ኤላም

ከውክፔዲያ
የኤላም ግዛት (ቀይ)

ኤላም ጥንታዊ ሃገር ነበር። ዛሬ ደቡብ-ምዕራብ ፋርስ በሆነ አቅራቢያ ተገኘ። መነሻው በዋና ከተማው በሱስን (ሹሻን) እና በካሩን ወንዝ ሸለቆ ከታሪክ መዝገብ መጀመርያ ሲሆን እስከ 547 ክ.በ. ድረስ ቆየ። ከሱመር እና ከአካድ (የዛሬ ኢራቅ) ወደ ምስራቅ የሆነ አገር ነበር። የኤላም መንግሥት ለፋርስ ከወደቀ በኋላ ቢሆንም የኤላም ቋንቋ በፋርስ አሐይመንድ መንግሥት በመደብኝነት ቆይቶ ነበር። ይህ ቋንቋ የፋርስኛ ዘመድ ሳይሆን ምናልባት ለደቡብ ሕንድ ድራቪዲያን ቋንቋዎች የተዛመደ ይሆናል።

እስከ ዛሬም ድረስ በፋርስ አገር ውስጥ ኢላም ክፍላገር ከጥንታዊው አገር ተሰይሞ ይገኛል።

ኤላማውያን የራሳቸውን ሀገር ስም ሃልታምቲ ብለው ሰይመውት ሲሆን ለጎርቤቶቻቸው ለአካዳውያን «ኤላምቱ» በመባል ታወቁ። 'ኤላም' ማለት 'ደጋ' ሊሆን ይቻላል። ከዚህ በላይ በብሉይ ኪዳን (ዕብራይስጥ መጽሐፍ ቅዱስ) አገሩ 'ኤላም' ተብሏል፤ ስሙም ከኖኅ ልጅ ሴም ልጅ ኤላም ነው።

ታሪክ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የኤላም ጥንታዊ ዘመን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የኤላም መጀመርያ ከተማ ሱስን ወይም ሹሻን ነበር። አንዳንዴም የሱመር አለቆች ወርረው አገሩን ይገዙ ነበር። በሱመር ነገሥታት መዝገብ ዘንድ የኪሽ ንጉሥ ኤንመባራገሲ (2384 ዓክልበ. ግድም) እንዲሁም የላጋሽ ንጉሥ ኤአናቱም (2200 ዓክልበ.) እና የአዳብ ንጉሥ ሉጋል-አኔ-ሙንዱ (2150 ዓክልበ.) ኤላምን አሸነፉት። በሌሎች ጊዜያት ኤላማውያንም ከተሞች ለምሳሌ የሐማዚ ወይም የአዋን (አቫን) ነገስታት በፈንታቸው ሱመርን ይገዙ ነበር። በአዋን ነገሥታት ዘመን የአካድ ንጉሥ ታላቁ ሳርጎን ኤላምን አሸንፎ (2075 ዓክልበ.) ከመግዛቱ በላይ በኤላም ውስጥ አካድኛን ይፋዊ ቋንቋ አደረገበት። ሆኖም ከሻርካሊሻሪ ዘመን በኋላ በ2013 ዓክልበ ግድም የአካድ መንግሥት በጉታውያን ወረራ ተሰብሮ ኤላም እንደገና ነጻ ወጣና አካድኛን ተወ። የሹሻን አገረ ገዥ የሆነ ኩቲክ-ኢንሹሺናክ ያንጊዜ የአዋን ንጉሥ ሆነና አዲስ ኤላማዊ ጽሕፈት አገባ። ኩቲክ-ኢንሹሺናክ አንሻንንና ሲማሽኪን ወደ ግዛቱ ጨመረ፤ እንኳን በ1986 ዓክልበ. ግድም እርሱ የአካድን ቅሬታ ያዘ። ነገር ግን በ1979 ዓክልበ. ግድም የኡር ንጉሥ ኡር-ናሙ አሸነፈውና የሲማሽኪ ሥርወ መንግሥት በኤላም ተነሣ።

በዚህ ወቅት ከመስጴጦምያ ጋር ሰላምና ጦርነት ተፈራረቀና እንኳን ገደማ የኡር ንጉሥ ሹ-ሲን ሴት ልጁን ለአንሻን መስፍን በትዳር ሰጠ። ነገር ግን የሱመር ኃይል ደክሞ ይጀምርና በ1879 ዓክልበ. ግድም፤ በሺማሽኪ ንጉስ በኪንዳታ መሪነት ኤላማውያን ከሹሻን ሕዝብ ጋር ኡር ከተማን አጠፉና ንጉሣቸውን የሹ-ሲን ልጅ ኢቢ-ሲንን ማረኩት። ከዚህ በኋላ ግን የኢሲን ከተማ ንጉሶች ኤላማውያን ከኡር አስወጥተው እንደገና ሰርተውት ኤላማውያን የበዘበዙትን ጣኦታቸውን ናና አስመለሱ።

የጥንታዊ ኤላም የብር ዋንጫ

የሚከተለው መንግሥት 'ኤፓርቲ' ይባላል። ደግሞ ከነገስታት ማዕረግ 'ሱካልማህ' ይባላል። በ1858 ዓክልበ. ግድም የመሠረተው ንጉሥ 2 ኤፓርቲ ነበር። በዚህ ጊዜ ሹሻን በኤላም ስልጣን ብትሆንም የመስጴጦምያ ኃያላት እንደ ላርሳ ምንጊዜ ሊይዙት ሞከሩ። በ1745 ዓክልበ. ገደማ ከሹሻን ወደ ስሜን በሆነ ከተማ የነገሠ ሌላ ኤላማዊ ንጉሥ ኩዱር-ማቡግ ልጁን ዋራድ-ሲን በላርሳ ዙፋን ላይ አስቀመጠ። የዋራድ-ሲን ወንድም ሪም-ሲን ተከተለውና በብዛት መስጴጦምያን አሸነፈ።

በዚህ ወቅት በኤፓርቲ መንግሥት ታዋቂ ከሆኑ ነገሥታት መኃል፤ ሺሩክዱቅ የባቢሎንን ሥልጣን ለመቃወም ከሌሎች አገሮች ጋር ስምምነት አደረገ። ሲዌ-ፓላር-ቁፓክ የመስጴጦምያ ነገሥታት እንደ ማሪ ንጉስ ዝምሪ-ሊም እንዲሁም የባቢሎን ንጉስ ሃሙራቢ 'አባት' ብለው ይጠሩት ነበር። ኩዱር-ናሑንተ የአካድ መቅደሶች በዘበዘ። ነገር ግን የኤላም ተጽእኖ በመስጴጦምያ አልቆየም። በ1675 ዓክልበ. ገደማ ሃሙራቢ ኤላማውያን አስወጥቶ የላርሳ ንጉሥ ሪም-ሲን ገለበጠውና መስጴጦምያን በሙሉ ገዛ። ሃሙራቢ የዘፍጥረት 14 አምራፌል ሲሆን ዋራድ-ሲን ወይም ሪም-ሲን አርዮክ እንደ ነበር ቢታስብም ዛሬ ብዙ ሊቃውንት ይህን ሃሳብ አይቀብሉም። በዚህ ምዕራፍ የተጠቀሰው ኤላማዊ ንጉስ ኮሎዶጎምር (በግሪኩ 'ኮዶሎጎሞር') ግን እንኳን ትክክለኛ ኤላማዊ ስም ('ኩዱር-ላጋማር') እንዳለው ይመስላል፤ ላጋማር የአረመኔ እምነታቸው ጣኦት ስም ነበርና።

ካሳውያን በ1507 ዓክልበ. ገደማ ባቢሎንን ካሸነፉ በኋላ ታሪካዊ ምንጮች አይበዙምና ስለ ኤፓርቲ መንግሥት መጨረሻ ዘመን ብዙ አይታወቅም።

የኤላም መካከለኛው ዘመን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ከክርስቶስ በፊት ከ1500 ዓመት ጀምሮ በአንሻን ከተማ ዙርያ አዳዲስ ሥርወ መንግሥታት ተነሡ። የንገስታት ማዕረግ 'የአንሻንና የሱስን ንጉሥ' ተብሎ ነበር። መጀመርያው 1500-1400 የኪዲኑ ሥርወ መንግሥት ሲሆን የሚከተለው 1400-1210 የኢጊሃልኪ ሥርወ መንግሥት ነበር። ከኢጊሃልኪ 10 ነገሥታት አንዳንዱ ካሣዊት ልዕልትን ያገባ ነበር። በ1330 ክ.በ. ገደማ የካሳውያን ንጉስ 2 ኩሪጋልዙ ለጊዜው ኤላምን ወረረ። ከዚያም በ1240 ክ.በ. ገደማ ሌላ ካሳዊ ንጉስ 4 ካሽቲሊያሽ ከኤላም ጋር ሲዋግ አላከናወነም። የኤላም ንጉሥ ኪዲን-ሑትራን በ1232 ክ.በ. የካሳውያን ንጉሥ ኤንሊል-ናዲን-ሹሚ አሸንፎ በ1230 ክ.በ. ደግሞ የካሳውያን ንጉስ አዳድ-ሹማ-ኢዲና አሸነፈ።

የሚከተለው ሥርወ መንግሥት የሹትሩክ ነገሥታት 1210-1100 ያሕል ገዙ። 2ኛው የሹትሩክ ንጉስ ሹትሩክ-ናሑንተ በ1184 ክ.በ. ካሳውይያንን በባቢሎን ሲዋጋ የሃሙራቢ ሕገጋት የተጻፈበትን ድንጋይ ከመማረኩ በላይ የማርዱክና የማኒሽቱሹ ጣኦታትና የናራም-ሲን ሐውልት ወደ ሱስን ማረከባቸው። በ1166 ሹትሩክ-ናሑንተ ካሳውያንን በፍጹም ድል አደረጋቸው። ነገር ግን በ1130 ሱስን ለባቢሎን ንጉሥ ለ1 ናቡከደነጾር ወደቀና የኤላም ንጉሥ ሑተሉሽ-ኢንሹሺናክ ወደ አንሻን ሸሸ። ከሱ በኋላ የኤላም ታሪክ ለጥቂት መቶ ዘመን አይገኝም።

የኤላም አዲስ ዘመንና ፍጻሜ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ከዚህ ዘመን እስከ 800 ክ.በ. ድረስ ስለ ኤላም ብዙ አይታወቀም። ቢያንስ አንሻን የኤላም ከተማ ሆኖ ቀረ። ኤላም ከባቢሎን ጋር በአሦር ላይ ስምምነት ያደርግ ነበር። የባቢሎን ንጉሥ ማር-ቢቲ-አፕላ-ኡሹር (992-987) ከኤላም ትውልድ እንደ ነበር ይታመናል። ኤላማውያን ከባቢሎን ንጉሥ ከማርዱክ-በላሱ-ኢቅቢ ጋራ ጦርነት በአሦር ንጉስ በ5ኛ ሻምሺ-አዳድ (831-819) ላይ አደረጉ። በዚያን ጊዜ ገዳማ ከኤላም ወደ ስሜን የማዳይ (ሜዶን) ሕዝብ በስሜን ፋርስና ዘመዶቹ ፋርሳውያንኡርምያህ ሐይቅ ዙሪያ ተነሡ።

ንጉሥ ሑምባኒጋሽ (751-725) ከባቢሎን ንጉሥ ከመሮዳክ ባልዳን ጋራ በአሦር ንጉስ በ2ኛ ሳርጎን ላይ ስምምነት እንዳደረገ ይታወቃል። ከሱ የተከተለው ንጉሥ 2ኛ ሹትሩክ-ናሑንተ በ718ና በ716 ክ.በ. በሳርጎን ሠራዊት እጅ ድል ሆነ። የሳርጎን ልጅ ሰናክሬም መሮዳክ-ባላዳንን ገልብጦ የራሱን ልጅ አሹር-ናዲን-ሹሚ በባቢሎን ዙፋን ላይ በ708 ክ.በ. ንጉስ አደረገው።

ሹትሩክ-ናሑንተ በወንድሙ ሐሉሹ ተገድሎ ይህ ሐሉሻ አሹር-ናዲን-ሹሚንና ባቢሎን በ702 ክ.በ. ማረከው። ሐሉሻ ግን በኩትር-ናሑንተ እጅ ተገደለ። ኩትር-ናሑንተ ዙፋኑን ለቅቆ በኡ ፈንታ የነገሠ ሑማ-መናኑ እንደገና ከአሦር ጋር ተዋገ። ሰናክሬም ግን በ697 ክ.በ. ባቢሎንን አጠፋው። በሰናክሬም ልጅ በአስራዶን ዘመን አንድ ኤላማዊ አገረ ገዥ በደቡብ መስጴጦምያ አመፃ አድርጎ ወደ ኤላም ሸሽቶ የኤላም ንጉስ ግን ገደለው። የአስራዶን ልጅ አስናፈር በ661 ክ.በ. ሱስንን ድል አድርጎ ወረራት። በዚህ አመት ደግሞ እስኩታውያን ሜዶንን ስለወረሩ የፋርስ ነገዶች ከዚያ ወደ አንሻን ፈልሶ ንጉሳቸው ተይስፐስ ያንጊዜ አንሻንን ማረከው። ሆኖም ለጊዜው የኤላም ነገሥታት ማዕረግ 'የአንሻንና የሱስን ንጉስ' ተብሎ ቆየ።

ከዚያ በአሦር ውስጥ የብሄራዊ ጦርነት ጊዜ ስለተከተለ እንዲሁም በኤላም የብሔራዊ ጦርነት ዘመን ተነሣ። በመጨረሻ ግን አስናፈር በ648 ክ.በ. ኤላምን በሙሉ ሲያጠፋ እንኳን እርሻቸውን በጨው ዘራ።

ከዚያ በኋላ የኤላም ኅይል ደክሞ በብዙ ትንንሽ መንግሥታት ተከፋፈለ። በመጨረሻ የፋርሶች አሐይመኒድ ነገሥታት በ546 ክ.በ. ሱሳንን ያዙት።

የኤላም መንግሥት ቢጠፋም ተጽእኖው በፋርስ መንግሥት ቀረ። ኤላምኛ ከፋርስ ሶስት ይፋዊ ቋንቋዎች አንዱ ነበር። ኤላምኛ ደግሞ የሐዋርያት ሥራ 2:9 እንደሚመስክር በ1ኛ ክፍለ ዘመንጴንጤቆስጤ ከተሰሙት ልሳናት አንዱ ነበር።

የኤላም ቋንቋ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ኤላምኛ ለጎረቤቶቹ ለሰናዓርኛም ሆነ ለሕንዳዊ-አውሮፓዊ ቋንቋዎች ወይም ለሴማዊ ቋንቋዎች ቤተሰቦች የተዛመደ አልነበረም። በኋለኛ ዘመን የተጻፈበት ከአካድኛ ባለ-ማዕዘን (ኩኔይፎርም) ጽሕፈት በተለመደ ጽሕፈት ሲሆን ከሁሉ ጥንታዊ የሆኑት ሰነዶች ግን ከዚህ በተለየ ማሥመርያ ኤላማዊ ጽሕፈት ነው የተቀረጹት። ባለፈው አመት ውስጥ ለዚህም ተመሳሳይ ጽሕፈት በጂሮፍት ፋርስ ተገኝቷል[1]። ከዚህ በፊት ቅድመ-ኤላማዊ ጽሕፈት የሚባል የስዕል ጽሕፈት ነበረ። ይህ ግን ኤላምኛ ለመጻፍ መጠቀሙ እርግጠኛ አይደለም።

አንዳንድ የቋንቋ ሊቃውንት እንደሚያምኑ ኤላምኛ የዛሬው ደቡብ ሕንድ ድራቪዲያን ቋንቋዎች (ታሚል ተሉጉ ወዘተ.) ዘመድ ይሆናል። በተጨማሪ በዛሬ ፓኪስታን የተገኘው ጥንታዊ የሕንዶስ ወንዝ ሥልጣኔ የሃራፓ ስዕል ጽሕፈት ስለነበረው ከኤላም ጋር ግንኙነት ሊኖር ይችላል ቢሉ፥ እስከ ዛሬ ድረስ ግን ለዚህ ጽሕፈት መፍትሔ ወይም ትርጉም ስላልተገኘም አጠያያቂ ሆኖ ቀርቷል።