ሚታኒ

ከውክፔዲያ
የሚታኒ መንግሥት በጫፉ፣ 1441 ዓክልበ.

ሚታኒ ከ1507 እስከ 1288 ዓክልበ. ግድም በስሜን ሶርያ፣ ስሜን ሜስጶጦምያና ደቡብ አናቶሊያ የቆየ ጥንታዊ መንግሥት ነበረ።

ሚታኒ ደግሞ በኬጥኛ ሑሪ፣ በግብጽኛ መተኒ ወይም ናሐሪን፣ በአካድኛ ሐኒጋልባት ይባል ነበር። ከጎረቤቶቻቸው ከኬጥያውያን፣ ጥንታዊ ግብጽአሦር ጋራ ይታገሉ ነበር፤ በመጨረሻ በ1307 ዓክልበ. ግድም ለአሦር መንግሥት ወደቆ ተገዥ ሆነ።

ያምኻድና የባቢሎን መንግሥታት በ1508-7 ዓክልበ. ለኬጥያውያን መንግሥት ንጉሥ 1 ሙርሲሊ በወደቁበት ጊዜ ያህል በሑራውያን ብሔሮች መካከል የሚታኒ መንግሥት በኪርታ እንደ ተመሠረተ ይታመናል። ሆኖም የግብጽ ፈርዖን 1 ቱትሞስ ከዚያ ትንሽ በፊት (1512 ዓክልበ.) ከኤፍራጥስ ወንዝ ማዶ በ«ናሓሪን» ላይ ዘምቶ ነበርና በአንዱ ጽሑፍ «መታኒ» ሲል ከዚህ ዘመቻ እንደ ሆነ ይታመናል፤ ቀደም-ተከትሉ እንዲህ ከሆነ ምናልባት ኪርታና የሚታኒ ባለሥልጣናት ከሙርሲሊ ዘመቻ በፊት በሑራውያን አገር ወይም ሐኒጋልባት ተመሠረቱ።

«ናሓሪን» የሚለው ግብጽኛ ስያሜ ደግሞ በእብራይስጥ መጽሐፍ ቅዱስ አራም-ናሓራይም (አረማይክ ናሓራይን ወይም «ኹለት ወንዞች») ይታያል። እንዲሁም በኪርታ ዘመን ያሕል የአራም-ናሓራይም ወይም እንደ ግሪክኛው የ«መስጴጦምያ» ንጉሥ ኲሰርሰቴም እስራኤልን አሸንፎ ለስምንት አመት እንደ ገዛ ይለናል (መጽሐፈ መሣፍንት 3:8)። «ኲሰርሰቴም» የሚለው ከዕብራይስጥ ስድብ ስለ ተዛበ ትክክል የንጉሥ ስም አይታስብምና የዚህ «ኲሰርሰቴም» መታወቂያ በእርግጡ ገና አልተፈታም።

የሚታኒ ሥርወ መንግሥት አለቆች የሕንዳዊ-ኢራናዊ ቋንቋ ተናጋሪዎች እንደ ነበሩ ይመስላል፤ ከቋንቋቸው የታወቁት ጥቂት ቃላትና ስሞች እንደ ሳንስክሪት፣ የጣኦታቸውም ስሞች ደግሞ እንደ ርግ ቬዳ ጣኦቶች ይመስላሉ። ከዚህ የተነሣ የሚታኒ ባለሥልጣናት በኋላ ሜዶንማዳይ ከተባለው አካባቢ (አሁን አዘርባይጃንና ስሜን ፋርስ) የደረሱ መስፍኖች እንደ ነበሩ ይታስባል። የገዙአቸው ተራ ሕዝቦች ቋንቋ ግን ሑርኛ ሲሆን በጊዜ ላይ አለቆቹም ሑርኛ ይናገሩ ነበር።


የሚታኒ ነገሥታት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]