ሉጋል-ዛገ-ሲ

ከውክፔዲያ

ሉጋል-ዛገ-ሲ ከ2107 እስከ 2077 ዓክልበ. ግድም (ኡልትራ አጭር አቆጣጠር) በሱመርኡማ ከተማ-አገር ንጉሥ ነበረ። ከአካድ መንግሥት በፊት መጨረሻውኛው ሱመራዊ ገዢ ነበር። ኡሩክን ከያዘ በኋላ ዋና ከተማውን አድርጎት «የኡሩክ ንጉሥ» የሚለውን ስያሜ እንደ ማዕረጉ ወሰደ። በዘመኑ ላይ ሌሎቹን የሱመር ከተሞች ይዞ በመጨረሻ መላውን ሱመር በኡሩክ መንግሥት ሥር ሆነ።

በ2095 ዓክልበ. ግድም ሉጋል-ዛገ-ሲ የኡማ ታሪካዊ ጠላት የሆነውን ከተማ ላጋሽን ንጉሡንም ኡሩካጊናን ድል አደረገ። ከዚህ በላይ ኡርንና ላርሳን ወደ ግዛቱ ጨመረ። በ2085 ዓክልበ. ግድም የኪሽ ገዥና የሱመር ላዕላይ ንጉሥ የሆነውን ኡር-ዛባባን ገልብጦ ኪሽንና ኒፑርን ያዘ፣ ከዚህም ጋር የሱመርን ላዕላይነት አገኘው። በአንድ ሰነድ የሉጋል-ዛገሢ ግዛት «ከላይኛው ባህር ጀምሮ እስከ ታችኛው ባህር ድረስ» ተዘረጋ። ይህ ማለት ከሜዲቴራኔያን እስከ ፋርስ ወሽመት ድረስ ይሆናል በማለት የዛሬው ሊቃውንት ቢያስቡም፣ ከዚሁ መፎከር ባሻገር በሜድትራኔአን አካባቢ ብዙ ተጽእኖ በውኑ እንዳልነበረው ይገንዘባሉ።

ሱመራዊ ነገሥታት ዝርዝር ዘንድ፣ የኪሽ መንግሥት ከተሸነፈ በኋላ፣ የሱመር ላዕላይነት ወደ ኡሩክ ተዛውሮ ሉጋል-ዛገ-ሲ ለ25 (34) አመታት እንደ ነገሠ ይላል። ከእርሱ በኋላ ግን ላዕላይነቱ ለአካድ ንጉሥ ሳርጎን ተዛወረ።

አሁን ከዘመኑ ከተቀረጹት ሰነዶች ብዛት የተነሣ ዘመኑ በኡማ ለ30 ዓመታት እንደ ቆየ ለማለት እንችላለን። በ2077 ዓክልበ. ግድም 'ታላቁ ሳርጎን' የኡሩክን ግድግዳ ሰብሮ ሉጋል-ዛገ-ሲን ገለበጠው፣ ሉጋል-ዛገ-ሲም በአንገት ብረትና ሰንሰለት እስከ ኒፑር መቅደስ ድረስ ተመራ።

ቀዳሚው
ኪሽ ንጉሥ ኡር-ዛባባ
ሱመር (ኒፑር) አለቃ
2085-2077 ዓክልበ. ግድም
ተከታይ
አካድ ንጉሥ ሳርጎን
ቀዳሚው
ኢሌ
ኡማ / ኡሩክ ንጉሥ
2107-2077 ዓክልበ. ግድም