መሐመድ

ከውክፔዲያ

ሙሐመድ (አረብኛ፦ محمد) 563-624 ዓ.ል. ተጨማሪ ስያሜዎች: የአላህ መልእክተኛ፣ ነብዩ፣ ረሱል።

አረቢያ ምድር የተነሳ ሃይማኖታዊና ፖለቲካዊ መሪ ነበር። በኢስላም እምነት የአምላክ (አላህ) የመጨረሻ ነቢይ እንደሆነ ይታመናል ። የአብርሃም ልጅ እስማኤል ሀረገ-ትውልድ ያለው ሰው እንደ ሆነ ይታመናል፤ የአረቢያ ምድር አልፎም አለም በባእድ አምልኮ በተጥለቀለቀበትና አለም ከእውነተኛው አምላክ አላህ ውጪ ሌላን ማምለክ በጀመረበት ግዜ አላህ የሰው ልጆችን ወደተፈጥሮአዊው ሐይማኖት (አላህን ብቻ ወደ ማምለክ) ይመልሱ ዘንድ የላከው የነብያት መደምደሚያ ነው።


ሙሐመድ የዐብደላህ ልጅ፣ የአብዱል ሙጦሊብ ልጅ፣ የሃሽም ልጅ፣ የአብዱመናፍ ልጅ፣ የቁሰይ ልጅ፣ የኪላብ ልጅ፣ የሙራ ልጅ፣ የከዕብ ልጅ፣ የሉአይ ልጅ፣ የጛሊብ (ጋሊብ) ልጅ፣ የፊህር (ቁረይሽ) ልጅ፣ የማሊክ ልጅ፣ የነድር ልጅ፣ የኪናናህ ልጅ፣ የኹዘይማ ልጅ፣ የሙድሪካ ልጅ፣ የኢልያስ ልጅ፣ የሙደር ልጅ፣ የኒዛር ልጅ፣ የመዕድ ልጅ፣ የዐድናን ልጅ።

ዐድናን ዘሩ ወደ የአላህ ነብይ እስማዒል ይሄዳል። ኢስማኤል ደግሞ የአላህ ወዳጅ የኢብራሂም (አብርሃም) ልጅ ነው።

ሙሐመድን (ሰ.ዐ.ወ), አላህ ከጥሩ ዘር መረጣቸው። የመሐይምነት ዘመን ቆሻሻም ወደ ዘር ግንዳቸው አልገባም (በትዳር የተወለደ ሰው እንጂ በዘራቸው የለም)።

ሙስሊም እንደዘገቡት የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡-

“አላህ ከእስማዒል ልጆች ኪናናን፣ ከኪናናህ ልጆች ውስጥም ቁረይሽን፣ ከቁረይሽ ሃሽምን፣ ከበኒ ሃሽም በኩል ደግሞ እኔን መርጧል።” (ሙስሊም ዘግበውታል)

"አወላለዳቸው"

የተወለዱት የዝሆን አመት (ዓመል ፊል) በመባል በሚታወው ዘመን ነው። ይህም ዓመት ሀበሻዊው የየመን አስተዳደር የነበረው ንጉስ አብረሃ ካዕባን ለማፍረስ የሞከረበት ኣመት ነበር። አላህም እጅግ በሚያስደንቅ ጥበብና ተአምር ሐሳቡን አምክኖታል። ይህ በቁርአን ታሪክ ተወስቷል። ነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) በዚሁ አመት በወርሃ ረቢአል አወል 12ኛው ቀን በእለተ ሰኞ እንደተወለዱ ዘገባዎች ያመለክታሉ።

"አስገራሚ ጅምርና ግልጽ በረከት"

አባት አልባ ሆነው ተወለዱ። እናታቸው እርሳቸውን የሁለት ወር እርጉዝ እያለች አባታቸው ሞቱ። አያታቸው ዐብዱል ሙጦሊብም የማሳደግ ሐላፊነቱን ወሰዱ። በያኔዎቹ ዐረቦች ባህል መሠረትም ከበኒ ሰዕድ ጎሳ የሆነችና ሐሊመት ቢንት አቢ ዙዓይብ የምትባል እንስት ታሳድጋቸው ዘንድ ተሰጣት።

የታሪክ ጸሐፊዎች እንደሚስማሙት ያኔ የበኒ ሰዕድ ቀዬ በድርቅ የተመታበት አመት ነበር። የእንስሳት ጋቶች ነጥፈዋል። አዝርእቱ ደርቀዋል። ነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) በሐሊማ ቤት ካረፉበት እና ጡቷን መጥባት ከጀመሩበት ቅጽበት አንስቶ ግን የሐሊማ ቤት በበረከት ተሞላ። ፍየሎቿ ጠግበውና ጋቶቻቸው በወተት ተሞልቶ ይመለሱ ጀመር።

በበኒ ሰዕድ መስክ ላይ እያሉ የተከሰተው የደረታቸው መቀደድ አላህ ለትልቅ ሐላፊነት እንደመረጣቸው የሚጠቁም የነብይነት ምልክት ነበር። አነስ ኢቢን ማሊክን (ረ.ዐ) ዋቢ በማድረግ ሙስሊም እንደዘገቡት የአላህ መልእክተኛ በልጅነታቸው ዘመን ከሕጻናት ጋር በመጫወት ላይ እያሉ ጅብሪል (ዐ.ሰ) መጣና ያዛቸው። አጋደማቸውም። ደረታቸውንም ሰነጠቀው። ልቦናቸውንም አወጣ። የረጋ ደም የሚመስል ነገርም ከውስጡ አስወገደ። “ይህ የሰይጣን ድርሻ ነው” አለም። በወርቅ ሳህን ውስጥ አድርጎም በዘምዘም ውሃ አጠበው። ከዚያም እንደነበር ጠገነውና ወደቦታው መለሰው። ልጆችም ወደ ሐሊማ ቤት እየሮጡ ሄደው “ሙሐመድ ተገደለ” በማለት ተናገሩ። ሲመጡ የነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) ፊት ገርጥቶ አገኙት። አነስ፡- “የዚህን ክስተት ፋና ከነቢዩ ደረት ላይ አይቻለሁ” ሲሉ ተናግረዋል። ከልባቸው ውስጥ የረጋ ደም የሚመስል ነገር መወገዱ እርሳቸውን ከልጅነት አጓጉል ባህሪያት አርቆ፣ ቁም ነገረኛ፣ ጽኑ፣ ሚዛናዊና ውብ ባህሪያት የተላበሱ ለማድረግ ነው። አላህ በጣም እንደሚጠብቃቸው እና እንደሚንከባከባቸው፣ ሰይጣንም እርሳቸውን የመተናኮል አቅም እንዳይኖረው መደረጉን ለማመልከትም ጭምር ነው። (ፊቅሁ ሲራ – ዶክተር ረመዷን አል-ቡጢ)

ይህ ክስተት ሐሊማ ሕጻኑን ወደ ቤተሰቦቹ እንድትመልስ ምክንያት ሆነ። ያኔ የነብዩ (ሶ.ዐ.ወ) እድሜ አምስት አመት ነበር። ስድስት አመት ሲሞላቸው እናታቸው አሚና ሞተች። አያታቸው ሊያሳድጓቸው ወሰዷቸው። ስምንት ዓመት ሲሞላቸው አያታቸው ሞቱ። የማሳደጉን ሐላፊነትም አጎታቸው አቡ ጧሊብ ወሰዱ።

"የላቀ እጣ ፈንታ"

አስራ ሁለት አመት ሲሞላቸው አጎታቸው አቡ ጧሊብ ወደ ሻም ለንግድ እርሳቸውን አስከትለው ወጡ። ቅፍለቱ በስራህ በተባለ ቦታ ላይ ሲያርፍ ቡሐይራ የተባለን አንድ መነኩሴ ለመጎብኘት ጎራ አለ። ሰውየው የክርስትና ሐይማኖትና መጽሐፍት አዋቂ ነው። ነቢዩን (ሰ.ዐ.ወ) በትኩረት አስተዋላቸው። በጥንቃቄ አጠናቸው። አናገራቸውም። ከዚያም ወደ አቡ ጧሊብ በመዞር፡- “ይህ ልጅ ምንህ ነው?” አላቸው። “ልጄ ነው” አሉት። (አቡ ጧሊብ በጣም ስለሚወዷቸው ልጄ በማለት ነበር የሚጠሯቸው።) ቡሐይራም፡- “ልጅህ አይደለም። የዚህ ልጅ አባት በሕይወት ሊኖር አይችልም” ሲል ተናገረ። አቡ ጧሊብም “የወንድሜ ልጅ ነው” አሉ። “አባቱ ምን ሆነ?” ሲል ጠየቃቸው። “ተረግዞ እያለ ሞተ” አሉ። “እውነት ብለሐል። በአስቸኳይ ወደሀገሩ ይዘኸው ተመለስ። አይሁዶች እንዳያገኙት ተጠንቀቅ። በአላህ እምላለሁ ካገኙት ይተናኮሉታል። ለታላቅ ደረጃ የሚበቃ ልጅ ነው” አላቸው። አቡ ጧሊብም ፈጥነው ወደ መካ መለሱት።

"እንጀራ ፍለጋ"

የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ለወጣትነት እድሜ ሲደርሱ እንጀራ ፍለጋ መሮጥ ጀመሩ። ፍየል ጥበቃ የጥረታቸው መጀመሪያ ነበር። በኋላ ላይ፡- “ለመካ ሰዎች በቀራሪጥ (መጠነ ትንሽ ክፍያ) ፍየል እጠብቅ ነበር።” ሲሉ ተናግረዋል።

"አላህ ያደረገላቸው ጥበቃ"

ከወጣትነት አጓጉል ድርጊቶችና ጨዋታዎች ሁሉ አላህ ጠብቋቸዋል። ስለ ራሳቸው እንዲህ ሲሉ ተናግረዋል፡-

“በመሐይምነት ዘመን ወጣቶች ይፈጽሟቸው የነበሩ ድርጊቶችን ለመፈጸም ያሰብኩት ሁለት ጊዜ ብቻ ነበር። በነዚህም ጊዜያት አላህ ያሰብኩትን እንዳላደርግ አቀበኝ። ከዚያ በኋላ በመልእክተኛነት እስኪልከኝ ድረስ ተመሳሳይ ድርጊት አስቤ አላውቅም። ይኸውም አንድ ቀን ሌሊት በመካ ከፍታማ ቦታዎች ላይ ፍየል አብሮኝ ይጠብቅ ለነበረ ልጅ፡- ‘ፍየሌን ጠብቅልኝ። ልክ እንደወጣቶች መካ ውስጥ ስጫወት ልደር’ አልኩት። ‘ይሁን’ አለኝ። ወደ መካ ወረድኩ። እዚያ እንደደረስኩ ከአንድ ቤት ውስጥ ዘፈን ሰማሁ። ምንድን ነው? በማለት ስጠይቅ፣ የሰርግ ዘፈን እንደሆነ ተነገረኝ። ቁጭ ብዬ ማድመጥ ስጀምር አላህ ጆሮዬን ደፈነው። ጥልቅ እንቅልፍም ወሰደኝ። ከእንቅልፍ ያነቃኝ የረፋዱ ጸሐይ ግለት ነበር። ወደ ባልንጀራየም ተመለስኩ። ስለ አዳሩ ጠየቀኝ። የሆነውን ነገርኩት። በሌላ ሌሊትም ተመሳሳይ ሙከራ አደረግኩ። ልክ የመጀመሪያው ሌሊት ዓይነት ሁኔታ አጋጠመኝ። ከዚያ በኋላ ያን ዓይነት ሐሳብ አስቤ አላውቅም።”

"በአላህ ብቻ መመካት"

የፍጡራን ፈርጥ ለየት ያለ የሕይወት ጅማሬ፣ አላህ ቀልባቸው ከርሱ ውጭ በሌላ አካል እንዳይንጠለጠል እንደፈለገ ያመለክታል። በአባት፣ በእናት፣ በአያት ወይም በአጎት፣ በገንዘብ፣ በስልጣን ወይም በሌላ ነገር እንዳይመኩ የፈለገ ይመስላል። ይህ ስሜት ለሙስሊም ባጠቃላይ እና ለዳዒ በተለይ ለስብእናው ስሪት እጅግ አስፈላጊ ነው። ከሚንከባከባቸው ክንድ ወይም ድሎት ከሚለግሳቸው ሰው ገንዘብ አርቆ አላህ ብቻ ሊጠብቃቸው እና ሊንከባከበው በመሻት ይህን አደረገ። ይህ ሲሆን፣ “አባቴ” በማለት ፋንታ “አምላኬ” ይላል። ነፍሳቸውም ወደ ገንዘብ ወይም ክብር፣ ወደ አያት ቅድመ አያቶች ንግስናና ስልጣን ወደማስመለስ ስሜት አትዘነበልም። ሰዎችም የዱንያ (ምድሯዊ) ክብር ከነብይነት የተቀደሰ ደረጃ ጋር አይቀላቀልባቸውም።

ይህም በመሆኑ መልእክተኛው ነብይ ነኝ ያሉት ዓለማዊ ክብርና ጥቅም ለማግኘት ወይም በዘመናችን አገላለጽ “በሐይማኖት ለመነገድ” ነው የሚባሉ ክሶች ሁሉ የሚቆሙበት መሠረት አጡ። ዓለማዊያንና አምላክ የለሾች በቅን የዳዕዋ ሰዎች ላይ ይህን ክስ በየዘመናቱ ሲሰነዘሩት ይደመጣል።

"ጠቃሚ ትምህርቶች"

ገና በለጋ እድሚያቸው እንጀራ ፍለጋ ያሳዩት ትጋት ሦስት ጠቃሚ ትምህርቶችን አካቷል።

1. አላህ ለነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) ያላበሳቸውን ውብ ባህሪና ረቂቅ ስሜት ያሳያል። አጎታቸው የተሟላ እንክብካቤ ያደርጉላቸው ነበር። ልክ እንደ አባት ያዝኑላቸውም ነበር። ይህም ሆኖ ግን መልእክተኛው (ሰ.ዐ.ወ) ሰርተው ማደር እንደሚችሉ ሲሰማቸው ወደ ስራ ተሰማሩ። የአጎታቸውን የገንዘብ ቀዳዳዎች ያቅማቸውን ያህል ለመሸፈን ጥረት አደረጉ። ከስራቸው የሚያገኙት ገቢ ምንም ያህል አነስተኛ ቢሆንም እንኳ ኩሩ ስብእናቸው፣ ያቅሙን ያህል ከመጣር የማይሰስተው ባህሪያቸው ወደ ስራ መራቸው። የአጎታቸው ውለታ ለመመለስና የተግባር ምስጋና ለማድረስ ይህን አደረጉ።

ስለዚህ አንተም ልክ እንደርሳቸው ጥንቁቅና ኩሩ ሁን። “ራስህን ባንገትህ ተሸከም።”

2. አላህ ለባሪያው በምድር ላይ የሚወድለትን የሕይወት ዓይነት የሚያብራራ አጋጣሚ ነው። ይኸውም አላህ ቢፈልግ ኖሮ ለነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) ገና ከሕይወታቸው መጀመሪያ ጀምሮ ኑሯቸውን ድሎታማ በማድረግ እንጀራ ፍለጋ ከመኳተን መታደግ ይችል ነበር። ግና ለሰው ልጅ መልካሙ ገንዘብ ለሕብረተሰቡ በሚሰጠው አገልግሎት ወይም በጥረቱ የሚያገኘው መሆኑን፣ ሳይሰራ እና ሳይለፋ፣ ለሚኖርበት ማሕበረሰብ ቅንጣት በጎ ነገር ሳያደርግ፣ ስራ ፈትቶና እጁን አጣጥፎ ተቀምጦ የሚያገኘው ገንዘብ ደግሞ መጥፎ መሆኑን በጥበቡ ሊያስተምረን ስለከጀለ ነው።

በመሆኑም ልክ እንደ ተወዳጁ ነብይ (ሰ.ዐ.ወ) ሐላል ስራዎችን ብቻ ሰርተህ ገንዘብ ለማግኘት ጉጉና ትጉ ሁን።

3. ዳዒ የኑሮ መሠረቱ ዳዕዋ ሲሆን፣ ወይም በሰዎች ስጦታና ምጽዋት ላይ ሲመሠረት ዳእዋው ክብደትና ግምት ያጣል።

يَا قَوْمِ لَا أَسْأَلُكُمْ عَلَيْهِ أَجْرًا إِنْ أَجْرِيَ إِلَّا عَلَى الَّذِي فَطَرَنِي أَفَلَا تَعْقِلُونَ

“ሕዝቦቼ ሆይ! በእርሱ (በማድረሴ) ላይ ምንዳን አልጠይቃችሁም። ምንዳዬ በዚህ በፈጠረኝ ላይ እንጂ በሌላ ላይ አይደለም። አታውቁምን?” (ሁድ 11፤51)

መልእክተኛው (ሰ.ዐ.ወ) የሰዎች ውለታ በአንገታቸው ዙሪያ ተጠምጥሞ ሐቅን ይሉኝታ ሳይዛቸው በድፍረት እንዳይናገሩ የሚያደርጋቸው አንድም አጋጣሚ በነብይነት ከመላካቸው በፊትም ሆነ በኋላ በሕይወታቸው ውስጥ እንዲኖር አላህ አልፈቀደም። ስለዚህም ለራስህ እና ለዳዕዋው ክብር ቀናኢ ሁን። ለምትሰጠው የዳዕዋ አገልግሎት ከሰዎች ምንዳም ሆነ ምስጋና አትሻ። የእስልምና ዳእዋ ልክ እንደ አንበሳ ኩሩና ቁጥብ፣ እንደ ዳመና ውሃ ንጹህ መሆኑን እወቅ።