ጥንታዊ ግብፅ

ከውክፔዲያ
(ከጥንታዊ ግብጽ የተዛወረ)

ጥንታውያን የግብጽ ባለሥልጣኖች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

እንዲህ የመሳለሉት ብዙ ሐውልቶች ከሁሉ ጥንታዊ የሆኑት የግብጽ ሕዝብ በ1 ሜትር ቁመት አሳዩ። ግብጻውያን የ«ሴት»ና የ«ሔሩ» ክልሶች መሆናቸውን ያምኑ ነበር።

መጽሐፍ ቅዱስ መሠረት ከማየ አይኅ ቀጥሎ መጀመሪያ የአፍሪካ ሕዝብ የኖኅ ልጅ የካም ዘሮች ናቸው፤ ይህ አገር ሰናዖር ለሚሉት ቅርብ ስለ ነበር የባብል ግንብ ከተሠራ በኋላ ከዚህ ተነስተው ወደ ግብፅ ወረዱ።

የግብጽ ቀድሞ ዘመን መንግሥት ዋና ጥንታዊ ነው፤ የመሠረተውም ፈርዖን ሜኒስ የተባለው ነው። ጸሓፊው ጊዮርጊስ ስንቄሎስ (፰፻ ዓ.ም. አካባቢ የጻፈው) ይህ ፈርዖን ሜኒስ በዕውነት የካም ልጅ ምጽራይም እንደ ነበረ ገመተ።

ዳሩ ግን አባ አውሳብዮስ በጻፉት ዜና መዋዕል ዘንድ (፫፻፲፯ ዓ.ም. ተጽፎ)፣ የድሮ ግብጻዊው ባለታሪክ ማኔጦን (፫ኛው ክፍለ ዘመን ዓክልበ.) ስለ ኋለኞቹ ግብጻውያን ሲጽፍ፣ ይኮሩበት የነበረው የታላቁ ጥንት ዘመን ከማየ አይህ አስቀድሞ እንዳለፈ፣ በኋላም በዚያው አገር ዳግመኛ ከሠፈረበት ከካም ልጅ ምጽራይም በውኑ እንደ ተወለዱ ጽፎ ነበር። ተመሳሳይ ታሪክ በእስላም ጸሐፊዎች በግብጻዊው እብን አብድ ኤል-ሀከም እና በፋርሳውያን አል-ታባሪሙሐመድ ቈንዳሚር መጻሕፍት ሲገኝ፣ ፒራሚዶችእስፊንክስ ወዘተ. ሁሉ የተሠሩ ከጥፋት ውኃ በፊት በኖሩት ክፉ ዘሮች ሆኖ፣ ከዚያ በኋላ ግን አገሩ ለካም ተወላጅ ለምጽራይም ('ማሣር' ወይም 'መሥር') ተሠጠ ብለው ጻፉ።

በግሪኩ ጸሐፊ ሄሮዶቶስ ዘንድ፣ የግብፅ ቀድሞ ዘመን የመጀመሪያው ፈርዖን ሜኒስ ነጭ አባይን ከመነሻው ወደ ጎን መለሰና ውሃው ይፈስበት በነበረው ላይ ሜምፊስ የተባለውን ከተማ ቆረቆረ። ታላቅ ንጉሥም ስለ ነበረ ከሞተ በኋላ ሕዝቡ እንደ አምላክ አድርገው አመለኩት። በዘመናዊ አስተሳስብ፣ ይህ ላይኛ ግብጽታችኛ ግብጽ ያዋሐደው መጀመርያው ፈርዖን መታወቂያ ለሥነ ቅርስ ከሚታወቀው ፈርዖን «ናርመር» ከተባለው ጋር አንድ ነው።

ናርመር (ሜኒስ) አገሩን ካዋሐደ አስቀድሞ ሌሎችም ነገሥታት (ለምሳሌ ንጉሥ ጊንጥ) በአገሩ ክፍሎች ብቻ ላይ እንደ ነገሡ ከተገኙት ቅርሶች (የመንደሮቹ መኳያ ሰሌዳ እንደሚያሳይ) ይታወቃል።

የሃይሮግሊፍ ቅርሶችና መዝገቦች ለማንበብ ችሎታው አሁን ስላለ፣ ሜኒስ ከነገሠ በኋላ የግብፅ ታሪክ በጥቂት መጠን ተገልጾአል። መጀመርያው ሥርወ መንግሥታት (፩ኛው እስከ ፮ኛው ድረስ) የቀድሞ ዘመን መንግሥት ይባላሉ። በ፩ኛው ሥርወ መንግሥት ሰባአዊ መስዋዕት በሰፊ ይደረግ ነበርና ከፈርዖኖቹ ጋራ ብዙ ሎሌዎች አብረው ይቀበሩ ነበር። የሔሩ ወገን በሴት ወገን ላይ ይበረታ ነበር። በ፪ኛው ሥርወ መንግሥት የፈርዖኖች መቃብር ከተማ ከላይኛ ግብጽ ወደ ታችኛ ግብጽ (ስሜኑ) ተዛወረ። በኋለኛ 2ኛው ሥርወ መንግሥት ዘመን የሴት ወገን ወኪል ፈርዖን ፐሪብሰን ተነሣና ያንጊዜ ትግሎች እንደ በዙ ይመስላል። በ፫ኛው ሥርወ መንግሥት መጀመርያ የሔሩ ወገን ለሥልጣን ተመልሶ፣ ነጨሪኸት የተባለው ፈርዖን የመጀመርያውን ሀረም (ፒራሚድ) አሠራ። ከርሱም በኋላ የተነሡት ታላላቅ ፈርዖኖች በጊዛ ሜዳ ላይ ፒራሚዶቻቸውን እንዲሁም የጊዛ ታላቅ እስፊንክስን ሠሩ። በ፬ኛውም ሥርወ መንግሥት የፈርዖኖች ዝሙት የገዛ እኅቶቻቸውን እስከሚያግቡ ድረስ ደረሰ። በ፭ኛው ሥርወ መንግሥት መጨረሻ ፈርዖኖች በሀረሞቻቸው ውስጥ የሀረም ጽሕፈቶች ያስቀረጹ ጀመር፤ እነኚህ ጽሕፈቶች የሔሩ ተከታዮች ወገን (ወይም «ደቂቃ ሔሩ») በሴት ተከታዮች ወገን ላይ የፈጸሙትን ጨካኝ የጭራቅነት ሥነ ስርዓት ይመሰክራሉ። ይህም አስጨናቂ ሁኔታ በ፮ኛው ሥርወ መንግሥት እየተቀጠለ ፈርዖኖቹ ዓለማቸውን ሁሉ ከነጎረቤቶቻቸውም ጋር በጽናት ይገዙ ነበር።

ኤብላሶርያ የ፮ኛው ሥርወ መንግሥት ፈርዖን 1 ፔፒ ቅርስ በፍርስራሹ ስለተገነ፣ አብዛኛው ሊቃውንት ፔፒ በኤብላ ዘመን በ2300 ዓክልበ. እንደ ነገሠ ገመቱ። ስለዚህ የቀድሞ ዘመን መጨረሻ በፍጹም ተስተዋል። ነገር ግን ይህ በጥንታዊ ቅርሶች ክምችት መካከል ስለተገኘ ዕድሜስ በዚያ ሊታወቅ አይችልም።[1] የቀድሞ ዘመናት ቅርሶች የተገኙባቸው ሥፍራዎች ኤብላና ጌባል በዘመናቸው የቀድሞ ዘመን ቅርሶች ጥናት መኃሎች ስለ ነበሩ እንደ ሙዚየም ያህል ቦታዎች ነበሩባቸው።

በተጨማሪ ለቀድሞ ነገሥታት ዘመኖች ዋና ምንጭ የሆነው ንጉሣዊ ዜና መዋዕል (ወይም «የፓሌርሞ ድንጋይ») በክፍሎች ሲካፈል፣ በየሁለቱ ክፍሎች የላም ቁጠራ ሰለተቆጠረ፣ እያንዳንዱ ክፍል አንድ ዓመት ሳይሆን አይቀርም የከብትም ቁጠራ የተደረገው በየ፪ ዓመት ነበር ብለው ገመቱ። ሆኖም በሠንጠረዡ እያንዳንዱ ክፍል ፮ ወር ከሆነ፣ የከብት ቁጠራ በየዓመቱ ይደረግ ነበር። ስለዚህ በብዙ መምህሮች ግምት የብዙ ፈርዖኖች ዘመን በ፪ ዕጥፍ ተረዘመ።

መጀመርያው መካከለኛ ዘመን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

«ንጉሥ መሪብሬ ቀቲ» የሚል የመዳብ ዕቃ ቅርስ

፮ኛው ሥርወ መንግሥት ከነገሠ በኋላ የግብፅ ታሪክ እጅግ ግልጽ ሆኖ አይታይም። በታሪክ ጸሐፍት እንደ ማኔጦን ዝርዝሮች በኩል፣ ለ፯ኛው-፰ኛው ሥርወ መንግሥታት በርካታ ስሞች ቢመዘገቡም፣ ከጥቂቶቹ ብቻ (እንደ ቃካሬ ኢቢዋጅካሬ) በስተቀር አንዳችም ሥነ ቅርሳዊ ማስረጃ ከቶ ስላልተገኘላቸው፣ ስሞች ብቻ ቀርተው በእውነት እንደ ኖሩ ወይም ዝም ብለው በማስመስል እንደ ተፈጠሩ አይታወቀም።

ቀድሞው ዘመን አልፎ መቃብሮች በሥነ ቅርስ እንደገና በግብጽ ሲታዩ፣ የሕዝብ ቁጥር ከበፊቱ እጅግ እንደ ተቀነሠ ግልጽ ነው።

ከቀድሞው ዘመን በኋላ በእርግጥኛነት የነገሡት መጀመርያ ፈርዖኖች ፱ኛውን መንግሥት በሄራክሌውፖሊስ የመሠረቱት በስማቸውም «ቀቲ» የተባሉት ናቸው። ከነዚህ ዋህካሬ ቀቲ ምናልባት መጀመርያው ፈርዖን ይሆናል። በሥነ ቅርስ ረገድ ግን ስለነዚህ ሥርወ መንግሥታት ልክ ቅድም-ተከተል ብዙ መረጃ የለንም።

በማኔጦን ዝርዝር ከ«አቅቶይስ» በቀር ለነዚህ ፱ኛ፣ ፲ኛ፣ ፲፩ኛ ሥርወ መንግሥታት እና እስከ «አመነመስ» ድረስ (፲፪ኛ ሥ.መ.) ምንም የፈርዖን ስያሜ አይሰጠንም። ከሌሎች የድሮ ምንጮች (በተለይ በሚካኤል ሶርያዊውባር ሄብራዩስ እንደ ታተመ) ለነዚህ «ጨለማ ዘመን» ፈርዖኖች መረጃ የነበረው ልማድ ይገኛል።

በዚህ መረጃ ዘንድ ለዚሁ ዘመን ከማኔጦን የቀሩት ስያሜዎች (በልዩ ልዩ ቅጂዎች) እንዲህ ናቸው፦

  1. «ፓኖፊስ»፣ 68 ዓመት - ወይም ምጽራይም
  2. «ኤውፒፓፍዮስ / ኤውፕሮፕሪስ / አፒፋኖስ»፣ 46 / 48 ዓመት - መጀመርያ መርከቦች የሠራ
  3. «ሳኖስ ኢትዮጶስ / አጣኖጵዮስ»፣ 60 ዓመት - በኩሽ መንግሥት ላይ ስለ ዘመተ «ኢትዮጶስ» ተባለ፣ ሳባንም ገደለ።
  4. «ፈርዖን / ፐርዖን ባርሳኖስ»፣ 35 ዓመት - ከእርሱ ጀምሮ «ፈርዖን» የሚለው ስያሜ ተጠቀመ።
  5. «ካሪሞን»፣ 4 ዓመት - በእርሱ ዘመን «አርሞኒስ» ሰዶምንና ለሎችን ከተሞች ሠራ።
  6. «አፊንቶስ / አፋንቶስ / አፒንቶስ»፣ 32 ዓመት - ወደ ከላውዴዎን ንጉሥ «ኪሳሮኖስ» ልኮ የመስጴጦምያ አረመኔ ትምህርት ወደ ግብጽ አስገባ፤ በአባይ ዳር «የግብጽ ባቢሎን»ን ሠራ።
  7. «አርሳኮስ / ኦርኮስ / አውሮንኮስ»፣ 33 ዓመት - ከተማ በስሙ ሠራ።
  8. «ሳሞኖስ / ሳሞስ / ሲሞኖስ»፣ 20 ዓመት
  9. «አርሚዮስ / ሂርኮስ / አርሚኖስ»፤ 27 / 25 ዓመት - በ«አሦር ንጉሥ ቤሉስ» ተሸነፈ።
  10. «ፋርናዶስ / ፓራንዶስ ጤባዊው»፤ 43 ዓመት
  11. «ፋኖስ / ፓኖስ»፤ 40 ዓመት - ሣራን ከአብርሃም የወሰደው ይባላል።
  12. «ሂስቆስ / ኢሶኮስ»፣ 21 ዓመት

ለዚህ ጨለማ ዘመን ፱ኛው/፲ኛው ሥርወ መንግሥት ያሉን ቅርሶች ብዙ አይደሉም። ከሥነ ቅርስ በእርግጥ የታወቁት ነገሥታት መሪብታዊ ቀቲነብካውሬ ቀቲመሪካሬ ይጠቅልላሉ። በዚህም ዘመን የተደረጀ ሥነ ጽሑፍ (ትምህርት ለመሪካሬ) ይታይ ጀመር።

በ2121 ዓክልበ. ግድም አዲስ «ጤባዊ» (፲፩ኛው) ሥርወ መንግሥት በ2 መንቱሆተፕ ተመሠረተ። ዋና ከተማው ጤቤስ በደቡብ ሲሆን በስሜኑ በሄራክሌውፖሊስ የነበረው ቀቲዎች ወገን በመሪካሪ መሪነት ዓመጹ። ለጊዜው ሁለቱ ፈርዖኖች — መሪካሬ በስሜንና መንቱሆተፕ በደቡብ — ይታገሉ ነበር። በመጨረሻ ግን መንቱሆተፕ ድል አድርጎ እንደገና መላውን ግብጽ ገዛ። ይህ መንቱሆተፕ የዙፋን ስሙን በየጊዜ የቀየረው ምክንያት ግልጽ ባይሆንም እንደ ቀድሞው ኻሰኸምዊ በመምሰል አዲስ አገር ሲገዛ አዲስ ስም እንዳወጣ ይሆናል። በግብጽ አረመኔ እምነት መንቱሆተፕ ደግሞ የጥንታዊ ጣኦት ኦሲሪስ ትስብዕት ለብዙ ዘመናት ይቆጠር ነበር።

ሦስቱ አንተፎች (1 አንተፍ2 አንተፍ3 አንተፍ) በአመጽ ምክንያት ስሜኑን ለመግዛት አልቻሉም። ከጤቤስ ወደ ስሜንም ሆነ ወደ ደቡብ የነበሩት የግብጽ ኖሞች ገዦች አይቀበሉዋቸውም ነበር። 3 መንቱሆተፕና ልጁ 4 መንቱሆተፕ በአጭር ዘመን ውስጥ ይገዙ ነበር። በዚህ 11ኛው (ጤባዊ) ሥርወ መንግሥት መጨረሻ፣ «የግብጽ መካከለኛ መንግሥት» ዘመን መሠረት ይባላል።

መካከለኛው መንግሥት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የመካከለኛው መንግሥት መሥራች ፩ አመነምሃት

የግብጽ መካከለኛው መንግሥት ወይም 12ኛው ሥርወ መንግሥት ገዦች ሁሉ (2002-1819 ዓክልበ.) ከሥነ ቅርስ በደንብ ይታወቃሉ።

የሥርወ መንግሥቱ መሥራች 1 አመነምሃት (2002 ዓክልበ.) የዱሮውን ጥንታዊ መንግሥት ፈሊጥ በሥነ ሕንጻ እና በሥነ ጽሑፍ ለማሳደስ ጣረ። በ1982 ዓክልበ. ልጁን 1 ሰኑስረት እንደ ጋርዮሽ ፈርዖን አስነሣው፣ ዋና ከተማቸውም ከጤቤስ ወደ እጭታዊ ተዛወረ። በ1973 ዓም በኩሽ መንግሥት ላይ ዘመቱ፣ በሚከተለውም ዓመት ልጁ ሰኑስረት በሊብያ እየዘመተ አመነምሃት በሤራ ተገደለ።

፩ ሰኑስረት (1972 ዓክልበ.) እንደገና በ1964 ዓክልበ. በኩሽ ላይ ዘመተ፤ ሎሌዎችንም ወደ ሲና ልሳነ ምድር ለማዕደን ላከ። አለቃውም ሲኑሄ በአንድ ሰነድ ዘንድ በሶርያ ይዘመት ነበር። በ1940 ዓክልበ. ልጁን 2 አመነምሃት እንደ ጋርዮሽ ፈርዖን አስነሣው፤ በ1938 ዓክልበ. ዓረፈ።

በ2 አመነምሃት ዘመን (1938 ዓክልበ.) ግብጽ ከኩሽ፣ ሊባኖስፑንት ጋር ንግድ ያካሄድ ነበር፤ ሥራዊቶቹም በሶርያም ይዘመቱ ነበር። በ1907 ዓክልበ. ልጁን 2 ሰኑስረት እንደ ጋርዮሽ ፈርዖን አስነሣው፤ በ1905 ዓክልበ ዓረፈ።

በ፪ ሰኑስረት ዘመን የገቡት ሴማውያን እረኞችና ነጋዴዎች

በ፪ ሰኑስረት ዘመን (1905 ዓክልበ.) ብዙ ሴማውያን ወደ ጌሤም የገቡት እንደ ነበር ይመስላል፤ ስለዚህ ይህ ፈርዖን በመጽሐፍ ቅዱስ ዮሴፍን እንደ ግብጽ ጠቅላይ ሚኒስትር የሾመው እንደ ሆነ በአንዳንድ ደራሲ ታስቧል። በዚህም ሥርወ መንግስት ያሉት የሌሎቹ ፈርዖኖች ጠቅላይ ሚኒስትሮች ሁላቸው በስማቸው ተዘግበዋል፣ የ፪ ሰኑስረት ጠቅላይ ሚኒስትር ስም ግን በመዝገቦቹ አልተረፈልንም። በ1898 ዓክልበ. ልጁን 3 ሰኑስረት እንደ ጋርዮሽ ፈርዖን አስነሣው፤ በ1888 ዓክልበ. ዓረፈ።

፫ ሰኑስረት (1888 ዓክልበ.) በኩሽ፣ ምድያምና ከነዓን ላይ ዘመተ፤ መታወቂያው የግሪክ ታሪክ ጽሐፊዎች የጠቀሱት ሴሶስትሪስ ከሆነ እስከ እስኩቴስም ድረስ እንደ ዘመተ ይባል ነበር። በ1879 ዓክልበ. ልጁን 3 አመነምሃት እንደ ጋርዮሽ ፈርዖን አስነሣው፤ በ1859 ዓክልበ. ዓረፈ።

3 አመነምሃት (1859 ዓክልበ.) ለአንዳንድ ሀረሞችና ሐይቅ በመሥራት ይታወሳል። በ1832 ዓክልበ. ልጁን 4 አመነምሃት እንደ ጋርዮሽ ፈርዖን አስነሣውና ዓረፈ።

፬ አመነምሃት (1832 ዓክልበ.) የማዕደን ጉዞ ወደ ሲና ላከ። በ1823 ዓክልበ. ያለ ልጅ አርፎ እኅቱ ሶበክነፈሩ ተከተለችው።

ሶበክነፈሩ (1823 ዓክልበ.) ንግሥት እየሆነች፣ በ1821 ዓክልበ. በጌሤም የሠፈሩት ሴማውያን የራሳቸው ፈርዖን ያክቢም ሰኻኤንሬ ተፈቀዱ። በ1819 ዓም ዓረፈች።

ግብጽ ከዚህ በኋላ እንደገና ስለተከፋፈለ፣ የመካከለኛው መንግስት መጨረሻ ይቆጠራል። በሁለተኛው ጨለማ ዘመን መጀመርያ፣ ሁለት ሥርወ መንግሥታት ነበር፤ በስሜኑ የሴማውያን 14ኛው ሥርወ መንግሥትና የሶበክነፈሩ ተከታዮች በጤቤስ 13ኛው ሥርወ መንግሥት ናቸው።

ሁለተኛው መካከለኛ ዘመን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ግብጽ በሂክሶስ ዘመን 1646-1590 ዓክልበ.

የግብጽ ሁለተኛው ጨለማ ዘመን (1819-1548 ዓክልበ. ግ.) የ13ኛው፣ 14ኛው፣ 15ኛው፣ 16ኛው፣ 17ኛው ሥርወ መንግሥታት ያጠቅልላል። ከነዚህ ሁለቱ፣ 14ኛው (1821-1741 ዓክልበ.) እና 15ኛው (1661-1548 ዓክልበ.)፣ ከከነዓን የወጡ በስሜን (በጌሤም) የተመሠረቱ ሥርወ መንግሥታት ነበሩ። ከሁለቱም መካከል ወይም ከ1741-1661 ዓክልበ. ግብጽ በአንዱ የ13ኛው ሥርወ መንግሥት ሥር እንደ ተዋኸደ ይመስላል። 14ኛው ሥርወ መንግሥት ከዮሴፍ በኋላ ዙፋን የተሰጡ ዕብራውያን ነጋዴዎችና እረኞች ይመስላሉ፤ በኋላ ወደ ባርነት ገብተው ሙሴ ወደ ሲነ ልሳነ ምድር የመራቸው (ዘጸአት) በ1661 ዓክልበ. በመጽሐፈ ኩፋሌ አቆጣጠር ነው። በዚያው አመት ፈርዖኑ (መርነፈሬ አይ) ከነሥራዊቱ ከነሠረገላዎቹ በቀይ ባሕር ጠፍቶ፣ የግብጽ ኃይል ድንገት ስለ ደከመ፣ ወዲያው ከከነዓን ወጥተው አንድ የአሞራውያን ሥራዊት ወይም «ሂክሶስ» ተብለው ግብጽን ወረሩ።

እነዚህ ሂክሶስ 1661-1548 ዓክልበ. ከኗሪ ግብጻውያን ሥርወ መንግሥታት ጋራ ጦርነቶች ተዋጉ። 13ኛው ሥርወ መንግስት በጤቤስ እስከ 1646 ዓክልበ. ግ. ቀረ፣ በፈንታው 16ኛው ሥርወ መንግሥት በጤቤስና ሌላ «የአቢዶስ ሥርወ መንግሥት» ከዚያ ወደ ስሜን በአቢዶስ እንደ ተነሡ ይመስላል። 15ኛው የሂክሶስ ሥርወ መንግሥት በ1596 ዓክልበ. ግድም የአቢዶስን መንግሥት አሸነፉ፣ በ1590 ዓክልበ. ደግሞ ጤቤስን ይዘው 16ኛውን ሥርወ መንግሥት አስጨረሱ። ይህም የሂክሶስ ጫፍ ነበረ። በ1588 ዓክልበ. ሂክሶስ እንደገና ጤቤስን ትተው አዲሱ 17ኛው ሥርወ መንግሥት በጤቤስ ቆመ። ይህ 17ኛው ሥርወ መንግሥት ሂክሶስን ወደ ስሜን መለሳቸው፤ በመጨረሻም ግብጻዊው ንጉሥ 1 አህሞሰ (1558-1533 ዓክልበ. ግድም) የሂክሶስ ቅሬታ በማስወጣቱ (1548 ዓክልበ.) ግብጽኝ ዳግመኛ ስላዋኸደ፣ የግብጽ «አዲሱ መንግሥት» በዚያው ይጀመራል።

አዲሱ መንግሥት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ዋቢ ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ Michael C. Astour, Eblaitica 4, p. 60.