ፖርቱጋል

ከውክፔዲያ

República Portuguesa
የፖርቹጋል ሪፐብሊከ

የፓርቹጋል ሰንደቅ ዓላማ የፓርቹጋል አርማ
ሰንደቅ ዓላማ አርማ
ብሔራዊ መዝሙር "A Portuguesa"

የፓርቹጋልመገኛ
የፓርቹጋልመገኛ
ዋና ከተማ ሊዝቦን
ብሔራዊ ቋንቋዎች ፖርቹጊዝ
መንግሥት
ፕሬዚዳንት
ጠቅላይ ሚኒስትር
ፕሬዚዳንታዊ ሪፐብሊክ
ማርሴሎ ሬቤሎ ደ ሶሳ
አንቶኒዮ ኮስታ
የመሬት ስፋት
አጠቃላይ (ካሬ ኪ.ሜ.)
ውሀ (%)
 
92,391 (110ኛ)
0.5
የሕዝብ ብዛት
የ2016 እ.ኤ.አ. ግምት
የ2021 እ.ኤ.አ. ቆጠራ
 
10,309,573 (83ኛ)
10,343,066[1]
ገንዘብ ዩሮ (€)
ሰዓት ክልል UTC ±0 / UTC +1
የስልክ መግቢያ +351
ከፍተኛ ደረጃ ከባቢ .pt


ፖርቱጋል ወይም ፖርቹጋል (ፖርቱጊዝኛPortugal /ፑርቱጋል/) በኤውሮፓ ውስጥ የሚገኝ ሀገር ነው። የፖርቹጋል መንግሥት በምዕራብና በደቡብ ከአትላንቲክ ውቅያኖስ፤ በምሥራቅና በሰሜን ከኤስፓኝ መንግሥት ጋር ይዋሰናል።

ስም[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የፖርቱጋል ስም ከአንድ ሮማይስጥ ወደብ ስም /ፖርቱስ ካሌ/ («የካሌ ወደብ»፣ የአሁንም ፖርቱ) መጥቷል። የ«ካሌ» ትርጉም እዚህ ቢካራከርም ዋናው አስተሳሰብ ከጋሊስያ (የእስፓንያ ክፍላገር) እና ከጥንቱ ጋላይኪ ወገን (ኬልቶች) ጋር እንደ ተዘመደ የሚለው ነው። በየጥቂቱ የሮማይስጥ አጠራር /ፖርቱስ ካሌ/ ወደ /ፖርቱካሌ/ (400 ዓም ግ.)፣ እና /ፖርቱጋሌ/ (600 ዓም ግ.) ተለወጠ፣ ከ800 ዓም ግ. በኋላ ለመላው አውራጃ ይጠቀም ጀመር። «ፖርቱጋል» (Portugal) የሚለው አጻጻፍ ከ1000 ዓም ግድም ጀምሮ ሲገኝ፣ በአማርኛ ደግሞ የአገሩ ስም እንደ እንግሊዝኛው አጠራር እንደ ፖርቹጋል ሊጻፍ ይችላል። የብርቱካን ፍራፍሬ፣ ዛፍ፣ ቀለም ስም ደግሞ ከፖርቱጋል ስም ደርሶልናል።

ታሪክ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የፖርቹጋል የጥንት ስም ሉዚታኒ ነው። በመጀመሪያም በአገሪቱ የነበሩት ሕዝቦች ሴልቶ ኢቤሪክ የሚባሉ የህንዶ-ኤውሮፓዊ ወገን ሆነው በኋላ ወደ ላቲንነት በልማድና በኑሮ በሃይማኖትም የተለወጡ ናቸው። የፖርቱጋል ሕዝብ በጀርመንና በኖርማንዲ በሮማውያንና በዐረቦች ሞሪ (ማውሪታኒ) ከሚባሉ በአፍሪካ ሰሜን ሕዝብና በዕብራውያንም የተቀያየጠ ነው። ነገር ግን እነዚህ ሁሉ ባንድነት ሰፊ ዘመን በሮማ መንግሥት ስለ ተገዙ በዘርም በልማድም አብዛኛውም ወደ ላቲንነት ተለውጠዋል። የሮማ መንግሥት ከወደቀ በኋላ በአምስተኛውና በስምንተኛው መቶ ዓመተ ምሕረት መካከል በነበረው ጊዜ ውስጥ እየተከታተለ ቢዚጎትና ስቤብ የሚባሉ የጀርመኖች ቀጥሎም የዐረቦች ወረራ ደርሶባቸዋል። በአስረኛው መቶ ዓ.ም. ግን አስቱሪዩ የሚባሉት የክርስቲያን ወገኖች እስላሞቹን አጥፍተው ሊስቦን ገብተው ገዥ ሆነው መንግሥታቸውን አቋቋሙ። ከዚያ ከ፲፪ እስከ ፲፬ መቶ ዓ.ም ድረስ ቤተ መንግሥቱን የቡርጎኝ ሥርወ መንግሥት ሲገዛው ቆይቶ በኋላ ሔቢዝ ለተባለው ቤተ መንግሥት አሳለፈው። በነዚህ መሪነት ጊዜ ይኸውም ማለት በ፲፬ኛውና በ፲፭ኛው መቶ ዓመተ ምሕረት ላይ የፖርቱጋል መንግሥት ከሌላው ሁሉ ይልቁንም በባሕርና በመርከብ ኃይል ሆነ።

በዚህ በ፲፭ኛው መቶ ዓ.ም. ላይ የቱርክ፣ የመስኮብ፤ የጀርመን፤ የእንግሊዝ፤ የፈረንሳይና የኤስፓኝ መንግሥታት እንደ ኃያላን መንግሥታት መቆጠራቸው አልቀረም። ነገር ግን ከነዚህ ሁሉ የፖርቱጋል መንግሥት በሌላው እንኳን ባይሆን በመርከብና አገር በመያዝ ከቀሩት ይበልጥ ነበር። የቀሩት የኤውሮፓ መንግሥታት እዚያው ወሰናቸው ላይ ገዥነታቸውን ለማጽደቅ እርስ በርሳቸው ሲጨቃጨቁ የፖርቱጋል መንግሥት ግን ደኅና ደኅና መርከቦችን አዘጋጅቶ እየላከ ከመንግሥቱና ከኤውሮፓ ርቆ የሚገኘውን የአሜሪካን፤ የእስያን፤ የአፍሪካን አገሮች ያስመረምር ነበር። መርማሪዎቹም እነቫስኮ ደጋማ፤ እነፔሬዝ፤ እነአንድራድ፤ እነካብራል በመርከብ እየሄዱ ለመከላከል ጉልበት የሌለውንና በጠባዩ ሀብት ያለበትን አገር መርምረው ሲመለሱ መንግሥቱ ወታደር በመርከብ እየላከ ብዙ አገር ያዘ።

በሚያዝያ ፳፩ ቀን ፲፭፻ እ.ኤ.አ. ፔድሮ አልቫሬዝ ካብራል የተባለው የፖርቱጋል መኮንን በትልቅ መርከብ ሄዶ ይን ጊዜ ለቀረው ዓለም ያልታወቀውን የብራዚልን አገር አስገበረና በፖርቱጋል መንግሥት ስም ቅኝ አገር አደረገው። ከዚያም አገር በተገኘው ወርቅ መንግሥቱ ሀብታም ሆነ። እንደዚሁም የመጀመሪያ የንጉሥ እንደራሴ የተባለው ፍራንቼስኮ ዳልሜዳ ወደ ህንድ አገር ሄዶ አገሩን ያዘ። ከተማውንም በጎአ አድርጎ ህንድንም የፖርቱጋል የቄሣር ግዛት አደረገና አገር ገዥውም የንጉሥ እንደራሴ ይባል ጀመር። ከዚያም በትልቁ ውቅያኖስ ውስጥ የሚገኙትን ደሴቶች ኑቤል ጉኔንና ዛሬ ፊሊፒን የሚባለውን አገር በየጊዜው በጦር ኃይል አስገበራቸው።

በዚሁ አኳኋን ወደ ኢትዮጵያም እነኮቪልሐኦ ቀደም ብለው በዓፄ እስክንድር ዘመን መጥተው እንደመረመሩትና የኢትዮጵያ መንግሥት በዚያ ጊዜ በነሱ አጠራር የቄሱ የዮሐንስ መንግሥት አለ ብለው አውርተው እንደነበረ ሌላ የፖርቱጋል የጦር መርከብ በአፍሪካ ድንበር በቀይ ባሕር ላይም እየተመላለሰ አስቀድሞ ከያዙት ከቱርኮችና ከግብጾች እየተዋጋ አንድ ጊዜም እየተሸነፈ አንድ ጊዜም እያሸነፈ ብዙ ጊዜ ተመላለሰ። በዚህ ሁሉ ምክንያት የፖርቱጋል መንግሥት ታላቅነት በሌላው ዓለም እንደ ታወቀ እንደዚሁም ፩ኛ ትልቅ መንግሥት መሆኑ ፪ኛ ክርስቲያን መሆኑ ኢትዮጵያ ባሉት የውጭ አገር ሰዎች አፍ እየተነገረ ዝናው በኢትዮጵያ ቤተ መንግሥት ዘንድ መሰማት ቻለ።

ደግሞ ይዩ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ዋቢ ምንጭ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ https://tabulador.ine.pt/indicador/?id=0011609&lang=EN የ2021 ቆጠራ፣ ብሔራዊ የስታስቲክስ ተቋም