ቡዳ

ከውክፔዲያ
ለቡዲስም መሥራች፣ ጎታማ ቡዳ ይዩ።

ቡዳ ማለት በዓይኑ በማየት ብቻ ሰዎች ላይ ጉዳት ሊያደርስ ይችላል ተብሎ የሚታመንበት መንፈስ ወይንም ሰው ነው። ይሄ አይነት እምነት በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኝ ሲሆን ለአነሳሱም ከዛር መንፈስ ጋር ተመሳሳይ አፈ-ታሪክ አለው።

የቡዳ አፈ-ታሪክ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የቡዳን አመጣጥ የሰውን ልጅ አጥኝው (አንትሮፖሎጅስት) ሬምኒክ መዝግቦት ይገኛል። እንደ አፈ ታሪኩ አገላለጽ፣ አዳም እና ሔዋን ከገነት ከተባረሩ በኋላ 30 ልጆች የነበሯቸው ሲሆን አንድ ቀን እግዚአብሔር ሔዋን ልጆቿን እንድታአየው ጠየቃት። እርሷ ግን በመፍራት 15ቶቹን እና ቆንጆ የሆኑትን ልጆቿን በዋሻ ደብቃ 15ቱን ብቻ ለእግዚአብሔር አሳዩ። እግዚአብሔርም በውሸቷና በአለመታዘዟ በማዘን ዋሻው ውስጥ ያሉት 15ቹ ልጆች የተረገሙና መጥፎ እንዲሆኑ ተራገመ። አንድ አንዶቹ ልጆች ግን እግዚአብሔርን ይቅርታ ጠየቁ። አምላክም በመራራት ገሚሶቹን ቀበሮጥንቸል ወዘተ አደረጋቸው። ገሚሶቹን ደግሞ ሰው እንደሆኑ ትቶ ግን የሰይጣን መልዕክተኛ እንደሆኑ እንዲቀጥሉ አደረገ። እኒህ እንግዲህ የቡዳ ሰዎች የቀደሙ ወላጆች ናቸው። ሬምኒክ የመዘገበው አፈ ታሪክ ሰፊ እምነት አይደለምና አብዛኞቹ ሰምተውት አያውቁም። በአንዳንድ ሥፍራ ብቻ የሚታመን ሊሆን ይችላል[1]

በመጽሐፍ ቅዱስ አስተያየት ስለዚህ ትምህርት አንዳችም አይገኝም። እንኳን «ዛር» ወይም «ቡዳ» የሚሉት ቃላት በመጽሐፍ ቅዱስ በፍጹም አይገኙም። ሆኖም የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ይህን ትንሽ ይመስላል። በመጽሐፈ ኩፋሌና ሌሎች መጻሕፍት መሠረት፣ የአዳምና የሕይዋን ልጅ ቃየል ወንድሙን አቤልን ከገደለው በኋለ ከእኅቱ ጋራ ተባረረ። የቃየል ልጆች በዘመናት ላይ እጅግ በደለኞች ሆኑ። የአዳምና ሕይዋን ሌላ ልጅ ሴት ግን ጻድቃን ልጆች ወለደ፤ የእግዚአብሔርም ልጆች ተባሉ። ሴት እራሱ ከሞተ በኋላ ልጆቹ አመጸኞች ሆኑ፣ የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ ንቀው ወደ ቃየል ልጆች ወረዱና ከነርሱ ጋር ተደባለቁ፤ አብረው ክፉ ልጆች (ናፊል) ወለዱ። እግዚአብሔር ማየ አይኅ ያመጣው ስለዚህ ነው ይባላል። ከሰው ልጆች ኖህና ቤተሠቡ ብቻ አመለጡ፤ ዳሩ ግን በጥፋት ውኃው የጠፉት ክፉ ሰዎች አስማተኞች ስለ ነበሩ፣ የኖህን ልጆች በፈተና ለማታለል እስከ ፍርድ ቀን ድረስ አጋንንት ሆነው እንዲቆዩ እግዚአብሔርን ለመኑት። እግዚአብሔርም በምኅረቱ እንግዲህ 10 ከመቶ (አንድ አሥረኛ) ያለ ሰውነቶች ክፉ መናፍስት ብቻ ሆነው የሚሰሙዋቸውን ሰነፎች ለማታለል እስከ ዕለተ ደይን ድረስ እንዲቆዩ ፈቀዳቸው። (ኩፋሌ 10፡3-7)

በቡዳ መበላት እና ለዚህ በሽታ መድሃኒት ነው ተብሎ የሚሰራበት ዘዴ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አንድ ሰው በፈራ ጊዜ፣ በደነገጠ ጊዜ በቡዳ የመበላት ዕድሉ ከፍተኛ ሆነ ተብሎ በዚሁ ነገር በሚያምኑ ሰዎች ይገለጻል። ቡዳ በሶስት አይነት መንገድ ሰውን ይበላል ተብሎ ይታመናል፣ ይሄውም ወደ ጅብነት በመቀየር፣ የአትክል ስር በመጠመዘዝ እና በቡዳ ዓይን በመመልከት ናቸው[2]

በዚሁ ባህል መሰረት አንድ ሰው በቡዳ ሲበላ በ4 አይነት መንገድ መድሃኒት ይፈለግለታል። አንደኛው ደብተራዎች ሲጸልዩለትና በጸበል ውሃ ሲረጩት ነው። ሁለተኛው ወደ ቃልቻ ቤት በመሄድ የቡዳውን መንፈስ በዛር መንፈስ በመተካት ነው። ሦስተኛው የኩበት ጭስ በማጨስ ሲሆን። አራተኛው ደግሞ በይውን ቡዳ ይዞ በማምጣት የጋለ መጥረቢያ ላይ ምራቁን እንዲተፋ በማድረግ ናቸው።

ማጣቀሻ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ http://www.lausanne.org/en/documents/all/nairobi-2000/187-ethiopian-case-study.html
  2. ^ http://www.lausanne.org/en/documents/all/nairobi-2000/187-ethiopian-case-study.html