ግዑዝነት

ከውክፔዲያ

ግዑዝነት ማለት ቁስ ነገሮች የሚገኙበት ፍጥነት እንዳይለወጥ የሚያደርጉት ተቃውሞ ነው። አካላት አርፈው ተቀምጠውም እንደሆነ ባሉበት እንዲሆኑ፣ በቀጥታ እየተጓዙም እንደሆነ፣ አቅጣጫቸውን ሳይቀይሩ ባሉበት ፍጥነት እንዲቀጥሉ ያላቸው ፍላጎት ወይም አዝማሚያ ግዑዝነታቸው ይባላል።

ግዑዝነት የቁሶች ወይንም ግዝፈት ያላቸው ነገሮች ሁሉ ዋና መገለጫ ባህሪ ነው።

የግዑዝነት ታሪክ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የግዑዝነት ጽንሰ ሐሳብ ከ፪ ሽህ ዘመናት መላምቶች፣ ክርክሮች እና ተሞክሮዎች በኋላ ተሻሽሎ የተደረጀ የሳይንስ ሐሳብ ነው። ግዑዝ አካላት፣ ለምሳሌ ድንጋዮች፣ በዘፈቀደ ከነበሩበት ተነስተው አይንቀሳቀሱም። ድንጋዮች የማሰብም ሆነ የመረዳት ችሎታ ሳኖራቸው ይህን መመሪያ አጥብቀው መከተላቸው ለፈላስፎች እንግዳ ነበር። የግዑዝነት ሐሳብ መደርጀት በቁሶች ላይ የሚታይን ይህን ክስተት አጥርቶ ለመገንዘብ ነበር።

የአሪስጣጣሊስ መርሆዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ከሁለት ሽህ አመታት በፊት የነበረው ዝነኛው ፈላስፋ አሪስጣጣሊስ ስለ ቁሳዊ እንቅስቃሴ ሁለት መርሆችን አስቀምጦ ነበር። አንደኛው መርህ፡ አንድ ቁስ ከርሱ ውጭ የሆነ ኃይል ካልአረፈበት በስተቀር፣ አርፎ ይቀመጣል። ሁለተኛው መርህ ደግሞ፡ የሚንቀሳቀስ ቁስ፣ በእንቅስቃሴው እንዲቀጥል የማያቋርጥ የኃይል ጫና ሊያርፍበት ያስፈልጋል ምክንያቱም የኃይል ጫናው ሲቋረጥ፣ በስተወዲያው እንቅስቃሴውም ስለሚያቆም።

በምሳሌ ለማየት፦ አንድ ድንጋይ ምንም ነገር ካልነካው ባለበት ተቀምጦ ይገኛል። ይህን ድንጋይ ወደ ሌላ ቦታ ለማሻገር ከተፈለገ፣ ጉልበት በላዩ ላይ ሊያርፍ ግድ ይላል። ለምሳሌ፦ አንድ ሰው ድንጋዩን አንስቶ ሲወረውረው።

አሪስጣጣሊስ ጉዳዩን ከመሪ ሃሳቦቹ አንጻር ሲመረምር እንግዳ ነገር አገኘ። በመርህ ሁለት መሰረት፣ አንድን ድንጋይ ለማንቀሳቀስ እና በእንቅስቃሴው እንዲቀጥል ለማድረግ ምንጊዜም ጉልበት አስፈላጊ ነው። ነገር ግን ድንጋይ ሲዎረዎር ፣ እጅ ውስጥ የሚገኘው ለትንሽ ሰኮንዶች ነው። እጅ ገፍቶ ከለቀቀው በኋላ፣ ከድንጋዩ ጋር አብሮ እየበረረ የሚገፋ ምንም ሰውም ሆነ ጉልበት የለም። ስለዚህ በመርህ አንድ መሰረት «ለምን ድንጋዩ ከእጅ ሲዎጣ ወዲያው አይቆምም?» በሌላ አነጋገር «ለምን ድንጋዩ ያለምንም ገፊ-ኃይል እየበረረ ይሄዳል?»

ለዚህ እንቆቅልሽ አሪስጣጣሊስ የሰጠው መልስ ከባቢውን አየር ያመካኘ ነበር። ድንጋዩ ከተወረወረ በኋላ በጉዞው እንዲቀጥል የሚገፋው ጉልበት ከከባቢው አየር ያገኛል። ስለሆነም፣ ከባቢ አየር በሌለበት ኦና ውስጥ ድንጋዩ ቢዎረወር ኖሮ መንቀሳቀሱን በስተወዲያው ያቆም ነበር።

የፈላስፋው ሃሳቦች ለሁለት ሽህ ዓመታት በብዙዎች ተሰሚነት ኖሯቸው እንደ ዶግማ አገለገሉ። አልፎ አልፎ ትችቶችና ተቃውሞዎች ቢነሱም፣ ለዚህ ሰው ከነበራቸው ክብር እና አድናቆት የተነሳ ተጻራሪ ሐሳቦች አልተሰሙም ነበር።

ኤምፒተስ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በጠፈር ኦና ውስጥ የሚመላለሱትን ፈለኮች ያስተዋሉ ፈላስፎች ግን የከባቢ አየር ለእንቅስቃሴ አስፈላጊ እንዳልሆነ ተረዱ። ስለሆነም አንድ ድንጋይ እጅን ከለቀቀ በኋላ በጉዞው መቀጠሉ፣ ከአየር ግፊት ሳይሆን፣ ወርዋሪው ለድንጋዩ በሚያስተላልፈው አንዳች ነገር ነው አሉ። ይህን አንዳች ነገር፣ አንቀሳቃሽ ጉልበት ወይም በነሱ አጠራር ኤምፒተስ(impetus) ብለው ሰየሙት። «ታዲያ የተላለፈው ኤምፒተስ በድንጋዩ ውስጥ እስካለ ድረስ፣ ለምን ድንጋዩ እስከ ዘላለም እንዲበር አያደርግም?» ለሚለው ጥያቄ በ፮ኛው ክፍለ ዘመን የነበር ፈላሳፋ ፍሊጶነስ ዮሐንስ፣ « ኤምፒተሱ በተወሰነ ጊዜ በኖ የሚጠፋ ስለሆነ ነው» በማለት መላ ምት አቀረበ። ይህ የኤምፒተስ ጽንስ የአሪስጣጣሊስን ስህተት በከፊል የጠገነ ቢሆንም፣ የፈላስፋው ተከታዮች ግን አውግዘው አልተቀበሉትም ነበር።

የቦርዲያንና ተከታዮቹ ማሻሻያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ከስምንት መቶ ዓመታት በኋላ፣ በ 14ኛው ክፍለ ዘመን የነበረው ፈረንሳዊ ፈላስፋ ዥን ቦርዳን የኤምፒተስን ያለምንም ምክንያት ተኖ መጥፋት ባለመቀበል የተሻሻለ ሐሳብ አቀረበ።

ያንድ የተወረወረ ድንጋይ እንቅስቃሴ መቆርቆዝ መንስዔ የአየር ሰበቃ እና የመሬት ስበት ለቁሱ ከተሰጠ እንቅስቃሴ በተቃራኒ አቅጣጫ እንቅፋት ስለሆኑ ነው ብሎ አስረዳ። ይህም ከአሪስጣጣሊስ የአየር ግፊት መላምት ሙሉ በሙሉ ተቃራኒ ሐሳብ ነበር።

በቦርዳን አስተምሮ፣ አንድ ዲንጋይ በተወረወረ ጊዜ፣ ከወርዋሪው እጅ ኤምፒተስ ይቀበላል። ያን አንቀሳቃሽ ጉልበት ገንዘቡ አድርጎ እስከዘላለም ለመጓዝ በተሰጠው አቅጣጫ፡ ወደፊትም ከሆነ ወደ ፊት፣ ወደጎንም ሆነ ወደጎን፣ ወደላይ፣ ወደታች፣ እንዲሁም በክብ እሚያዞርም ከሆነ በክብ ለመሄድ ይፈልጋል። ሆኖም የአየር ሰበቃና የመሬት ስበት፣ በእንቅስቃሴው ተቃራኒ ስለሚቆሙ እና ስለሚያበላሹት፣ ኤምፒተሱ ተሟጦ እንዲያልቅ ያደርጋሉ። በዚህ ሁኔታ ድንጋዩ ለመሄድ የሚፈልግበትን አቅጣጫ ትቶ ያርፋል።

አዲሱ የቦርዲያን ሐሳብ በተለያዩ ፈላስፎች በተጨባጭ እየተፈተሸና በተሞክሮ እየተረጋገጠ መጣ። የአሪስጣጣሊስ ስህተቶችም ጎልተው መታየት ጀመሩ። ዘመኑ የለውጥ ዘመን ስለነበር ሌሎች የአውሮጳ ፈላስፎች በተራቸው የቦርዲያን ሐሳብ ግድፈት እንዳለው ማየታቸው አልቀረም። እንደ ቦርዲያን አስተሳሰብ፣ በጠፈር የሚሽከረከሩት ፈለኮች (ፕላኔቶች) ፣ ጸሓይን እየዞሩ የመንቀሳቀሳቸው ምክንያት አምላክ አለምን ሲፈጥር፣ ከመነሻው ኤምፒተስ ስለሰጣቸው ነው ብሎ ነበር። ኤምፒተስ ማለት አንቀሳቃሽ ጉልበት ነው። የጉልበት አንዱ ጸባይ ያረፈበትን ቁስ ፍጥነት መጨመር ነው። እንግዲህ በፈለኮቹ ውስጥ ያ ጉልበት ምንጊዜም ካለ፣ ፍጥነታቸው ያለማቋረጥ እየጨመረ መሄድ ነበረበት ምክንያቱም የአየር ሰበቃ በጠፈር ውስጥ ስለማይገኝ። በሃቅ የሚሆነው ግን፣ ከቦርዲያን ሀሳብ በተቃራኒ ፈለኮች የሚጓዙት ከፍ ዝቅ በማይል ውሱን ፍጥነት ነው።

ሌላው በቦርዲያን ሐሳብ ላይ የተነሳው ትችት፣ ኤምፒተስ ክባዊ ሊሆን ይችላል የሚለው የፈላስፋው አስተምሮ ነበር። ጂያምባኒታ ቤኔድቲ የተባለ የጣሊያን ምሁር ድንጋይ በወንጭፍ ሲዎረወር፣ ምንም እንኳ ወንጭፉ ድንጋዩን በክብ ምህዋር እያንቀሳቀሰ የክብ ኤምፒተስ ቢሰጠውም፣ ወንጭፉን ሲለቅ ግን የክብን ሳይሆን የቀጥተኛን አቅጣጫ ይይዛል። ከዚህ ተነስቶ፣ የቁስ ነገሮች የተፈጥሮ ፍላጎታቸው በቀጥተኛ መስመር መጓዝ ነው የሚል ድምዳሜ ላይ ደረሰ።

የአሪስጣጣሊያዊ ሐሳብ ማጠቃለያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የኤምፒተስ ጽንሰ ሐሳብ ከአሪስጣጣሊስ መነሻ ሐሳብ የተሻሻለ ቢሆንም በአጠቃላይ መልኩ በአሪስጣጣሊያዊ አስተሳሰብ ስር ይመደባል። ምክንያቱም ሁለቱም አስተሳሰቦች የሚመዘዙት «  የቁሶች ተፈጥሯዊ ፍላጎት በእረፍት (ዜሮ ፍጥነት) መገኘት ነው» ከሚል እምነት ስለነበር ነው። አሪስጣጣሊስ በምድር ላይ ያለው ከባቢ አየር ሰበቃ፣ የቁሶችን ተፈጥሯዊ ባህርይ ጋርዶ እንደደበቀው በጊዜው አያውቅም ነበር። ስለዚህ፣ ለነገሮች መንቀሳቀስ ምንጊዜም ጉልበት አስፈላጊ መስሎ ታየው። ይህ ስህተት በኢምፔተስ ጽንሰ ሐሳብ ሰርጾ በመገኘቱ፣ የሚቀጥለው ሳይንሳዊ አብዮት መከሰት ግድ አለ።

ግዑዝነት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በ፲፮ኛው እና ፲፯ኛው ክፍለ ዘመን አውሮጳ፣ እጅግ ከፍተኛ የሳይንስ ምርምር፣ ክርክር ፣ የሐሳቦች ሥርጭትና መታደስ የተካሄደበት አህጉር ነበር። የአሪስጣጣሊስም ጥንታዊ ሐሳቦች፣ በዘመኑ የለውጥ ንፋስ ሥራቸው እስኪነቀል ታድሰዋል። የግዑዝነት ጽንሰ ሐሳብም፣ መነሻው የአሪስጣጣሊስ እና ኤምፒተስ አስተሳስብ ቢሆንም፣ በዚሁ ዘመን በተነሱት ተማሪዎች ኬፕለርጋሊሊዮ እና ኒውተን ተራ በተራ ባስተካከሉት ሁኔታ በልዩና ጽኑዕ መሰረት ላይ ሊመሰረት በቅቷል።

የዚህ የአዲሱ ሐሳብ መነሻ፣ ቁስ አካላት ከፍ ዝቅ በማይል አንድ ፍጥነት እና አንድ ቀጥተኛ አቅጣጫ መጓዝ የተፈጥሮ ፍላጎታቸው ነው የሚል ነው። ማለትም በነገሮች ላይ የውጭ ጉልበት እስካለረፈ ድረስ፣ ፍላጎታቸው አርፎ መቆም ብቻ ሳይሆን፣ ሌላም ፍጥነት ካላቸው ከፍ ዝቅ ሳይል በዚያ ፍጥነት መቀጠል ነው። ይህ ግን ከለት ተለት ተሞክሮ የሚቃረን ይመስላል ምክንያቱም በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱ ነገሮች ከውጭ ጉልበት ካላገኙ ምንጊዜም ስለሚቆሙ። ለአሪስጣጣሊስ መሳሳትም ዋናው ምክንያት ይህ ነበር። በምድር ላይ የነገሮች ቆሞ መገኘት ምክንያት በተፈጥሮ ፍላጎታቸው ሳይሆን፣ በሰበቃ ጉልበት ተገደው ነው። ከምድር፣ ከአየር እና ከሌሎች ቁሶች ጋር በሚያደርጉት ፍትጊያ ምክንያት ቁሶች እንቅስቃሴያቸው ይሞታል። በኦና ውስጥ ቢሆኑ ኖሮ ያለማቋረጥ በተንቀሳቀሱ ነበር።

የኤምፒተስን አስተሳብ ግድፈቶች ለማረም የተቻለው በአዲሱ አመለካከት የቁሶችን እንቅስቃሴ በማየት ነበር። አዲሱ አመለካከት፣ ቁሶች ጉልበት ሳያርፍባቸው ሊንቀሳቀሱ መቻላቸው በውስጣቸው እንደክትባት በተወጉት እና በተላለፈላቸው ልዩ ጉልበት አይደለም። ይልቁኑ ቁሶች፣ በተፈጥሮአቸው፣ ያለምንም እርዳታ፣ በአሉበት ፍጥነት፣ በቀጥተኛ መንገድ ለመንቀሳቀስ ይፈልጋሉ። ይህ የቁሶች መሰረታዊ ባህርይ ግዑዝነታቸው (inertia) በመባል ተሰየመ። ስለዚህ ግዑዝነት ማለት፣ በዘመናዊ ትርጓሜው፣ « አንድ ቁስ አካል የያዘውን ፍጥነት እንዳይቀየር የሚያሳየው ተቃውሞ» ማለት ነው። ሓሳቡ እጅግ የተሳካ ስለነበር፣ እስካሁን ዘመን ድረስ ይሰራበታል።

ድንጋይ ውርወራ ከግዑዝነት ጽንሰ ሐሳብ አንጻር[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ከግዑዝነት ጽንሰ ሐሳብ አንጻር፣ አንድ ድንጋይ ነባራዊ ፍጥነቱን በጉልበት ካልተገደደ አይቀይርም። ለምሳሌ አርፎ ቁጭ ያለ ድንጋይ ፍጥነቱ ዜሮ ስለሆነ፣ ይህን ፍጥነት መልቀቅ አይፈልግም። ድንጋዩን ለማንቀሳቀስ ጉልበት ያስፈልጋል። በእጅ እየተገፋ፣ በጉልበት ተገዶ ድንጋዩ የተወሰነ ፍጥነት ላይ ይደርሳል። የድንጋዩ ግዑዝነት ለውጥን ምንጊዜም ስለሚቃወም ጉልበት አስፈለገ። ሆኖም አንድ ጊዜ፣ አዲስ ፍጥነት በእጅ ተገዶ ከያዘ በኋላ፣ ሲለቀቅ፣ አሁንም ይህን አዲሱን ፍጥነት እንዳይቀየር ግዑዝነቱ ግድ ይላል። ድንጋዩ፣ በራሱ ተፈጥሯዊ የግዑዝነት ባህርይ ምክንያት በያዘው ፍጥነት ለዘላለም መጓዝ ይጀምራል። ግን ደግሞ የአየር ሰበቃ በጉዞው ተቃራኒ የሆነ ጉልበት ያሳርፍበታል። ይህ ጉልበት፣ የድንጋዩን ግዑዛዊ ተቃውሞ ቀስ በቀስ በማሸነፍ ፍጥነቱን እንዲቀንስ ያደርጋል። ሰበቃው በጉልበት የድንጋዩን ፍጥነት ቀይሮ ዜሮ ሲያደርሰው፣ ድንጋዩ አዲሱን ፍጥነት በመያዝ አርፎ ይቀመጣል።

ሌሎች ምሳሌዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የመኪና ጎማዎችና የኤሌክትሪክ ጄኔረተሮች፣ የፈለኮች በፀሐይ ዙሪያ መዞር፣ ወዘተ በከፊል የግዑዝነታቸው ባህርይ ውጤት ናቸው። የፔንዱለም መዎዛዎዝ፣ ሩዋጮች ማብቂያ መስመራቸውን አልፈው መንደርደር፣ ኳስ ተጫዋቾች "ማጣጠፋቸው" ፣ እነዚህ ሁሉ የግዑዝነት ውጤት ናቸው። ባጠቃላይ መልኩ፣ ግዑዝነት የቁስ አካላት መገለጫ ባህርይ እንደመሆኑ፣ በአብዛኛው የገሃዱ ዓለም ክስተቶች ሠርጾ ይገኛል።