ጋብቻ

ከውክፔዲያ

ጋብቻ በሰዎች መካከል የሚፈጠር ማህበራዊ የአንድነት ሥርዓት ወይም ህጋዊ ስምምነት ነው። ስርዓቱ የሚመሠረተው በሰርግ ስነስርአት ወይም በሌላ ዝግጅት ሊሆን ይችላል። የዚህ ተቋም አወቃቀር እንደየ ባህሉ፣ እንደየ ሃይማኖቱ እና እንደየ ጊዜው ይለያያል። በወንድ እና በሴት መካከል ለሚፈጠር ጋብቻ ወንዱ ባል የሚባል ሲሆን ሴቷ ደግሞ ሚስት ትባላለች።

በመጽሐፍ ቅዱስ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ጋብቻ በመጽሐፍ ቅዱስ መጀመርያ የሚታየው አዳምና ሔዋን በእግዚአብሔር ፈቃድ ሲጋቡ ነው። ይኸው ጋብቻ በእግዚአብሔር አስተያየት ሁለቱም አንድ ሥጋ በሆኑበት ጊዜ ነበረ። ይህ ማለት አዳምና ሕይዋን በአምላኩ ፈቃድ ያለ ምንም ኅጢአት ፍትወታቸውን እርስ በርስ ለማርካት ተፈቀዱ። ይህ ሁኔታ ለፍቅር፣ ለደስታና ለማዝናናት የሚገባ ብቻ ሳይሆን፣ በተለይ ልጆችን ለመውለድና በቤተሠብ ለማሳደግ ያስመቻል። ስለዚህ የባልና የሚስት ጋብቻ እንደ ቸሩ አምላክ ግል ስጦታ ይቆጠራል። ከጋብቻ ውጭ ሌላ መንገድ ሁሉ ጥፋት ስለሚያመጣ፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ጸንተው የሚኖሩ የትዳርን ጥቅም ብዙ አይስቱም።

ብሉይ ኪዳንሕገ ሙሴ ዘንድ የማጫ ሥርዐት ደግሞ ይጠቀሳል። ይህ ለእጮኛይቱ ወላጆች የሚበደር መጠን ነበር፤ አሁንም ብዙ ጊዜ ከጥሎሽ ጋራ (ወደ አዲሱ ቤተሠብ ከወላጆቹ ከሚመልሰው መጠን ጋር) ይደናገራል።

የቤተሰብ ትስስር በአስላም[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በዚህ የቁርኣን አንቀፅ ከምዕመናን ባህሪያት ውስጥ አላህ እንዲቀጥል ያዘዘውን ነገር የሚቀጥሉ ሲል ይገልፃቸዋል። ለነዚህ ምርጥ የመኖሪያ አገር (ጀነት) አላቸው። በሌላ በኩል አላህ እንዲቀጥል በርሱ ያዘዘውን ነገር የሚቆርጡ ሠዎች መጥፎ መኖሪያ (ጀሃነም) ተዘጋጅቶላቸዋል።

“ከጌታህ ወዳንተ የተወረደው እውነት መኾኑን የሚያውቅ ሰው እንደዚያ እርሱ ዕውር እንደኾነው ሰው ነውን? የሚገሠጹት የአእምሮ ባለቤቶች ብቻ ናቸው። እነዚያ በአላህ ቃል ኪዳን የሚሞሉ የጠበቀውንም ኪዳን የማያፈርሱ ናቸው። እነዚያም አላህ እንዲቀጠል በእርሱ ያዘዘውን ነገር የሚቀጥሉ ጌታቸውንም የሚያከብሩ መጥፎንም ቁጥጥር የሚፈሩ ናቸው። እነዚያም የጌታቸውን ውዴታ ለመፈለግ የታገሱ፣ ሶላትንም አዘውትረው የሰገዱ፣ እኛ ከሰጠናቸው ሲሳይም በምስጢርም ኾነ በግልጽ የመጸወቱ፣ ክፉውንም ነገር በበጎ የሚገፈትሩ ናቸው። እነዚያ ለእነሱ መጨረሻይቱ ምስጉን አገር አለቻቸው። (እርሷም) የመኖሪያ ገነቶች ናት። ይገቡባታል። ከአባቶቻቸውም፣ ከሚስቶቻቸውም፣ ከዝርያቸውም መልካም የሠራ ሰው (ይገባታል)። መላእክትም በእነርሱ ላይ ከየደጃፉ ሁሉ ይገባሉ። ‘ሰላም ለእናንተ ይኹን። (ይህ ምንዳ) በመታገሳችሁ ነው። የመጨረሻይቱም አገር ምን ታምር!’ (ይሏቸዋል)። እነዚያም የአላህን ቃል ኪዳን ከጠበቀ በኋላ የሚያፈርሱ አላህም እንዲቀጠል በእርሱ ያዘዘውን ነገር የሚቆርጡ በምድርም ላይ የሚያበላሹ እነዚያ ለነሱ እርግማን አለባቸው። ለእነሱም መጥፎ አገር (ገሀነም) አላቸው።” (ሱረቱ ረዕድ 13፤ 19-25)

ብዙ ምሁራን አላህ እንዲቀጥል ያዘዘው ማለት ዝምድና ወይም “ሲለት አር-ረሂም” እንደሆነ ይስማማሉ። ዝምድና በተመለከተ እጅግ ብዙ የቁርአን አንቀፆችና ሀዲሶች ተጠቅሠዋል።

ስለ ኡማው አንድነት ስናስብ ብዙ ነገሮችን ማሠብ ያስፈልጋል። በተለይ የቤተሠብ አንድነት ሳይኖር የኡማው አንድነት መኖር አይታሠብም። ኢስላም ቤተሰብን በሦስት ዕርከን ያየዋል። የወላጅና የልጆች ቤተሠብ፣ የእምነት ቤተሰብና የሠው ልጅ ቤተሠብ። ሦስቱም ዕርስ በርስ የተሣሠሩ አንዳቸው ለአንዳቸው አስፈላጊ ናቸው። ነገር ግን፤ የደም ትስስር ያለበት ቤተሠብ ከሁሉ በላይ አስፈላጊው ነው። ስለትልቁ (የሠው) ቤተሠብ ስናስብ ትንሹ ቤተሠብ (የደም ትስስር) ያለው ሚና ወሳኝ መሆኑን ልናውቅ ይገባል። በጥሩ ቤተሠብ የሚያድጉ ህፃናትና ለልጆች ትኩረት የሚሰጡ ወላጆች ከሌላው በበለጠ ይበልጥ ምርታማ፣ የተረጋጋነ ሠላማዊ ናቸው። በቤተሠብ ውስጥ ሦስት ወሣኝ ነጥቦች አሉ።

  • 1.በጥንዶች መካከል ያለ ግንኙነት
  • 2.በወላጆችና ለልጆች መካከል ያለ ግንኙነት
  • 3.በዘመዶች መካከል ያለ ግንኙነት።

ኢስላም ሶስቱንም አክብሯል። እነዚህን ዝምድናዎች መጠበቅ የኢማን ምልክት ነው። ቃል ኪዳንን መሙላት፣ የሌሎችን መብት ማወቅ፣ ፍቅር፣ ርህራሄ፣ እንክብካቤ፣ ክብር መስጠት ሁሉ መልካም ግንኙነት ለመፍጠር ወሣኞቹ ናቸው። ነብዩ ቲርሚዚ ላይ እንደተዘገበው “ከምእመናን መካከል በኢማኑ ምሉዕ የሆነው ለቤተሠቦቹ መልካም ባህሪ የሚያሳይና ሩህሩህ ነው” ብለዋል። በሌላ ዘገባ “ከናንተ መካከል ምርጡ ለቤተሠቦቹ ምርጥ የሆነው ነው። እኔ ከናንተ የበለጠ ለቤተሠቦቼ ምርጡ ነኝ።” (ኢብን ማጃህ)

  • 1.የጥንዶች ግንኙነት፡- ኢስላም ወጣቶች የትዳር አጋሮቻቸውን ሲመርጡ በልዩ ጥንቃቄ እንዲሆን ያሳስባል። በምርጫ ወቅት ለሞራልና ለሃይማኖት ጥንካሬ ልዩ ትኩረት መስጠት ይገባል። ባልና ሚስት ግዴታቸውንና ሃላፊነታቸውን ጠንቅቀው መረዳት አለባቸው። ባል ቤተሠቡን የመመገብና ወጪዎቹን የመሸፈን ሃላፊነት አለበት። ለሚስቱ ጥሩ የትዳር አጋር መሆን፣ እሷንም ሆነ ቤተሠቦችዋን ማክበር፣ በማንኛውም ጉዳይ ሊያማክራት ይገባዋል። በአጠቃላይ ጥሩ የቤተሰብ መሪና አርአያ መሆን ይጠበቅበታል። ሚስት፡- የባሏን ኃላፊነት ማወቅ፣ እሱንና ቤተሠቡን ማክበር፣ ፍላጎቱን መጠበቅ፣ ማገዝና ማማከር፣ ያለሱ ፈቃድ የሚያስከፋውን ነገር ከማድረግ መቆጠብ ሲኖርባት ሁለቱም አንዳቸውን ለአንዳቸው አላህ ስለፈቀደላቸው ለአላህ አመስጋኞች መሆንና በተሠጣቸውም ሊረኩ ግድ ይላል።
  • 2.ወላጆችና ልጆች፡- ወላጆች የልጆቻቸውን ስሜት መረዳትና በጥሩ ትምህርትና የሥነ- ምግባርና መንፈሳዊ እነፃ ሊያሳድጓቸው ያስፈልጋል። ለልጆቻቸው አዛኝ፣ አፍቃሪና ሩህሩህ ሲሆኑ በልጆቻቸው መካከልም ፆታንም ሆነ ሌላን ነገር መሠረት ያደረገ አድልዖ ከማድረግ መቆጠብ አለባቸው። ልጆች እያደጉ ሲመጡ በቤተሠቡ ጉዳይ እንዲሳተፉ ማድረግና ማማከር ያስፈልጋል። አግብተው ሲኖሩም ወላጆች በልጆቻቸው ትዳር ላይ እስከዚህም መግባት የለባቸውም። ልጆች ወላጆቻቸውን መተባበር መታዘዝና መርዳት ይጠበቅባቸዋል። ወላጆቻቸው ሲያረጁ ሊረዷቸው ሊያዝኑላቸውና ሊንከባንከቧቸው ይገባል። ከሞቱም በኋላ ዱዐ ሊያደርጉላቸው ግድ ነው።
  • 3.ዝምድና፡- ኢስላም ለዝምድና ጠንካራ ትኩረት ሰጥቷል። ሁሉንም መንከባከብም ይገባል። አላህ እንዲህ ይላል፡-

“እናንተ ሰዎች ሆይ! ያንን ከአንዲት ነፍስ (ከአዳም) የፈጠራችሁን ከእርስዋም መቀናጆዋን (ሔዋንን) የፈጠረውን ከእነርሱም ብዙ ወንዶችንና ሴቶች የበተነውን ጌታችሁን ፍሩ። ያንንም በርሱ የምትጠያየቁበትን አላህንና ዝምድናዎችንም (ከመቁረጥ) ተጠንቀቁ። አላህ በእናንተ ላይ ተጠባባቂ ነውና።” (ሱረቱ ኒሣዕ 4፤1)

ቤተሠብ የትስስር መረብ ነው። አንዳንዱ ቅርብ ነው። አንዳንዱ ሩቅ ነው። ኢስላምም ቅድሚያ የሚገባቸው ቅድሚያ የሚሠጣቸውና ሚዛን እንዳይዛባ ያስጠነቅቃል።