ኡራርቱ

ከውክፔዲያ
ኡራርቱ ከ868-848 ዓክልበ. በንጉሥ አራሙ

ኡራርቱ በጥንት የነበረ መንግሥት ሲሆን በደብረ አራራት ዙሪያ ተገኘ።

ስያሜው «ኡራርቱ» አሦርኛ ሲሆን ከደብረ አራራት ስም ጋር እንደ ተዛመደ ይታሥባል። በአሦርኛ ሰነዶች «ኡራርቱ»ና «ናይሪ» የሚሉት ስሞች ለዙሪያው ከ1300 ዓክልበ. አካባቢ ጀምሮ ተዘግበዋል። በተጨማሪ በሱመር አፈ ታሪክ «አራታ» የተባለ ሀገር ምናልባት 2450-2350 ዓክልበ. ይታወቅ ነበር፣ እሱም ከአሶርኛው «ኡራርቱ» ጋር ዝምድና እንዳለው የሚያስቡ አሉ። በትንቢተ ኤርምያስ (ብሉይ ኪዳን 600 ዓክልበ. አካባቢ) ደግሞ በ51:27 የአራራት፣ የሚኒ እና የአስከናዝ መንግሥታት ሲጠቅስ፣ ይህ «አራራት መንግሥት» ማለት በዚያን ጊዜ የነበረው የኡራርቱን መንግሥት ይገልጻል። በኡራርትኛ የመንግሥቱ ስም «ቢያይኒሊ» ተባለ።

ከአሦርኛ መዝገቦች እንደምናውቅ፣ ከ1300 እስከ 868 ዓክልበ. ድረስ እነዚህ «ናይሪ» ወይም «ኡሯትሪ» ብሔሮች በተለያዩ ነገዶች ይኖሩ ነበር፤ በ868 ዓክልበ. የናይሪ ሕዝቦች በንጉሥ አራሙ ተባብረው የኡራርቱ (ቢያይኒሊ) መንግሥት ፈጠሩ።

የኡራርቱ የራስ ቁር

በቋንቋ ረገድ ኡራርትኛ ከበፊቱ ሑርኛ ጋር ተዛመደ። ሑራውያን በተለይ ከ2075-1300 አክልበ በስሜን መስጴጦምያ ይታወቁ ነበር።

ይህ የኡራርቱ መንግሥት ከ868 ዓክልበ ጀምሮ እስከ 598 ዓክልበ. ድረስ ያህል ቆየ። በ598 ዓክልበ. የሜዶንና የእስኩቴስ ሰዎች ወርረው የኡራርቱን መንግሥት ጨርሰው ሀገሩ ከዚያ በኋላ በተለይ «አርመኒያ» ተብሏል።