ሶቅራጠስ

ከውክፔዲያ
የሶቅራጠስ ምስል በሮሜ ሰወች ከግሪኩ እንደተቀዳ፣ ለቨር ቤተ መዘክርፈረንሳይ

ሶቅራጠስ (470 ዓ.ዓ. - 399 ዓ.ዓ.) የነበረ ዋና የጥንት ግሪክ ፈላስፋ እና አስተማሪ እንዲሁም የምዕራቡ አለም ፍልስፍና መስራች ነበር። ሶቅራጥስ በግሪክ ዋና ከተማ አቴንስ ይኖር ነበር። የሶቅራጥስ ጥናት የሰው ልጆች እንዴት ያስባሉ? በሚለው ጥያቄ ላይ ያጠነጠነ ነበር። በሌላ ጎን የሶቅራጠስ ዘዴ የሚባለውን አይነት የምርምር መንገድ በመፍጠሩም ይጠቀሳል። ማለት ከአንድ ጥያቄ ተነሰቶ ወደ ጠለቅ ያለ ጥያቄ በመሻገር ነገሮችን ከስረ መሰረታቸው ለመረዳት መሞከሪያ ዘዴ ሲሆን በዘመኑ እንግዳና የራሱ የፈላስፋው ዋና ፈጠራ ነበር።

አንድ ሰው እንዴት ሰናይ (ጥሩ) ሊባል ይቻላል በሚለው ጥያቄም ዙሪያ አስተዋጽዖ በማድረግ የሥነ ምግባር መስራችም ነው። የሶቅራጠስ አስተሳሰብ ዘዴወች ለምዕራቡ አለም ማደግ ባደረጉት አስተዋጽዖ እንዲሁም በፕላቶ እና አሪስጣጣሊስ ሰርጾ የምዕራቡን አለም አስተሳሰብ በመቀየራቸው፣ በአሁኑ ዘመን ይሄ ፈላስፋ የምዕራቡ አለም ፍልስፍና አባት በመባል ይታወቃል።

የህይወት ታሪክ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሶቅራጠስ በዘመኑ ምንም አልጻፈም፣ ስለሆነም የህይወት ታሪኩ ብዙ አይታወቅም። ይልቁኑ የርሱ ተማሪወች የነበሩት ፕላቶ እና ዜኖፎን ስለርሱ በመመዝገባቸው አንድ አንድ ነገሮችን ለማወቅ ተችሏል። ፕላቶ በተለይ አስተማሪው ያደረጋቸውን ዋና ዋና ቃለ ምልልሶች በመመዝገቡ የሶቅራጥስ አስተሳሰቦች ከሞላ ጎደል ለቀሪው ትውልድ ተላልፈዋል።

ሶቅራጠስን ይጠላ የነበረው የዚያው ዘመን ተውኔት ደራሲ አሪስቶፋነስ በበኩሉ ስለሶቅራጠስ ጉሞቹ የተሰኘ ተውኔት ጽፎ ነበር። በዚህ ተውኔቱ ፈላስፋው እብድ እና የሰወችን ገንዘብ ሆን ብሎ የሚዘርፍ አጭበርባሪ አድርጎ አቅርቦታል። ፕላቶ በበኩሉ አስተማሪው በነጻ ያስተምር እንደንበር ሳይዘግብ አላለፈም።

እንደ ፕላቶ ዘገባ፣ የሶቅራጠስ እናት ፌናርት የተሰኘች አዋላጅ ነበረች። ሶቅራጠስ እናቱ ሴቶች ልጅ እንዲወልዱ እንደምትረዳ ሁሉ እርሱ ደግሞ ሰዎች አዳዲስ አሳቦችን እንዲወልዱ ለመርዳት እንደሚሞክር መናገሩ ይጠቀሳል። የሶቅራጠስ አባት ድንጋይ አናጢ የነበረው ሶፍሮኒስከስ እንደነበር ይጠቀሳል። ሶቅራጠስ በዘመኑ ድሃ የነበረ ሲሆን ለዚህ ምክንያቱ ከገንዘብ ይልቅ እውቀት ይበልጣል ብሎ ስለሚያምን ነበር። ሶቅራጠስ ስራ እንደማይሰራና በፍልስፍና ሃሳብና ክርክር ጊዜውን እንደሚያሳልፍ ፕላቶ ዘግቦት ይገኛል። ዛንቲፕ የተሰኘች ከርሱ በዕድሜ በጣም የምታንስ ሴትን አግብቶ ሶስት ልጆች እንደነበሩት ፕላቶ ጽፏል።

ሶቅራጠስ ብዙ ጊዜ ወደ ገበያ በመውጣት ውይይት መክፈት ደስታው ነበር። ብዙ ሰወች ስለሚናገረው ነገር ለመስማት ይጓጉ ነበር። ከነዚህ ሰወች መካከል ጥቂት የማይባሉት የራሱ ተማሪወች ሲሆኑ በሚሄድበት ሁሉ እየተከተክሉ ከሚያስተምረው ለመረዳት ይሞክሩ ነበር። እርሱም ሆን ብሎ ከባድ ጥያቄወችን በመጠየቅ ምንም እንደማያውቁ ለማሳየት ይጥር ነበር። ስለሆነም ብዙ ሰወች በሚጓጉት ልክ ይናደዱበት ነበር።

ማነው ጠቢቡ?[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሶቅራጠስ ይኖርበት የነበረው ዘመን የአቴናኃይል እየተዳከመ በስፓርታ ሊጠቃና ሊወድቅ ባለበት ነበር። ስለሆነም ሶቅራጠስ የአቴናን ውድቀት ለማቆም አቴናን እንደተናዳፊ ዝንብ ያጠቃ ነበር።

በዚህ መካከል ነበር የሶቅራጠስ ጓደኛ የሆነው ቼረፎንደልፊውን ጠንቋይ እንዲህ ሲል የጠየቀው፡ "ከሰወች ልጆች ሁሉ በጥበቡ ከሶቅራጥስ የሚበልጥ አለን?" ፣ የጠንቋዩም መል "ማንም ከርሱ የሚበልጥ የለም" የሚል ነበር። ይህ መልስ ለሶቅራጠስ እንቆቅልሽ ነበር፣ ምክንያቱም ሶቅራጠስ በራሱ ምንም ጥበብ እንደሌለው ያምን ነበርና። ስለሆነም የዕንቆቅልሹን ፍቺ ለማግኘት በአቴናውያን ዘንድ አዋቂ ናቸው ሚባሉ ግለሰቦችን፣ ገጣሚወችን፣ ኪነ ጥበበኞችን፣ መሪወችን እየሄደ ጥያቄ መጠየቅ ጀመረ። ከዚህ ተመክሮው እኒህ በህዝቡ ዘንድ አዋቂ የተባሉ ሰወች ምንም እንኳ ለራሳቸው ብዙ የሚያውቁና እና ጠቢብ የሆኑ ቢመስላቸውም ሲመረመሩ ግን እምብዛም የማያውቁና ጥበብ የጎደላቸው መሆኑን አረጋገጠ።

ስለሆነም ሶቅራጠስ የጠንቋዩን እንቆቅልሽ እንደፈታ አመነ። በእርሱ አስተያየት ህዝቡ አዋቂ ናቸው የሚላቸው ሰወች ምንም እንኳ ለራሳቸው አዋቂ የሆኑ ቢመስላቸውም፣ ሲፈተኑ ግን አላዋቂ ናቸው። በዚህ ትይዩ ሶቅራጠስ አላዋቂ እና ጥበብም የጎደለው መሆኑን እራሱ ስለሚያውቅ በዚህች ምክንያት እርሱ ከሌሎቹ የተሻለ ሆኖ ተገኘ።

በሌላ አነጋገር አለማወቁን ማወቁ ከሌሎቹ በተሻለ ጠቢብ አደረገው። ይህ እንግዴህ የሶቅራጥስ እንቆቅልሽ ተብሎ የሚታወቀው ነው። በአቴናውያዊን ባለስልጣናት ዘንድ ጥላቻ ያስነሳበት ይሄው ጉዳይ ነበር።

የሶቅራጠስ ሞት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የሶቅራጠስ ሞት (1787)

ሶቅራጠስ 70 ዓመት በሞላው ጊዜ የአቴና መንግስት እንዲያዝና ለፍርድ እንዲቀርብ አደረገ። በወቅቱ ሁለት ክሶች ሲቀርቡበት አንደኛው "በትምህርትህ ወጣቱን አበላሽተሃል" የሚል ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ "ለግሪክ ጣዖታት አልተገዛህም" የሚል ነበር። እንደ ፕላቶ ዘገባ ግን ሶቅራጠስ የግሪክ ጣኦታት አምላኪ ነበር። በአንድ አንድ ተመራማርወች ዘንድ የአቴንስ መንግስት ያቀረባቸው ክሶች በውሸት ላይ የተመሰረቱ ናቸው። የሆኖ ሆኖ፣ ክሪቶ የተሰኘው የፈላስፋው ጓደኛ ለጠባቂወቹ ጉቦ በመስጠት እንዲያመልጥ ሁኔታውን አመቻችቶ ነበር። ሶቅራጠስ ግን እምቢ በማለት ቀረ እንጂ አላመለጠም።

ሶቅራጠስ ለፍርድ በቀረበ ጊዜ ሰፊ የሆነ የመከላከያ ክርክር በማቅረብ የአቴናን መንግስት ክስ ውድቅ ለማደርግ ሞክሯል። ከዚህ በኋላ ዳኞቹ ምን አይነት ቅጣት እንዲበይኑበት እንደሚፈልግ ሲጠይቁት፣ ለአቴና ህብረተሰብ ካበረከተው ጥሩ ተግባራቱ አንጻር በቀሪው ዘመኑ ሁሉ ነጻ እራት እንዲያመጡለት ተናገረ። ነገር ግን ፍርድ ቤቱ ወይ በቅጣት እንዲለቀቅ ወይንም ደግሞ እንዲገደል የእጅ ምርጫ አደረገ። ውጤቱም ሶቅራጠስ እንዲገደል የሚል ሆነ።

ይሁንና ሶቅራጠስ ሞትን አይፈራም ነበር። ሞቱን ለማስቀረት ይቅርታም ሆነ ሌላ ማባበያ አላቀረበም። በርሱ ሥነ ምግባር መሰረት ላመነበት ነገር እስከመጨረሻ መቆሙ ሰናይ ድርጊት ነበር። ስለሆነም ሄምሎክ የተሰኘ መርዝ ጠጥቶ እንዲሞት ስለታዘዘ፣ መርዙን በመጠጣት አለፈ።

የሶቅራጠስ ሃሳቦች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሶቅራጠስ የሰወችን ስህተት ለማሳየት ወደ ኋላ አይልም ነበር። እራሱም እንደማያውቅ ያስተምር ነበር። አለማወቄን አውቃለሁ የሚለው ጥቅስ ከዚህ ፈላስፋ ይመነጫል። ስለሆነም ሶቅራጠስ የዕውቀቱን ድንበር እና ልክ ያውቅ ነበር።

ከስነ ምግባር አንጻር ሶቅራጠስ ያምን የነበረው የሰው ልጆች ዕኩይ ተግባር የሚፈጽሙት የተሻለ ነበር ስለማያውቁ ነው።

ሶቅራጠስ እንደሚለው "ያልተመረመረ ህይወት ምንም ዋጋ የሌለው ህይወት ነው"። ማለቱ እያንዳንዱ ሰው ስለራሱ ህይወት አላማና ተግባር እንዲመረምር መልካም ነው የሚል ነው።

ብዙው ሰው የሚያየውን ነገር ከልብ እንደማይመለከት/እንደማይገነዘብ ያምን ነበር።

በተረፈ ሶቅራጠስ ስለ ህይወት ትርጉም እና ስለሰናይ ተግባራት ብዙ ጥይቄወችን በማቅረቡ ይጠቀሳል። እኒህ ጥያቄወች እስከ አሁኑ ዘመን የፍልስፍና ዋና ጥያቄና አነሳሽ ሃሳቦች ናቸው።

ከሶቅራጠስ በፊት ፍላስፍና ማለት የሂሳብ ጥያቄወችን ለመመለስ የሚጥርና ስለ ተፈጥሮ አለም ጥያቄወችን የሚያቀርብ ነበር። እርሱ ግን ሥነ እውቀትን ፣ ሥነ ምግባርንና ፖለቲካን በመመርመር የፍልስፋናን አድማስ በጣም አስፍቶታል። ስለሆነም የምዕራቡ አለም ፈላስፋ በመባል ይታወቃል።