መፀው

ከውክፔዲያ

መፀው ትርጉሙ አበባ ማለት ነው። መገኛው ግስ መፀወ ሆኖ አበበ፤ አበባ ያዘ ማለት ነው። አበባና ነፋስን ቀላቅሎ የያዘው ዘመነ መፀው ምስጢሩ መዓዛ መስጠት፣ እንቡጥና ፍሬ ማሳየት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ባሕረ ሐሳብ (የዘመን አቆጣጠር) መሠረት ሰኔ ፳፮ቀን የገባው ክረምት መስከረም ፳፭ ቀን አብቅቶ አዲሱ የአበባ ወቅት መፀው መስከረም ፳፮ ቀን ይጀመርና እስከ ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ድረስ ይከርማል።

በዚሁ ወርኅ ተራሮች አበቦችን በዛፎች ጫፍ ላይ ተክለው እንደ ሰንደቅ ዓላማ ሲያውለበልቡ ስናይ የሚሰማን ደስታ ከመጠን ያለፈ ነው። ብዙ ደራስያን ስለ አበቦች ተናግረዋል ዘምረዋል ጽፈዋል። ከደራስያኑ ተቀድመው ጠቢቡ ሰሎሞን ስለአበቦች ሲናገር «እነሆ ክረምት አለፈ ዝናሙም አልፎ ሔደ አበቦችም በምድር ላይ ተገለጡ የዜማም ጊዜ ደረሰ» ብሏል።

ዮሐንስ አድማሱ ደግሞ «የመፀው ነፋስ፣ የጥቅምት የኅዳር የትሣሥ አየር፤ አብራጃው ሲነፍስ፤ ይሰለቻል ወይ?» ይላል። በርግጥ አይሰለችም

እንደዚሁም የስድስተኛው ምዕት ዓመቱ ቅዱስ ያሬድ ደግሞ በድጓው እንደጻፈው፣ «ሐለፈ ክረምቱ፤ ጸገዩ ጽጌያት። (ክረምቱ አለፈ፤ አበቦችም ፈኩ።)» ብሎለታል


የወቅት ስም የመግቢያው ቀን የማለቂያው ቀን
መፀው (አበባ) መስከረም ፳፮ ታኅሣሥ ፳፭
በጋ ታኅሣሥ ፳፮ መጋቢት ፳፭
ፀደይ (በልግ) መጋቢት ፳፮ ሰኔ ፳፭
ክረምት ሰኔ ፳፮ መስከረም ፳፭

ምንጭ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]