መለስ ዜናዊ

ከውክፔዲያ
መለስ ዜናዊ
የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር
ከነሐሴ ፲፯ ቀን ፲፱፻፹፯ ዓ.ም. እስከ ነሐሴ ፲፬ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም.
ፕሬዝዳንት ነጋሶ ጊዳዳ
መ/አለቃ ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ
ቀዳሚ ታምራት ላይኔ (ተግባራዊ)
ተከታይ ኃይለማሪያም ደሳለኝ
የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት
ከግንቦት ፳ ቀን ፲፱፻፹፫ ዓ.ም. እስከ ነሐሴ ፲፮ ቀን ፲፱፻፹፯ ዓ.ም.
ጠቅላይ ሚኒስትር ተስፋዬ ዲንካ
ታምራት ላይኔ
ቀዳሚ ተስፋዬ ገብረ ኪዳን (ተግባራዊ)
ተከታይ ነጋሶ ጊዳዳ
ሌላ ስም ለገሠ ዜናዊ አስረስ (የትውልድ)
የተወለዱት ግንቦት 1 ቀን 1947 ዓ.ም.
አድዋኢትዮጵያ
የሞቱት ነሐሴ 14 ቀን 2004 ዓ.ም.
ብረስልስቤልጅግ
የፖለቲካ ፓርቲ ሕወሐትኢህአዴግ
ባለቤት አዜብ መስፍን
ሀይማኖት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ክርስትና

መለሰ ዜናዊ (የትውልድ ስማቸው ለገሠ ዜናዊ አስረስ) (ሚያዝያ ፴ ቀን ፲፱፻፵፯ ዓ/ም - ነሐሴ ፲፬ ቀን ፳፻፬ ዓ/ም) የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሰው ነበሩ። በአድዋ ትግራይ የተወለዱ ሲሆን ከ፲፱፻፹፯ ዓ/ም አንስተው እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ በኢትዮጵያ የጠቅላይ ሚኒስትር ሥልጣን በከፍተኛው የአመራር ቦታ ላይ ነበሩ። የኢህአዴግና የሕውሓት ሊቀመንበር በመሆን ኢህአዴግ ስልጣን ላይ ከወጣ ጀምሮ ቆይተዋል።

አቶ መለስ ዜናዊ አባታቸው (አቶ ዜናዊ አስረስ ከጎዣም አገው ቤተሰባዊ ትስስር እንዳላቸው ይታመናል[1]) የትግራይ ተወላጅ ሲሆኑ፣ በእናታቸው በኩል ደግሞ ኤርትራዊ ናቸው።

መለስ በታወቀው ጀነራል ዊንጌት 2ኛ ደረጃ ተምህርት ቤት የተማሩና ከአጼ አህለስላሴ የኮከብ ተማሪዎች ሽልማት የተሸለሙ፣ ከዛም ወደ በረሃ ወርደው በታጋይነት ከመሰለፍቸው በፊት፤ የአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ ሜዲካል ፋክልቲ ተማሪ ነበሩ።  ትግርኛ፣አማርኛና፡ እንግሊዝኛ አቀላጥፈው መናገር ይችላሉ።

መለስ ዜናዊ ስልጣን ላይ በነበሩባቸው ጊዜያት ለሀገራቸው ኢትዮጵያ ባደረጓቸው አስተዋፅኦዎች የኢትዮጵያ ባለውለታ ናቸው ይባላሉ፡፡ ኢትዮጵያም እንደ እርሳቸው ያለ መሪ አግኝታ እንደማታውቅ በሰፊው ይነገራል፡፡

ወደ ስልጣን አመጣጥ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አቶ መለስ የሚመሩት ሕውሓት የኮሎኔል መንግስቱ ኅይለ ማርያምን አምባገነናዊ መንግስት በትጥቅ ትግል ሲታገሉ ከነበሩ ድርጅቶች አንዱ ነበር። አቶ መለስ የሕወሓት አመራር ኮሚቴ መሪ ሆነው በ1971 ተመረጡ፤ ቀጥሎም በ1975 የድርጅቱ ማእከላዊ ኮሚቴ ሊቀመንበር ሆኑ። የደርግ መንግሥት ከወደቀም ጀምሮ የሕወሓትና የኢህአዴግ ሊቀ-መንበርም ሆነው አገልግለዋል። ኢህአዴግ የአራቱ ፖለቲካ ፓርቲዎች ማለትም የኦሮሞ ህዝቦች ዲሞከራሲያዊ ድርጅት፣ የብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ፣ የህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ፣ የደቡብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ውህደት ነው። ወደ ስልጣን ሲመጡ በጊዜው ላቋቋሙት ጊዜያዊ መንግስት ፕረዚዳንት ሆነው ካገለገሉ በሗላ 1985 ለመጀመሪያ ጊዜ ጠቅላይ ሚንስትር ሆነው ተመረጡ። በጊዜው የፕረዚደንትነቱን ቦታ የተረከቡት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ናችው።

የሽግግር መንግስታቸው[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የአምባገነኑ የመንግስቱ ኃይለ ማርያም አስተዳደር እንደ ወደቀ አዲስ አበባን የተቆጣጠረው ኢአሓዴግ በሕዝብ ምርጫ ሳይሆን ብሔረሰቦችን መሰረት ባደረገ በጥቂት ግለሰቦች የሽግግር መንግሥቱ በመቋቋሙና በተለይም የአማራን ሕዝብ(የአማራን የፖለቲካ አስተሳሰብ) ያለው ፖርቲ ሳይወከል መቅረቱ አብዛኛውን ሕዝብና ምሁራንን በጣም አስቆጣ።

የኢህአዴግ ደጋፊዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በወቅቱ በአምባ ገነኑ ደርግ ስር ተጨቁኖ ለነበረው ድሃ ኢትዮጵያዊ የኢህአደግ ወደ ስልጣን መምጣት ሌላ አማራጭ ስላልነበር የኢሕአዴግን መንግስት ሕዝቡ ለመቀበል ስለ ተገደደ በጊዜው ኢህአዴግ ይህ ነው የተባለ ተቃውሞ አልገጠመውም። በአንጻሩ ከጅምሩ በትጥቅ ትግል ኢሕአዴግን ሲረዱ የነበሩ የአረብና የምዕራባውያን መንግስታት ከጎንህ አለን በማለት በሁለት እግሩ አንዲቆም አስችለውታል።

ይሁን እንጂ እያደር ሲመጣ የአቶ መለሰ ዚናዊ መንግስት የታገለለትን ዓላማ ስቶ ዲሞክራሲን በማፈን የነጻ ፕሬስ አፈና በማካሄድና የብአዊ መብት ረገጣ ስላበዛ ብዙ የምዕራባዊያን ድጋፍና ከማጣቱም በላይ የብዙ ሺ ኢትዮጵያዊያን ለስደት ዳርጎአል። ሆኖም ዓለም አቀፉን ሽብርተኛ ለመታገል በሚል ሽንገላ ሱማሌን በመውረሩ ምክንያት በጆርጅ ቡሽ የምትመራ አሜሪካ ቀንደኛና ዋነኛ የኢህአዴግ ደጋፊ ሆና ቀርታለች። ቀጣዩ የአሜሪካ መሪ ባራክ ኦባማም የአገራቸውን ጥቅም ለማስጠበቅ ካላቸው ፍላጎት አልቃይዳንና አልሸባብ የተባሉ የአክራሪ እስላም ቡድኖችን እየታገልኩ ነው ላለው ኢሕአዴግን ድጋፋቸውን ቀጥለዋል።

የኢህአዴግ ተቃዋሚዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

መለስ ዜናዊ ከአጼ ኃይለ ስላሴ ሽልማት እንደተቀበለ (1964 ዓ.ም.)

ምንም እንኳ በደርግ የግፍ አገዛዝ የተማረረው ኢትዮጵያዊ ሁሉ ኢህአዴግን ለመቀበልና አብሮ ለመስራት ወደ ኋላ ባይልም ውሎ ሲያድር ግን በኢህአዴግ የአገር ውስጥ ፖሊሲ መከፋቱ አልቀረም። የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ብሎ ራሱን የስየመው ቡድን ከኢህአዴግ ጋር በመቃቃሩ ራሱን ከፓርላማውና ከካቢኔው አግልሎ ወደ ትጥቅ ትግሉ ተመለሰ።

ጠ.ሚ. መለስ የኤርትራን የመገንጠል ጥያቄ ያለምንም ማንገራገር መፍቀዳቸው ብቻ ሳይሆን ሁሉም ብሔረሰብ እንዲገነጠል የሚያስችለውን አንቀጽ በሕገ መንግስታቸው በማካተታቸው በተለይ በምሁራን ዘንድ የከረረ ተቃውሞ አስነስቶባቸዋል። ሁሉም በክልሉ በቋንቋው ይማር የተሰኘው ፖሊሲያቸውም በብዙዎች ዘንድ ጥርጣሬና መከፋፈልን በመፍጠሩ በሀገርና ከሀገር ውጭ በተደጋጋሚ የተቃውሞ ሰልፎች ተካሂዶባቸዋል።

በ1997 ዓ.ም. አጋማሽ ጠቅላላ ምርጫ ሲደረግ ከተለያዩ የፖለቲካ ህቡዕ ፓርቲዎች የተውጣጣ ቅንጅት የተሰኘ ጥምር የፖለቲካ ፓርቲ እንደ አንድ የፖለቲካ ድርጅት ተወዳደረ። በውጤቱም የዓለም ታዛቢዎች በተገኙበት በአዲስ አበባ ከተማ ከመቶ 97 እጁ መራጭ የተቃዋሚውን ፓርቲ ቅንጅትን መረጠ። በውጤቱ የተደናገጠው የአቶ መለስ መንግስት ለመጀመሪያ ጊዜ የአዲስ አበባን ፖሊስ በፌዴራል ቁጥጥር ስር አዞረ። የአዲስ አበባ ምክር ቤትንም በኦሮሚያ መስተዳደር ስር እንዲተዳደር አዲስ ድንጋጌ አወጣ።

ይሁን እንጂ ብዙም ገለልተኛ ታዛቢ በሌለበት ከአዲስ አበባ ውጪ ኢሕአዴግ 90 በመቶ ማሸነፉ ስለታወጀ ተቃዋሚዎች አድልዎ ተደርጎብናልና ምርጫው እንደገና ይጣራ ብለው ለከፍተኛ ፍርድ ቤት የክስ ማመልከቻ በማስገባታቸው ማጣሪያ ተካሄደ። ተቃዎሚዎች በጠቅላላው የምርጫ ውጤት ባለመስማማታቸው ያሸነፉበትን የፓርላማ ወንበር ባለመቀበል የገዢው ፓርቲ በበላይነት ከተቆጣጠረው ፓርላማ ራሳቸውን አገለሉ።

ሚሥስ አና ጎሜዝ የተባሉ የአውሮፓ ታዛቢ ቡድን መሪ ምርጫው አድልዎና ጫና እንደነበረበት ለዓለም ሕዝብ ምስክርነታቸውን ተናገሩ። አብዛኛዎቹ ታዛቢዎች (አፍሪካ ሕብረት አና የጂሚ ካርተርማእከል) ምርጫው በኢትዮጲያ ከተካሄዱ ምርጫዎች በጣም የተሻለ መሆኑን መሰከሩ። በሺ የሚቆጠሩ የቅንጅት ደጋፊዎች በዋና ዋና ከተማዎች በመውጣት ሰላማዊ ሰልፍ በቁጣ በሚገልጹበት ጊዜ ቁጥሩ በርካታ የሆነ ሕዝብ በፖሊስ በቀጥታ በተተኮሰ ጥይት ሕይወቱን አጥቶአል። የአቶ መለስ መንግስት አብዛኛዎችን በህዝብ የተመረጡ የቅንጅት ፓርቲ አባላትንና በሺህ የሚቆጠሩ አባላትን ባገር ክህደት አና መንግስትን ለመገልበጥ በመሞከር ከሰሳቸው። ሁለት ዓመት በፈጀ የፍርድ ሂደትም ፍርድ ቤቱ የቅንጅት መሪዎችን አገርን በመክዳት ወንጀል ጥፋተኛ ሆነው አገኛቸው። ይሁን እንጂ ሁሉም የ ቅንጅት መሪዎችና አብዛኛው ደጋፊ አባላት ጥፋታቸውን አምነው ይቅርታ በመጠየቃቸው ከእስር ነጻ ወጡ።

  1. ^ http://ethiopiazare.com/the-news-50/the-news/289-meles-father