እሽቢ-ኤራ

ከውክፔዲያ

እሽቢ-ኤራ ከ1900 እስከ 1872 ዓክልበ. ግድም ድረስ (ኡልትራ አጭር አቆጣጠር) የኢሲን ንጉሥና ከ1878 በኋላ የሱመር ንጉሥ ነበር።

ሱመር ነገሥታት ዝርዝር ላይ ለ፴፫ ዓመታት እንደ ገዛ ሲለን፣ ከ፳፱ ወይም ፴ የዓመት ስሞች ብቻ ለእርሱ ተገኝተዋል። ከነዚህም ውስጥ ለምሳሌ፦[1]

  • «ጊርታብ ከተማ የጠፋበት ዓመት» (1900 ዓክልበ.)
  • «የማርቱ ከተማ የጠፋበት ዓመት»(1896 ዓክልበ.)
  • «የኢሲን ከተማ ግድግዳ ያሠራበት ዓመት» (1893 ዓክልበ.)
  • «የኪማሽና የኤላም ሥራዊት የተሸነፉበት ዓመት (1889 ዓክልበ.)
  • «በብርቱ መሣሪያ ኤላማውያንን ከኡር ውስጥ ያባረራቸውበት ዓመት» (1878 ዓክልበ.)

በኡር ንጉሥ ኢቢ-ሲን ዘመን (1901-1879 ዓክልበ.) የዑር መንግሥት ኃይል እየወደቀ ነበር። ጠላቶቹ አሞራውያንና ኤላም ያስቸግሩት ጀመር። በዚያም ዓመት ታላቅ ረሃብ በመካከለኛ ምሥራቅ ጀመረ። ኢሽቢ-ኤራ አንድ አሞራዊ ሹም ከማሪ ሲሆን ኢቢ-ሲን የኒፑርና የኢሲን ገዥ አደረገው። በረሃብ ምክንያት እህል ለዑር ለመግዛት ኢቢ-ሲን ብዙ ብር ለኢሽቢ-ኤራ ሰጠው። ኢሽቢ-ኤራ ግን የኢሲን መንግሥት ነጻነት አዋጀ። ኤላማውያን ሲያስቸግሩ ኢሽቢ-ኤራና ኢቢ-ሲን ይዋጋቸው ነበር። በመጨረሻ በ1879 ዓክልበ. ግድም ኤላማውያን በንጉሣቸው ኪንዳቱ ሥር ዑርን አጠፉ። በሚከተለው ዓመት አሞራዊው እሽቢ-ኤራ ኤላማውያንን ከዑር አስወጣቸውና የሱመርና አካድ ላዕላይነት ያዘ።

ቀዳሚው
ኡር ንጉሥ ኢቢ-ሲን
ሱመር ንጉሥ
1878-1872 ዓክልበ. ግድም
ተከታይ
ሹ-ኢሊሹ
ቀዳሚው
የለም
ኢሲን ንጉሥ
1900-1872 ዓክልበ. ግድም
  1. ^ የእሽቢ-ኤራ ዓመት ስሞች