ሸዋ

ከውክፔዲያ

ሽዋኢትዮጵያ ገጸ ምድር መሃል ላይ የሚገኝ ታሪካዊ ሥፍራ ነው። ለብዙ መቶ ዓመታት በሉዐላዊነት በራሱ መሪዎች ሲተዳደር የኖረ የኢትዮጵያ አካል ሲሆን፣ ርዕሰ ከተማው እስከ ፲፰፻፹፱ ዓ/ም በሰሜን ሸዋ ውስጥ በየጊዜው በተለያዩ ሥፍራዎች ሲፈራረቅ ቆይቶ ባለፉት መቶ በላይ ዓመታት ግን አዲስ አበባ ሆናለች። ደብረ ብርሃንአንኮበርአንጾኪያልቼ እና እንጦጦ በተለያዩ ጊዜያት የሸዋ ርዕሰ ከተማዎች ነበሩ። የሸዋ ገጸ ምድር እምብርት ባሁኗ ኢትዮጵያ መሃል የሚገኙት ተራራዎች ናቸው። በአህመድ ግራኝ ወረራ ጊዜ የባሌ ክፍለ ሀገር ከተወሰደ በኋላ የሸዋ ድንበር የኢትዮጵያ የደቡብ-ምሥራቅ ድንበር ነበር። የግዛቱ ተራራማነት የተፈጥሮ መከላከያ በመሆን ከውጭ ወረራ ለመላ አገሪቱ ደጀን የነበረና በፍትህ የአስተዳደር ዝናውም ለሌላ የኢትዮጵያ ዜጋዎች መጠጊያና መሸሸጊያም ነበር። አንዳንዴም በወራሪ ሕዝቦች ምክንያት ከቀሪው የኢትዮጵያ ግዛቶች ተግንጥሎም አብዛኛው የሰሜን ሸዋ ግዛቶች፣ ማለትም ሰላሌ(ግራሪያ)፤መርሃቴ፤ ደራ፤ መንዝ፤ ተጉለትይፋትምንጃር እና ቡልጋ ሕዝብ ክርስቲያን አማራ እና ኦሮሞዎች ናቸው። ደቡብ እና ምሥራቅ ሸዋ ግን አብዛኛው የኦሮሞ ብሔር እና የእስላም ኃይማኖት ተከታዮች ናቸው። በሰሜን ሸዋ ብዙ ታሪካዊ አብያተ ክርሲያናት እና ገዳማት ይገኛሉ። ከነዚህም በዋናነት የሚጠቀሰው፣ አቡነ ተክለ ኃይማኖትሰላሌ ወረዳ የመሠረቱት ታዋቂው የደብረ ሊባኖስ ገዳም ይገኙበታል።

Selale Famous : Danny Mack

የሰላሌ ታዋቂ ሰው : Danny Mack

ቀደምት ታሪክ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሸዋ ለመጀመሪያ ጊዜ በታሪክ የተመዘገበችው በ896 እ.ኤ.አ. በተመሠረተውና ዋና ከተማውን ወለላ (Walalah)ላይ አድርጎ በነበረው የእስላም ግዛት ውስጥ ነው በማለት በኢትዮጵያ ታሪክ ዘጋቢዎች ይታመናል። ከነዚህም አንድ፣ ስለ ኢትዮጵያ ብዙ ትምህርታዊ መጽሐፍትን የደረሰው ሀንቲንግፎርድ (G.B.W. Huntingford) ነው። ይህ ግዛት ወደ ፲፪፻፸፮ ዓ/ም በይፋቱ ሱልጣን ሥር ተጠቃለለ። በቅርብ ጊዜ በፈረንሳይ የሥነ-ቅርስ ባለሙያዎች ጥናት መሠረት ሦስት ቦታዎች የሸዋ እስላማዊ ንጉዛት(በዘውድ የሚተዳደር ግዛት) የከተማ ማእከላት ናቸው ተብለው ተገምተዋል።

ሣህለ ሥላሴ ንጉሠ ሸዋ

አጼ ይኩኖ አምላክ የዘመኑን የዛግዌ ስርወ መንግሥት በመቃወም ሲነሱ ከክርስቲያን አማራዎች አገር ከሸዋ እንደተነሱ እና ቀድሞውንም የአክሱም ነገሥታት በጉዲት መነሳት ሥልጣናቸውን ሲለቁ ከዛች ንግሥት በመሸሽ ተከታዮቻቸውንና ቤተ ሰባቸውን ደብቀው የኖሩት በዚሁ በሸዋ ውስጥ ነበር። እንዲሁም ክብረ ነገሥት (አንቀጽ 39) እንደሚለው፣ ሸዋ የአጼ ቀዳማዊ ምኒልክ ክፍላገር ሆኖ ነበር። ሆኖም አንዳንድ ዘመናዊ ሊቃውንት የዳሞትና የአክሱም መንግሥታት ሥልጣን እስከ ሸዋ ድረስ ወደ ደቡብ እንዳልተዘረጋ የሚል ጥርጣሬ አለባቸው።

፲፮ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መላው ክርስቲያን ኢትዮጵያ በአህመድ ግራኝ ሠራዊት (አዳል) በተወረረ ጊዜ ሸዋ ተመልሶ የእስላም አገር ሆነ። ከዚያ ጊዜ ጀምሮ እስከ ፲፰ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ የሸዋ ታሪክ እምብዛም ባይዘገብም አጼ ልብነ ድንግል እና ልጆቻቸው በወረራ ጊዜያት ሸዋን መሸሻቸው አድርገውት እንደነበር ተጽፏል።

የሸዋ ነገሥታት ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት በይኵኖአምላክ ጊዜ ከደብረ ሊባኖስ ወደ ሐይቅ በመጡት በአባ ተክለሃይማኖት እገዛ እንደተመሠረተ ይታመናል። የአኵስም ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት በዮዲት ጕዲት ተንኮታኩቶ ወደመጥፋት ደርሶ ነበረ። የዮዲት ጕዲት ጦር በሸዋ ጭፍሮች ከተሸነፈ ወዲህም ሰሎሞናዊው ሥርወ መንግሥት አላንሰራራም ነበር። ይኵኖአምላክም ከንግሥናው በፊት በይፋት፣ በመርሐ ቤቴ፣ በተጕለትና በመንዝ ኖሯል። ከይኵኖአምላክም ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት ውስጥ 99 ሀገራትን (በሓውርት) ያስገበረው ዓምደ ጽዮን ደማቅ ታሪክ ካላቸው ነገሥታት መሃል አንዱ ነው። ከግራኝ ይማም አሕመድ በኋላ ጎንደር መናገሻ ከመሆኗ ጋራ ተያይዞ የሸዋ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት ለጎንደሩ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት መሠረት ሆኗል። ከዚያም በኋላ በ17ኛው ክ/ዘመን ነጋሢ ይፋት አካባቢ ያለውን ቦታ ይቆጣጠር ጀመር። በይፋዊ ታሪክ፣ የነጋሢ አባት ልብሰ ቃል (በመንዝ የአጋንቻ ጌታ) በአጼ ልብነ ድንግል ታናሽ ልጅ በያዕቆብ በኩል የሚመጣ በአባት በኩል የዘር ሐረግ ያለው ነው ይላል። ይህም ማለት ከሰለሞን ስርወ መንግስት ጋር የተያያዘ ነው ማለት ነው። በዚህ መሰረት የጎንደር ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት ከሸዋ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት በኋላ የመጣና ያበበ ነው ማለት ይቻላል።

የሸዋ መሪዎች ማዕረጋቸው ደግሞ በሸዋ ብቻ የሚገኘው መርዕድ አዝማች ነበር። የነጋሢ ልጁ ስብስትያኖስ የመጀመሪያው መርዕድ አዝማች ነበር። ተከታታይ መሪዎች ይሄንን ማዕረግ ሲጠቀሙበት ቆይተው የመርዕድ አዝማች ወሰን ሰገድ ልጅ ሣህለ ሥላሴ በአባታቸው ወንበር ሲቀመጡ ንጉሠ ሸዋ ተባሉ። ከሳቸውም በኋላ ልጃቸው ንጉሥ ኃይለ መለኮት ለስምንት ዓመታት ነግሠው ጥቅምት ፴ ቀን ፲፰፻፵፮ ዓ/ም ሲያርፉ ልጃቸው አቤቶ ምኒልክ ገና ሕጻን ነበሩ። ወዲያው በዓፄ ቴዎድሮስ ተማርከው መቅደላ ከኖሩ በኋላ አምልጠው ሸዋ ሲገቡ በአባታቸው ወንበር ንጉሠ ሸዋ ተብለው ነገሡ።ከርሳቸው በኋላ ቀዳማዊ ግርማዊ ኃይለ ሥላሴ የሸዋ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት የመጨረሻው ንጉሥ ናቸው። በ፲፱፻፳፫ ዓ/ም የንጉሠ ነገሥትነቱ በትረ ሥልጣን ወደ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሲዘዋወር፤ አልጋ ወራሽነቱን እና የጥንቱን የሸዋ መሳፍንት ማዕርግ ለልጃቸው አስፋ ወሰን ሰጥተዋቸው ልዑል መርዕድ አዝማች አስፋ ወሰን ተባሉ።

የሸዋ አማርኛ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በተለምዶ የሸዋ አማርኛ የሚባለው ርቱዕ አማርኛ ነው። አሁን ላይ በመላው የኢትዮጵያ ክፍላተ ሀገራት ቅቡልነት አግኝቷል። ለአማርኛ መዝገበ ቃላት መዳበርም የሸዋ ሊቃውንት የማይተካ ድርሻ አበርክተዋል።

የሰሜን ሸዋ ዞን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የቆየ ታሪክ ካላቸው አካባቢዎች አንዱ የሰሜን ሸዋ ዞን ነው፡፡ ፲፭ሺ ፱፻ ነጥብ ፺፯ ካሬ ኪሎ ሜትር ስፋት ያለው የሰሜን ሸዋ ዞን በሁለት የከተማ አስተዳደሮችና በሃያ ሁለት ወረዳዎች ተከፋፍሎ ፪ ነጥብ ፫ ሚሊዮን ህዝብ የሚኖርበት ሲሆን ውርጭ፣ ቆላ፣ ደጋና ወይና ደጋ የአየር ንብረቶችን አካቶ ይዟል። አዋሳኞቹም በምዕራብ፣ በደቡብ ምዕራብ፣ በደቡብና ደቡብ ምስራቅ ኦሮሚያ ክልል፣ በሰሜን ምስራቅ አፋር፣ በሰሜን ደቡብ ወሎና ኦሮሚያ ዞኖች ናቸው።

ዞኑ ከቅድመ ታሪክ ጀምሮ እስከ ታሪክ ዘመን ያሉ አሻራዎች የሚገኙበት ስለመሆኑ የሥነ ቅርስ ግኝቶች ይጠቁማሉ። ከ፲፪፻፸ ዓ/ም እስከ ፲፭፻፳፯ ዓ/ም ድረስ «የሰሎሞን ስርወ መንግሥት» የመራሄ መንግሥቱ ዋና ማዕከል እንደነበረም የተለያዩ የታሪክ ምንጮች ይገልፃሉ። የሰሜን ሸዋ ምሥራቃዊ ክፍል ከ፰፻፸፪ ዓ/ም ጀምሮ ዋነኛው የእስልምና ስርወ መንግሥት መቀመጫ ከመሆኑ ባሻገር ከ፲፪ኛው እስከ ፲፮ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ የይፋት ስርወ መንግሥት የማዕከላዊ መንግሥቱ ተቀናቃኝ ኃይል እስከመሆን ደርሶ ነበር። በመጨረሻም ከሌሎች ታሪካዊ ሁኔታዎች ጋር ተደማምሮ በ፲፮ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የእስልምናው ኃይል በግራኝ አህመድ መሪነት በማየሉና በማሸነፉ ማዕከላዊ መንግሥቱ ከሸዋ ወደ ጎንደር ለመዛወር ተገዷል።

፲፮፻፺፮ ዓ/ም በመንዝ የተንቀሳቀሰው የሸዋ ስርወ መንግሥት እንደገና ማዕከላዊ መንግሥቱ ወደ ሸዋ በመመለሱ በዘመናዊ ታሪካችን ላይ ጉልህ አስተዋጽኦ አበርክቷል። በእነዚህ የታሪክ ሂደቶችም ሰሜን ሸዋ የበርካታ ጥንታዊ የታሪክና የባህል ነፀብራቅ የሆኑ አሻራዎች ባለቤት ሊሆን ችሏል።

ታሪካዊ ቦታዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የሸዋ ወታደሮች፣ በ፲፰፻፷ ዎቹ
  • ቁንዲ ከተማ - ረጅሙን የዞኑን ተራራ ተንተርሳ የምትገኘው የቁንዲ ከተማ ሌላዋ ታሪካዊ ቦታ ናት። ከተማዋ የተመሰረተችው በመርዕድ አዝማች ወሰን ሰገድ ነው። ከአንኮበር አሥር ኪሎ ሜትር ሲቀር በምትገኘው ቁንዲ የሚገኘው ቤተ መንግሥት በግንብ የተከበበ እንደነበረ በዙሪያው የሚታየው ፍርስራሽ ያረጋግጣል። የቁንዲ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያንም የዚያን ዘመን የእደ ጥበብ ውጤት ያንፀባርቃል።
  • አልዩ አምባ - የአንኮበር ታሪክ ሲዘከር የስምጥ ሸለቆ አካል የሆነችው የአልዩ አምባ ከተማና የአብዱል ረሱል የእስልምና መቃብር ሥፍራ አብረው የሚጠቀሱ ናቸው። አልዩ አምባ ከአንኮበር ከተማ አሥራ ሁለት ኪሎ ሜትር ያህል ቁልቁል ሲወረድ ትገኛለች። አልዩ አምባ እንደ ሐረር በግንብ የተከበበች ስትሆን በምስራቅ፣ በደቡብና በምዕራብ በሮች አሏት። ከመካከለኛው ዘመን ጀምሮ እስከ ፳ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ድረስ በኢትዮጵያ ታሪክ ጥንታዊ ከሚባሉት የቀረጥ ኬላዎችና የንግድ ማዕከል አንደኛዋ ነበረች። የፈረንሲስ ዲፕሎማት ሮቺ ሄሪኮርት እንደፃፈው ከ፲፭፻ እስከ ፲፯፻ የሚጠጉ ግመሎች የአገር ውስጥ ምርት ወደውጭ ያጓጉዙባት ነበር። በ፲፰፻፴፬ ዓ/ም እና ፲፰፻፴፭ ዓ.ም በአገራችን መጀመሪያ የሆነው የቀረጥ ውል የተፈረመው በአልዩ አምባ ገበያ መሠረት ነው። በከተማዋ ከፐርሽያ (ኢራን) ፣ ከህንድና ከአረብ አገሮች የሚመጡ በርካታ የውጭ አገር ዜጎች ይኖሩባት እንደነበርም ጎብኝዎች ጽፈውላታል። በዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ ዘመን የቀረጥ መሥሪያ ቤት ሲከፈት በአልዩ አምባ የጉምሩክ ጽሕፈት ቤት ሥራውን እንዲጀምር ተደርጎ ነበር። ስልክም ወደ ኢትዮጵያ እንደገባ ከእንጦጦ እስከ አልዩ አምባ ድረስ መስመር ተዘርግቶለት ነበር። አልዩ አምባ የተዳከመችው የባቡር ሐዲድ በከተማዋ ማለፍ ባለመቻሉና ወደ ድሬ ዳዋ በመዛወሩ መሆኑ ይነገራል። ዛሬ የአልዩ አምባ ገበያ አብዛኛዎቹን አርጎባዎች ይዞ የአፋርንና አማራ ብሔረሰቦችን ያገናኛል።
  • ሳላይሽ የጦር መሳሪያ ግምጃ ቤት - (ኮረማሽደብረ ብርሃን ወደ አዲስ አበባ ዋናውን መንገድ ተከትሎ አምሣ አራት ኪሎ ሜትር ከተጓዙ በኋላ ሐሙስ ገበያ ላይ ወደግራ በመታጠፍ አሥራ ሦሥት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የኮረማሽ ከተማ ይገኛል። የዳግማዊ ምኒልክ የመሳሪያ ግምጃ ቤቶች፣ አሰራራቸው የዕንቁላል ቅርጽ የሆነ አስራ አራት ሕንጻዎች አሉ። ቤቶቹ ከአድዋ ድል ማግስት ለጦር መሣሪያ ማከማቻነት ተብለው የተሰሩ ሲሆን የቦታው የተፈጥሮ አቀማመጥ የጐብኝን ቀልብ ይስባል። የጦር መሣሪያ ግምጃ ቤቶቹ ቀደም ሲልም ለአፈንጋጭ ባለሥልጣናት እስር ቤት በመሆን አገልግለዋል። ከእስረኞቹ መካከልም ልጅ ኢያሱ ይጠቀሳሉ።
  • የአቡኑ ከተማ ሰላ ድንጋይ - ከደብረ ብርሃን በስተሰሜን ሰባ ሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች። ለሠላሳ ስምንት ዓመታት የኢትዮጵያ ፓትሪያርክ የነበሩት ግብፃዊው አቡነ ማቴዎስ መንበረ ጵጵስናቸው በዚችው በሰላ ድንጋይ ነበር። በ፲፰፻፸፭ ዓ/ም እሳቸው ያሠሩት የሰላ ድንጋይ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን በመብረቅ አደጋ ቢፈርስም እንደገና በ፲፱፻ ዓ/ም በዳግማዊ ምኒልክ ልዩ ትዕዛዝ ተሠርቶ ምኒልክ ባሉበት በአቡኑ ተባርኳል። የቤተክርስቲያኑ ሕንፃ የውስጥ አሠራር ውበት ዓይንን የሚማርክና የዘመኑን የሕንፃ ሥራ ልዩ ችሎታ የሚመሰከር ነው። በውስጡም ከግብጽ የመጣውን የአቡነ ማቴዎስ መቀመጫ ጨምሮ በርካታ የታሪክና የባህል ቅርሶች ይገኙበታል።

ሰላ ድንጋይ የንጉሥ ሣህለ ሥላሴ የትውልድ ሥፍራም ናት። በእናታቸው በወይዘሮ ዘነበወርቅ እንደተሰራችና በስማቸውም የምትጠራው ሰገነት ከተሰራች ብዙ ዘመናት አስቆጥራለች። ሰላ ድንጋይ የአብዛኛዎቹ የሸዋ ነገሥታት ሚስቶችና እቁባቶች መቀመጫ ስለነበረች የወይዘሮዎች ከተማ በመባልም ትታወቃለች።

  • ባልጭ አማኑኤል ቤተ ክርስቲያን - የሚገኘው ከደብረ ብርሃን ፪፻፷ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምንጃር ሸንኮራ ወረዳ ባልጭ ከተማ ነው። ቤተ ክርስቲያኑ የተመሠረተው በ፲፮ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በዓፄ ገላውዲዎስ ሲሆን ዳግማዊ ምኒልክ በ፲፰፻፸ዎቹ አሳድሰውታል።

በቅድስቱ ግድግዳ ላይ የተሳሉት ጥንታዊ የፈትል ስእሎች ከመንፈሳዊ መግለጫነት ባሻገር ደጃዝማች ምኒሊክ በልጅነታቸው በዓፄ ቴዎድሮስ ሲማረኩ፣ በ፲፰፻፶፯ ዓ.ም ከመቅደላ ሲያመልጡና በኋላም በፍቼ ከተማ ከዓፄ ዮሐንስ ጋር ያካሄዱትን ስምምነት የሚገልጹ ናቸው። በመካነ ፈውስነቱ በአገራችን ስሙ እየገነነ የመጣው የሸንኮራ ዮሐንስ ፀበልም የሚገኘው ከባልጭ ከተማ የአሥራ አምስት ደቂቃ የእግር ጉዞ በኋላ ነው። ፀበሉ ቀደም ሲል በሽተኞችን ያድን እንደነበር ይነገር እንጅ ቀሳውስትና የፀበሉ አስተዳዳሪዎች ግን ከ፲፱፻፶፯ ዓ.ም ጀምሮ ዝናው እንደታወቀ ይናገራሉ። ፀበሉ የሚገኝበት አካባቢ ዳገታማና ቁልቁለት በመሆኑ ከአዲሱ ዩሐንስ ቤተ ክርስቲያን ሕንፃ አጠገብ ሆኖ ሲመለከቱት የአካባቢውን አስደናቂ መልክአ ምድራዊ አቀማመጥና በተፈጥሮ ውበት የታደለውን የመስህብ ሥፍራ ማየት ያስደስታል።

  • ወፍ ዋሻ ደን - በሰሜን ሸዋ ከሚገኙ የተፈጥሮ መስህብ ስፍራዎች መካከል የወፍ ዋሻ ደን አንዱ ነው። ደኑ አምስት ወረዳዎችን፡- ጣርማበር፣ ቀወትን፣ አንኮበርን፣ ላሎማማንና ጌራቀያን የሚያካልል ሲሆን አሥራ ሰባት ሺህ ሄክታር የሚጠጋ የቆዳ ስፋት አለው። ደኑ ጎሽ ሜዳ፣ ወፍ ዋሻና ጓሳ በተባሉ የጉብኝት ሥፍራዎች የተከፋፈለ ነው።
  • የጣርማ በር ዋሻ - ሰው ሰራሽ የሆነው የጣርማ በር ዋሻ የወፍ ዋሻ ደን አካል ነው። ከ፲፱፻፳፱ ዓ/ም እስከ ፲፱፻፴፪ ዓ/ም ባሉት ዓመታት በኢጣልያኖች የተሠሩት የጣርማ በር ዋሻዎች ሶስት ሲሆኑ ትልቁ የ ፮፻፵፪ ሜትር ርዝመት አለው። የአገራችን ረጅሙ የመሬት ውስጥ መንገድ ከመሆኑም በተጨማሪ ሰሜን ኢትዮጵያን ከደቡብ ጋር የሚያገናኝ ዋና ጐዳና ነው።
  • የጐዜ መስጊድ - ከደብረ ብርሃን ከተማ ፺፫ ኪሎ ሜትር ርቃ ከምትገኘው የሸዋሮቢት ከተማ በስተ ምዕራብ ላይ ይገኛል። የጐዜ መስጊድ በ፲፭ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የይፋት ስርወ መንግሥት ከፍተኛ ደረጃ በደረሰበት ዘመን ከተሠሩት አርባ መስጊዶች ውስጥ አንዱና የመጨረሻው መሆኑ ይነገራል። ከ፭፻ ዓመታት በላይ እድሜ እንዳለው የሚነገርለት ይህ መስጊድ አሠራሩ አራት ማዕዘን ሲሆን ግድግዳውና ጣራው ባልተጠረቡ ድንጋዮች የተገነባ ነው። የድንጋዩን ክዳን የተሸከሙት አራት አግዳሚ የጣውላ ወራጆች ሲሆኑ ምሰሶዎቹ አራት ናቸው። መስጊዱ የአርጐባ መንደሮች በስተግርጌው አድርጎ ከኮረብታ ላይ ይገኛል። በዙሪያው ጥንታዊ የመቃበር ሥፍራ፣ የድሮ ነዋሪዎች የውሃ ማጠራቀሚያ ጉድጓዶች እንዲሁም በውስጥ የቆዩ የሃይማኖቱ መሪዎች አራት ጦሮች አሉ። ቀደም ሲል በመስጊዱ ዙሪያ የአርጐባ ማኅበረሰብ አባላት ይኖሩ የነበረ ሲሆን አሁን ግን ኮረብታውን ለቀው ከግርጌው መንደራቸውን መሥርተው ይኖራሉ። ይሁን እንጅ ዛሬም ቢሆን መስጊዱ ዋነኛ የእምነት ቦታቸው ነው። በታላቁ ስምጥ ሸለቆ ውስጥ የሚገኘው ይህ መስጊድ የአርጐባን ብሔረሰብና በአካባቢ ያለውን ውብ የተፈጥሮ መስህብ በስተግርጌው አድርጎ ሲታይ ዓይንን ይማርካል።
  • የሙሽራ ድንጋዮች - በተለምዶ የሙሽራ ድንጋዮች በመባል የሚታወቁት ትክል ድንጋዮች ከአጣዬ ከተማ በምዕራብ በኩል ፳፩ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ልዩ ሥፍራው ገድሎ ሜዳ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ይገኛሉ። ገድሎ ሜዳ ደጃዝማች ምኒልክ፲፰፻፶፯ ዓ.ም ከመቅደላ እስር ቤት አምልጠው ሲሄዱ በምትካቸው በዓጼ ቴዎድሮስ ተሹመው ከነበሩት አቶ በዛብህ ጋር ጦርነት ያደረጉበት ሥፍራ ነው። ጦርነቱም በዓፄ ምኒልክ አሸናፊነት ተጠናቋል።

“ሙሽራ ድንጋዮች” በገድሎ ሜዳ ምዕራባዊ ዳርቻ ላይ የሚገኙ የሰው ቅርጽ ያላቸው ትክል ድንጋዮች ናቸው። ትክል ድንጋዮቹ ቆመውና ካሉበት ሳይነሱ የሚገኙ ፳፩፣ በሥፍራው ወድቀው የሚገኙ ፪፣ ከሥፍራው ተነስተው ገበሬዎች ለእርሻ ድንበር መለያ የተጠቀሙባቸው ፵፬ ናቸው። የሙሽራ ድንጋዮች ስያሜቸውን ያገኙበት በአንድ ወቅት በመንገድ ላይ እያሉ ሙሽሮችና ሠርገኞች ባደረጉት ከልክ ያለፈ ጭፈራ እግዚአብሔርን በማሳዘናቸው ተረግመው ወደ ቤታቸው ሳይመለሱ ወደ ድንጋይነት ተቀይረው በዚያው እንደቀሩ ይነገራል።

የሙሽራ ድንጋዮች ታሪካዊ አመጣጥ ከላይ በተገለጸው አኳኋን የተለየ ጥንታዊ ሰዎች ለአንድ ዓላማ ያቆሟቸው ትክል ድንጋዮች ናቸው ተብሎ ይታመናል። ምናልባትም ከአክሱም ዘመን በፊት ጀምሮ ሲያያዝ የመጣ የእደ ጥበብ ውጤት እንደሆነ ይገመታል። የሙሽራ ድንጋዮች በአብዛኛው ከደቡብ ኢትዮጵያ የጥያ ትክል ድንጋዮች ጋር ተመሳሳይነት አላቸው። እነዚህ ምስጢርን ያዘሉ የታሪካችን አሻራዎች ለጥናትና ምርምር የሚጋብዙና ለተመልካች ደግሞ የሚያዝናኑ ናቸው።