ሪፋት

ከውክፔዲያ

ሪፋት (ዕብራይስጥ: ריפת) በኦሪት ዘፍጥረት 10:3 መሠረት የጋሜር ያፌት ፪ኛ ልጅ ነበር። በ፩ ዜና መዋዕል 1:6 ደግሞ ሲጠቀስ፣ በአንዳንድ ዕብራይስጥ ቅጂ ስሙ በስኅተት ዲፋት ይባላል።

ፍላቪዩስ ዮሴፉስ እንዳሰበው፣ ሪፋት የወለዳቸው ብሄር «ሪፋትያውያን፣ አሁንም ጵፍላጎንያውያን የተባሉት» ነበር። ቅዱስ አቡሊደስ ደግሞ ሪፋት የ«ሳውሮማትያውያን» አባት አንደ ሆነ ጻፉ።

ሪፋት ብዙ ጊዜ ከሪፋያዊ ተራሮች ጋር ግንኙነት እንዳለው ይታስባል። በጥንታዊ ግሪኮች ታሪክ ጸሐፍት ዘንድ በሪፋያዊ ተራሮች ግርጌ ሪፋያውያን፣ አሪምፋያውያን ወይም አሪማስፒ የተባለ ብሔር ይገኝ ነበር። እነዚህ ተራሮች መታወቂያ ባብዛኛው ጸሐፍት ዘንድ ከዑራል ተራሮች ሰንሰለት (በዛሬው ሩስያ) ጋር አንድላይ ነው። በመጽሐፈ ኩፋሌ ሰንሰለቱ «ራፋ» ይባላል።

አውጉስት ቪልሄልም ኖበል ሃልዮ ዘንድ፣ ሪፋት ቄልታውያንን ወለዳቸው። በፕሉታርክ መሠረት ቄልታውያን ከራፋ ተራሮች ወደ ስሜን አውሮፓ ተሻግረው ነበርና[1]

በመካከለኛው ዘመን በአይርላንድ አፈታሪክ ደግሞ የአይርላንድና የስኮትላንድ ኗሪዎች ከሪፋት ወይም «ሪፋት ስኮት» (ስኮት ማለት እስኩቴስ) ተወልዱ። ለምሳሌ በጽሑፉ ሌቦር ጋባላ ኤረን በአንዳንድ ቅጂ መሠረት፣ በፌኒየስ ፋርሳ ፈንታ የጋሜር ልጅ «ሪፋት ስኮት» የእስኩቴስ ገዢ እና የጎይደሎች ወይም ሚሌሲያን ወላጅ ነበረ።

ዋቢ ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ Keil and Delitzsch Biblical Commentary on the Old Testament: Genesis 10:3.