የኢትዮጵያ የባህል ሙዚቃ መሣሪያዎች
ኢትዮጵያ ውስጥ የተለያዩ የባህል ሙዚቃ መሣሪያዎች አሉ። እነዚህም መሣሪያዎች የጅማት፣ የትንፋሽና የምት ተብለው ወደ ሶስት ይከፈላሉ።
የክር ሙዚቃ መሣሪያዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]
እነዚህ መሣሪያዎች ድምጽ የሚሰጡት በንዝረት ነው።
- በገና፡ መንፈሳዊ ዜማዎችን ለማዜም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኝ የሙዚቃ መሣሪያ ነው።
- ክራር፡ ይህ የጅማት የሙዚቃ መሣሪያ ለአያሌ ዓመታት ለደስታ፣ ለትካዜ፣ ለፍቅርና ለቀረርቶ ስንጠቀምበት የቆየ መሣሪያ ነው።
- መሰንቆ (ማሲንቆ)፡ በተለይ በሰሜን ኢትዮጵያ የሚገኝ ጥንታዊ የሙዚቃ መሣሪያ ነው።
- ዲታ፡ በሲዳሞ የሚገኝ የጅማት መሣሪያ ነው።
- ዱል፡ በጋምቤላ የሚገኝ የጅማት መሣሪያ ነው።
የትንፋሽ ሙዚቃ መሣሪያዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]
እነዚህ መሣሪያዎች ድምጽ የሚሰጡት በትንፋሽ ኃይል ነው።
- ዋሽንት፡ አብዛኛውን ጊዜ እረኞች በሀገር ቤት ይገለገሉበታል። በተጨማሪም በመድረክ ላይ ለክራርና ለመሰንቆ ቅኝት በመስጠትና ዜማን በማጀብ ያገለግላል።
- አምቢልታ፡ ሶስት ዓይነት አመቢልታዎች አሉ። ስማቸውም ኡፍን፣ አውራ እና የማ ነው። በኢትዮጵያ ለክብረ በዓልና ወደ ጦር ሜዳ ለሚሄድ ሰልፈኛ የሚነፋ አድማቂ መሣሪያ ነው።
- መለከት፡ ቀደም ባለው ጊዜ ሰዎች ተሰብስበው የመንግሥት አዋጅ እንዲሰሙ ትዕዛዝን መስጫ መሣሪያ ሆኖ ሲያገለግል የቆየ ነው።
- ድንኬ፡ በሲዳሞ ክፍለ ሀገር በወላይታ አካባቢ ለአስከሬን ማጀቢያነት የሚያገለግል መሣሪያ ነው።
- ፖረሬሳ፡ በደቡብ ኢትዮጵያ ለዘፈን ማጀቢያ የሚያገለግል መሣሪያ ነው።
- ሁራ፡ በከፋ ክፍለ ሀገር ያሉ ጎሳዎች የሚጠቀሙበት የሙዚቃ መሣሪያ ነው።
- ሁልዱዱዋ፡ በሲዳሞ ክፍለ ሀገር የቀብር ሥነ ሥርዓት ለመግለጽ የሚነፋ መሣሪያ ነው።
- ጨቻ ዝዬ፡ በደቡብ ኢትዮጵያ ውዝዋዜ ለማድመቅ የሚያገለግል የሙዚቃ መሣሪያ ነው።
- ዛክ፡ በከፋ ክፍለ ሀገር የሚገኝ የሙዚቃ መሣሪያ ነው።
- ሸመቶ፡ በከፋ ክፍለ ሀገር የሚገኝ የሙዚቃ መሣሪያ ነው።
- ፋንፋ፡ በከፋ ክፍለ ሀገርና በጋሞጎፋ /ኮንሶ/ የሚገኝ የሙዚቃ መሣሪያ ነው።
- አዋዛ፡ በወለጋ ክፍለ ሀገር በአሶሳ አካባቢ የሚገኝ የሙዚቃ መሣሪያ ነው።
የምት ሙዚቃ መሣሪያዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]
- ከበሮ፡ ለዘፈን ማድመቂያና ለሠርግ እንዲሁም ለቤተ ክርስቲያን ዝማሬ ቀሳውስት በሽብሸባ ጊዜ የሚጠቀሙበት መሣሪያ ነው።
- አታሞ፡ ለሙዚቃና ለጭፈራ የሚያገለግል መሣሪያ ነው።
- ነጋሪት፡ በሰልፍ ጊዜ የሚጎሰም የሙዚቃ መሣሪያ ነው።
- መቋሚያ፡ ለመንፈሳዊ ዝማሬ ከከበሮው ስልት ጋር በተዛመደ ሁኔታ በመንቀሳቀስ ቀሳውስት የሚጠቀሙበት መሣሪያ ነው።
- ፀናፅል፡ ለመንፈሳዊ ዝማሬ ቀሳውስት የሚጠቀሙበት መሣሪያ ነው።
- ቅል፡ ቅል በውስጡ ጠጠሮች ወይም ፍሬዎች ተጨምረውበት ለዘፈን ማድመቂያ ያገለግላል።
- ቻንቻ፡ በጋሞጎፋ ክፍለ ሀገር በጭፈራ ጊዜ በወገብ ላይ የሚታሰር አዳማቂ መሣሪያ ነው።
- ካመባ፡ ከሸክላ የተሠራ በደቡብና በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ የሚገኝ መሣሪያ ነው።
- ቃጭል፡ አብዛኛውን ጊዜ ለመንፈሳዊ ዜማ የሚያገለግል መሣሪያ ነው።
- ቶሞ፡ በጋምቤላ ብሔረሰብ ውስጥ እውቅና ተወዳጅ የሆነ የሙዚቃ መሣሪያ ነው። በተጨማሪም በኬንያ፣ ኡጋንዳ፣ ታንዛኒያ፣ ናይጄሪያ፣ ሱዳንና ዛየርም በዚህ መሣሪያ እንደሚጠቀሙ ታውቋል።
- ጋሬ፡ በጋምቤላ ብሔረሰብ ውስጥ በእግር ላይ ታስሮ ጭፈራን የሚያደምቅ የሙዚቃ መሣሪያ ነው።
- የግመል ቃጭል፡ ይህ መሣሪያ በተለይ ከእንጨት የሚሠራ ሆኖ ሙዚቃን ለማጀብ የሚጠቅም መሣሪያ ነው።
ተዛማጅ መጣጥፎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]
ማጣቀሻ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]
- ናሽናል ቢብሊዮግራፊ ቡድን፣ የአንጋፋ አርቲስቶች መዝገበ የሕይወት ታሪክ፣ መጋቢት ፳፻፣ ገጽ 32-35 Archived ሴፕቴምበር 29, 2011 at the Wayback Machine