ጉታውያን

ከውክፔዲያ

ጉታውያንመስጴጦምያ በላይ ባሉት ተራሮች «ጉቲዩም»፣ «ጉቲ» ወይም «ቁቲ» በተባለ ሀገር የመጣ ሕዝብ ነበረ። በ2010 ዓክልበ. ገደማ የአካድ መንግሥት በወደቀበት ዘመን ወርረው የሱመር አለቆች ሆኑ።

ጉታውያን በመስጴጦምያ ጽሕፈቶች ዘንድ ኋላቀርና ሥልጣኔ የናቀ ሕዝብ ይመስላሉ። ከነገስታታቸው ስሞች በቀር፣ ስለ ቋንቋቸው ጸባይ አንዳችም ነገር ዛሬ አይታወቅም።

መጀመርያ በታሪክ መዝገብ የሚታዩ፣ ለአዳብ ንጉሥ ለሉጋል-አኔ-ሙንዱ መንግሥት (2130 ግ.) ግብር ከሚከፍሉ ሕዝቦች መካከል ሲዘረዝሩ ነው። በጽላት መዝገብ ዘንድ አገራቸው ከሹቡር ደቡብና ከኤላም ስሜን ይገኛል። በአካዳውያንም ዘመነ መንግሥት፣ ለንጉሥ ታላቁ ሳርጎን (2070 ግ.) ተገዥ ሁነው ከሉሉቢ ብሔር አጠገብ ነበሩ። ናራም-ሲን (2049-2030 ግ.) ደግሞ የጉቲዩም ንጉሥ ጉላዓን አሸንፎ አገሩን እንደ ያዘው በአንድ ሰነድ ይዘገባል።

በ2021 ዓክልበ. ግ. የአካድ ንጉሥ ሻርካሊሻሪ የጉቲዩምን ንጉሥ ሻርላግን ማረከው፤ በ2018 ግ. «ቀንበር (ግብር) በጉቲዩም አደረገበት» ይዘገባል። የአካድ መንግሥት ግን ከዚያ ድካም ለመሆን ሲጀምር፣ ጉታውያን በመስጴጦምያ ላይ ብዝበዛ ያድርጉ ነበር። ሠራዊት እንደ ደረሰባቸው ግን ሸሽተው ነበር። ከቤት ማለፍ ወይም እንኳን በእርሻ መግባት አስጊ ሁኔታ ስለ ሆነ፣ የመስጴጦምያ ምጣኔ ሀብት ተበላሸና ራብ ሆነ። በመጨረሻ፣ (2010 ግ.) ጉታውያን አካድን ወረሩና ገዙት። እንዲሁም የጉቲ ሠራዊት ኡሩክንና ኤላምን የዛኔ ወረሩ። የጉታውያን ንጉሥ ኤሪዱፒዚር እራሱን እንደ አካድ ነገስታት በማምሰል፣ ማዕረጉ 'የጉቲ ንጉሥና የ4 ሩቦች ንጉሥ' ተባለ። ጉታውያን በአገሩ ሁሉ የታሰሩት እንስሶች ከጉረኖአቸው ፈቱ። የጉታውያን ግዛት ለእርሻ ተግባርም ሆነ ለዜና መዋዕል ዝገባ ጥንቁቅ አልነበረም። በሱመራዊው ነገሥታት ዝርዝር በአንዳንድ ቅጂ 25 ዓመታት ብቻ እንደ ገዙ የሚለው አቆጣጠር ትክክል ይመስላል፤ በትንሽ ጊዜ ውስጥ አገሩ በጽኑ ረሃብ ተያዘ። የኤላም ንጉሥ ኩቲክ-ኢንሹሺናክ ከጉታውያን ዘመን በፊትና በኋላ ስለሚታወቅ ለ124 አመታት (እንደ ሌላ ቅጂ) ሊሆን አይችልም።

በ1985 ዓክልበ. ያሕል፣ የኡሩክ ንጉሥ ኡቱ-ኸጛል የጉታውያን ንጉሥ ቲሪጋንን እንዳሸነፈ ጉታውያንንም ከአገራቸው እንዳስወጣ ይባላል። ከዚህ በኋላ በ1974 ዓክልበ. የኡር ኡር-ናሙ ጉቲዩምን ዘረፈው። በ1742 ዓክልበ. የኤሽኑና ንጉሥ 2 ኢፒቅ-አዳድ የጉቲዩም ዋና ከተማ አራጳን ያዘ። በ1676፣ 1674ና 1669 ዓክልበ. የባቢሎን ንጉሥ ሃሙራቢ ጉቲዩምን እንደገና ድል አደረገው።

በኋለኛ ዘመን፣ በአሦር መንግሥት 'ጉቲ' የሚለው ስም ለሜዶን ይጠቅም ነበር። በፋርስም ንጉሥ ቂሮስ ዘመን፣ ታዋቂ አለቃ ጉባሩ 'የጉቲ አገረ ገዥ' ተባለ። በተራሮቹ የሚገኘው የዛሬው ኩርድ ሕዝብ ከጉቲዎቹ እንደ ተወለዱ የሚያምኑ ብዙ ናቸው።

ቀዳሚው
ኢሉሉ
ሱመር ነገሥታት
2010-1985 ዓክልበ. ግድም
ተከታይ
ኡቱ-ኸጛል