋው ወቅት ጦርነት የሚካሄድባት በክረምት ደግሞ ሰፊ ሰራዊት በመያዝ ከጊዜ ወደጊዜ በሚቀያየረው ዋና ከተማ የሚሰፈርባት ነበረች። በዚህ ጊዜ መኳንንቶቹ ለነሱ ፈቃድ የሚታዘዝ ንጉስ የሚፈልጉበት ጊዜ ነበር። የወደፊቱ ንጉስ ስልጣን ተቀናቃኞች፦ ሐመልማል፣ ሐርቦ፣ አቤቶ ፋሲል እና ይስሐቅ እርስ በርሳቸው መካካድና መጣላት ስላበዙ ሰርጸ ድንግል ከነሱ ተለይቶ ርቆ በመሄድ የራሱን ሰራዊት አዘጋጅቶ በግብረ ገብ በማነጽ ቀስ በቀስ ወደስልጣን ወጣ። በሸዋ ውስጥ ይገኙ የነበሩ የጦር መሪወች ምርጫ በማካሄድና ብሎም በዘመኑ የነበረችው "እናት ንግስት" ሰብለ ወንጌል በማጽደቋ ንጉሰ ነገስት ለመሆን በቃ።
[ለማስተካከል] የአጎቱ ልጆች ማመጽ
ይህ ከሆነ በኋላ ባህር ንጉስ ይስሃቅ የተባለው ያሁኑ ኤርትራ መሪ በአጼ ሚናስ ዘመን ያመጸ ቢሆንም ልጁ ሲነግስ የልጁን ስልጣን ተቀበለ። ይሁንና ሰርጸ ድንግል ሙሉ ሰላም ኑሮት አገሪቱን አላስተዳደርም ። የራሱ ያጎት ልጅ የሆነው ሐመልማል በ1563 ፣ ክሁለት አመት በኋል ፋሲል የተባለው ሌላው ያጎቱ ልጅ አመጽ አስነስተውብታል (ምንም እንኳ ሁቱም ቢሸነፉ)።
[ለማስተካከል] የቱርኮች ጦርነት፣ የግንቦች መታነጽ ፣ በአክሱም የአክሊል መድፋት
መልሶም በ1569 ከቱርኮች ጋር ባደረገው ጦርነት ለመጀመሪያ ጊዜ ቱርኮችን አሸነፈ። ለዚህ መታሰቢያ በእምፍራዝ (ጉዛራ) በ1571 ቤ/መንግስት አሰራ። ወደ ሰሜንም በመዝለቅ በወገራ እና በአይባ ሌሎች ቤ/መንግስቶችን አሰርቷል። የኪዳነ ምህርት ቤ/ክርስቲያንም እንዲሁ።
ከዚያም ባህር ንጉስ ይስሐቅ በኦቶማን ቱርኮችና በአዳል ሰራዊት ታግዞ አመጽ ማስነሳቱ አልቀረም። በዚህ ጊዜ ንጉሱ ወደ ትግራይ በመዝመት በ1578 ባህረ ነጋሹንና (በአዲ ቆሮ) አባሪ ኦቶማኑን ኦዝደሚር ፓሻንና የአዳል መሪ የነበረውን ሱልጣን መሃመድ አራተኛ (በተምቤን) ጦርነት አሸንፎ ገደላቸው። በድባርዋ (የድሮው ኤርትራ ዋና ከተማ) የነበሩት ቱርኮችም ያለምንም ተኩስ እጃቸውን ሰጡ። በዚያውም ሰርጸ ድንግል በአክሱም ስርዓተ ተክሊሉን ፈጸመ (ይህ እንግዲህ ከዘርዓ ያዕቆብ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑ ነው)፣ መልአክ ሰገድ የሚለውንም ስም ያገኘው በዚህ ግዜ ነበር። ከ10 አመት በሁዋላ፣ በ1588 ኦቶማን ቱርኮች፣ ከተባረሩበት ድባርዋ መልሰው ሊቆጣጠሩ ሲሞክሩ በመሸነፋቸው አርቂቆ ላይ የነበረውን ግዛታቸውን ሰርጸ ድንግል አፈረሰባቸው። በዚህ ምክንያት የቱርኩ መሪ ፓሻ በወርቅ ያጌጠ ፈረስ እስከ ሳዱላው በመላክ ከንጉሱ ዘንድ ሰላም እንደሚሻ አስታወቀ። [1]
[ለማስተካከል] ሌሎች ዘመቻዎች እና ሰላም
ሰርጸ ድንግል የኖረበት ዘመን ከግራኝ አህመድ ወረራ ጥቂት ዘመን አሳልፎ ስለነበር የህዝቦች ፍልሰት በዚሁ ዘመን ይታይ ነበር። የኦሮሞን ወደ ሰሜን ወረራ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጋፈጠ ንጉስ ይሄው ሰርጸ ድንግል ነው። በዚሁ ዘመን የኦሮሞወች ጥንካሬ ከማየሉ የተነሳ ኑር ኢብን ሙጃሂድ የተሰኘውን የግራኝን ምትክ በመግደል ሐረርን ወረው ነበር። ቀጥሎም ወደሰሜን በመዝመት ሰርጸ ድንግል በነገሰ በ10ኛው አመት ዝዋይ ሃይቅ አካባቢ ከንጉሱ ሰራዊት ጋር ተጋጭተው ተሸነፉ። ከዚህ በኋላ ንጉሱ በኦሮሞወች ቡድኖች ላይ በ1578 እና በ1588 ዘምቷል።
በ1580 እና 85 ደግሞ በቤተ እስራኤል (ፈላሾች) ቡድኖች ላይ ዘምቷአል። አገው ላይም በ1581 እና 85፣ ጋምቦ ላይ በ 1590 እናም ሱዳን ውስጥ በሻንቅላ ላይ አድርጓል። እንራያ ደግሞ ሁለት ጊዜ በ 1586 እና 97 ጦርነት በመክፍት ህዝቡን ከነመሪያቸው ክርስቲያን አደርገ። ስለመጨረሻው የ1597 ዓ.ም. ዘመቻው የንጉሱ ዜና-መዋዕል [2] እንዲህ ሲል ያትታል፡
- መነኮሳት ተሰብስበው ንጉሱ ወደዳሞት ጦር ሜዳ እንዳይሄድ ለመኑት፣ ንጉሱ ግን ልቡ እንደደነደነ ስለተገነዘቡ በተወሰነ ወንዝ [አሳ የሚበዛበት የገሊላ ወንዝ ] ውስጥ የሚገኝን አሳ እንዳይበላ አጥብቀው አስጠነቀቁት። እሱ ግን የተባለውን ቸል በማለት ባስጠነቀቁት ወንዝ ሲያልፍ ከዚይ ወንዝ የወጣን አሳ በላ። ሳይዘገይም በጸና ታመመና ሞተ። [3]
በሞተም ጊዜ ሬማ ደሴት፣ ጣና ሃይቅ፣ መድሃኔ አለም ቤ/ክርስቲያን ተቀበረ። [4]
የሰርጸ ድንግል መንግስት ረጅምና ከመጀመሪያው ጀምሮ ብዙ ጦርነት የበዛበት ቢሆንም ንጉሱ ለልጁ ያዕቆብ ያስረከበው ግዛት ግን ሰላማዊና ያልተከፋፈለ ታላቅ ሃገር ነበር። [5]
[ለማስተካከል] የስልጣን ሽግግር
በጥንቱ ኢትዮጵያ ታሪክ የስልጣን ሽግግር ብዙ ችግር የተሞላበት ነበር። የሰርጸ ድንግል ስርዓትም ከዚህ አላመለጠም። አጼ ሰርጸ ድንግል ከህጋዊ ባለቤታቸው ንግስት ማርያም ሰና ሴት ልጆችን እንጂ ወንድ ልጅ አላገኙም። ሐረግዋ ከተባለች የቤተ እስራኤል (ፈላሻ) ቅምጣቸው ግን ያዕቆብ የሚባል ወንድ ልጅ ነበራቸው። ይሁንና ልጅ አባቱ በሞተ ጊዜ ገና የ7 አመት ህጻን ነበር። በዚህ ምክንያት የሰርጸ ድንግል ወንድም ልጅ የነበረው ዘድንግል ስልጣን ላይ ይወጣል የሚል ግምት በመላ ሃገሪቱ ተንሰራፍቶ ነበር። ነገር ግን ንግስት ማርያም ሰና ከልጆቻ ባለቤቶች ራስ አትናትዮስ የጎንደር መሪ እና ራስ ክፍለ ዋህድ የትግራይ መሪ ጋር በመሆን ህጻኑን የእንጀራ ልጇን ያዕቆብን በራስ አትናቲዮስ ሞግዚትነት የንጉሰ ነገስትነቱን ስልጣን እንዲወርስ አደረገች።
[ለማስተካከል] ማጣቀሻወች
- ^ Hubert Jules Deschamps,(sous la direction). Histoire générale de l'Afrique noire de Madagascar et de ses archipels Tome I : Des origines à 1800. Page 410-411 P.U.F Paris (1970);
- ^ በፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክኸርስት የተተረጎመ "The Ethiopian Royal Chronicles. Addis Ababa: Oxford University Press, 1967.
- ^ G.W.B. Huntingford, Historical Geography of Ethiopia (London: British Academy, 1989), p.149.
- ^ R.E. Cheesman, "Lake Tana and Its Islands", Geographical Journal, 85 (1935), p. 498
- ^ Hubert Jules Deschamps,(sous la direction). Histoire générale de l'Afrique noire de Madagascar et de ses archipels Tome I : Des origines à 1800. Page 410-411 P.U.F Paris (1970);
|
||||||||||||||