ደምሳቸው ፈንታ መንግስት
ጋዜጠኛ ደምሳቸው ፈንታ መንግስት / Demisachew Fenta Mengist በአማራ ክልል ምስራቅ ጎጃም ዞን አዋበል ወረዳ ወጀል በተባለች አነስተኛ ከተማ ከእናቱ ወ/ሮ እሰይነሽ ጫኔ እና ከአባቱ አቶ ፈንታ መንግስት ሚያዚያ 23 ቀን 1977 ዓ.ም ተወለደ። የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን የጀመረው በ1985 ዓ.ም በደብረ ማርቆስ ከተማ በሚገኘው ተክለሃይማኖት 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው። የ1ኛ እና 2ኛ ክፍል ትምህርቱን ተክለ ሃይማኖት ከተከታተለ በኋላ 3ኛ ክፍል ሲሆን ወጀል 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ገብቶ እስከ 8ኛ ክፍል ተማረ። በወቅቱ ማለትም በ1993 ዓ.ም በወጀል ከተማ የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ያልነበረ በመሆኑ ምክንያት 9ኛ እና 10ኛ ክፍልን ደጀን ከተማ በመሄድ "ጎጃም በር" አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተከታትሏል። 11ኛ እና 12ኛ /የመሰናዶ/ ትምህርቱን ደግሞ ቢቸና ከተማ "በላይ ዘለቀ" አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተምሯል። በወቅቱም ዩኒቨርሲቲ የሚያሰገባ ውጤት ማምጣት በመቻሉ በ1997 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተቀላቀለ።
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በ1999 ዓ.ም በትያትር አርትስ የመጀመሪያ ዲግሪውን ተቀብሏል። የዩኒቨርሲቲ ትምህርቱን ካጠናቀቀ በኋላ በአዋበል ወረዳ ማስታወቂያ ጽ/ቤት /በአሁኑ አጠራር "የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት"/ በፕሬስና ኢንፎርሜሽን ዴስክ ሃላፊነት ሠርቷል። በኋላም መንግስት በ2001 ዓ.ም ስራን መልሶ የማደራጀት /BPR/ ተግባር ሲያካሂድ በፕሬስ ዜናና ፕሮግራም የስራ ሂደት አስተባባሪነት ተመድቦ አገልግሏል።
ደምሳቸው መጋቢት 2001 ዓ.ም የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽንን በጋዜጠኝነት የተቀላቀለ ሲሆን ከጀማሪ እስከ ከከፍተኛ ሪፖርተርነት አገልግሏል። በአሁኑ ወቅትም በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን የትብብር ዝግጅቶች ዳይሬክተር የምርመራ በመሆን እየሰራ ይገኛል፡፡ በድርጅቱ ቆይታው፡-
- በአማራ ራዲዮ ከጀማሪ እስከ ከፍተኛ የፕሮግራም ሪፖርተር
- በበኩር ጋዜጣ የዜናና መጣጥፍ ከፍተኛ ሪፖርተር
- በአማራ ቴሌቪዥን ትህምርታዊ ፕሮግራሞች ከፍተኛ ሪፖርተር
- በአማራ ቴሌቪዥን የዶክመንታሪ ፕሮግራሞች ከፍተኛ ሪፖርተር
- በአማራ ራዲዮ፤ ኤፍኤም ባህርዳር፤ ደሴና ደብረ ብርሃን ዜና አቅራቢነት
- ከ2007 ዓ/ም ጀምሮ በአማራ ቴሌቪዥን በአዘጋጅነት (አርታዒነት)
- ከሀምሌ 2008 ዓ/ም እስከ መስከረም 30/2010 ዓ.ም የአማራ ቴሌቪዥን ምክትል ዋና አዘጋጅ (Deputy Editor-in-Chief)
- ከጥቅምት 1/2010 ዓ.ም እስከ ህዳር 30/2011 ዓ.ም የድርጅቱ የፕሮሞሽንና ገበያ ልማት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር እንዲሁም
- ከታህሳስ 1/2011 ዓ.ም እስከ አሁን ድረስ የአማራ ቴሌቪዥን ፕሮግራሞች ዋና አዘጋጅ
- ከጥቅምት/2013 እስከ መስከረም 2016 ዓ.ም ድረስ በአማራ ቴሌቪዥን የምርመራ ዘገባዎች አርታኢ/Editor
- ከጥቅምት 2016 ዓ.ም እስከ ሕዳር 2017 ዓ.ም የስትራቴጂክ ልማት ተወካይ ዳይሬክተር እንዲሁም
- ከሕዳር 2017 ዓ.ም ጀምሮ የትብብር ዝግጅቶች ዳይሬክተር ሆኖ እየሰራ ይገኛል፡፡
ኮርፖሬሽኑ በ2005 ዓ.ም አዲስ ያሰራውን የሚዲያ ኮምፕሌክስ ሲያስመርቅ በድርጅቱ የስራ ቆይታዉ ባሳየው የላቀ የስራ አፈጻጸም ከተሸለሙ የድርጅቱ ሰራተኞች አንዱ መሆን ችሏል። በዚህም ከምክትል ጠ/ሚንስትር ደመቀ መኮንን እጅ የምስጋና የምስክር ወረቀትና የማበረታቻ ሽልማት ተቀብሏል። በተጨማሪም የአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት በሰጠው ነፃ የትምህርት እድል አማካኝነት በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ በሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፍ 2ኛ ዲግሪውን አግኝቷል።
ደምሳቸው በ2002 ዓ.ም ከወ/ሮ ሙሉእመቤት መልኬ ጋር ትዳር የመሰረተ ሲሆን መባ የተባለች ሴት ልጅ በጥር 16/2005 ዓ.ም ፤ ሮቤል የተባለ ወንድ ልጅ በጥር 09/ 2008 ዓ.ም ፤ በነሃሴ 15/2012 ኪሩቤል የተባለ ወንድ ልጅ እንዲሁም ሰኔ 02/2015 ዓ.ም ዘዳዊት የተባለ ወንድ ልጅ ወልደዋል፡፡