ደብረ ብርሃን

ከውክፔዲያ
(ከደብረብርሃን የተዛወረ)
ደብረ ብርሃን
አገር  ኢትዮጵያ
ክልል አማራ ክልል
ዞን ሰሜን ሸዋ
ከፍታ 2,840 ሜትር
የሕዝብ ብዛት
   • አጠቃላይ 50,780
ደብረ ብርሃን is located in ኢትዮጵያ
{{{alt}}}
ደብረ ብርሃን

9°41′ ሰሜን ኬክሮስ እና 39°32′ ምሥራቅ ኬንትሮስ

ደብረ ብርሃንሸዋ ክፍለ ሀገር የጅሩ ሸዋ ሜዳ ተጉለትና ቡልጋ አውራጃ ዋና ከተማ ናት። ከተማዋ የሰሜን ሸዋ ዞን (አውራጃ) አስተዳደር ርዕሰ ከተማ ከመሆኗ ባሻገር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስም ዋና ጽሕፈት ቤት እዚሁ ይገኛል።

፲፱፻፺፰ ዓ/ም ማዕከላዊ የስታትስቲክስ ባለስልጣን እንደተመነው ደብረ ብርሃን ከተማ የ፷፯ ሺህ ፪፻፵፫ ሰው መኖሪያ ስትሆን ከነሱም ፴፬ ሺህ ፶፭ ወንዶችና ፴፫ ሺህ ፻፹፰ ሴቶች ይገኙባታል ይላል።[1]

በሌላ ገለልተኛ የግምት ትመና ደግሞ ከተማዋ የ፶፯ ሺህ ፯፻፹ ሕዝብ መኖሪያ እንደሆነች ተገምቷል። የከተማዋ አቀማመጥ በ9°41′ ሰሜን ኬክሮስ እና 39°32′ ምሥራቅ ኬንትሮስ ላይ ነው።[2]

ደብረ ብርሃን ከአዲስ አበባ ፻፴ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በደሴ መስመር ላይ የምትገኝ ስሆን ፱ የአስተዳደር ቀበሌዎችም አሏት። የአየር ንብረቷ ደጋማ ነው። የተቆረቆረችውና ስያሜዋን ያገኘችው ደግሞ በ፲፬፻፵፮ ዓ/ም አካባቢ በዓፄ ዘርአ ያዕቆብ (፲፬፻፴፬-፲፬፻፷፰) ነበር። ከተማዋ ድሮ የንጉሡ የግራ በአልቴሃት (ግራ በአልቴሃት ከንጉሡ ሦሥት ሚስቶች የአንደኛዋ የክብር ስም ነው) ርስት ነበረች። በ፲፬፻፵ዎቹ መጀመሪያ አጤው ከእንደግብጣን ወጨጫ ተራራ ማለትም ከአዲስ አበባ በስተምዕራብ ከነበረው ያባታቸው አጤ ዳዊት መናገሻ ሥፍራ ተነስተው ሲጓዙ በአካባቢው ውበት ስለተደሰቱ የድንኳን ከተማቸውን ከተሙባት። በኋላም ቤተ መንግሥት አሳንፀውና ባለወርቅ ጉልላት የነበረውን የሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አሰርተው ቆረቆሯት። "ተአምረ ማርያም" የተሰኘ የጥንት ድርሳን የከተማዋን ስያሜ ከአንድ ተአምራዊ ሁነት ጋር አያይዞ ይገልፀዋል። በ፲፬፻፵፮ ዓ/ም በክርስትና ሃይማኖት ካህናትና በጥቂት የሃይማኖቱ ተከራካሪዎች መካከል ክርክር ይነሳል። ንጉሡና የካህናቱ አለቆች በተገኙበት አንድ ዕለት በጉባዔ ክርክሩ ተካሄደ። በመጨረሻም «እስጢፋኖሳውያን» በሚል መጠሪያ የሚታወቁት ተከራካሪዎች አቋማቸውን እንዲያስተካክሉ ተጠይቀው አሻፈረን በማለታቸው ከፍተኛ ቅጣት ይደርስባቸዋል።

ይህ በሆነ በ፴፰ኛው ቀን በመጋቢት ፲ ቀን 1446|፲፬፻፵፮ ዓ/ም ረዘም ላለ ጊዜ / ምናልባትም ለቀናት/ የቆየ ቦግ ያለ ብርሃን ከሰማይ ይወርዳል። የብርሃኑ መውረድ ለእስጢፋኖሳውያን ስህተተኛነት ለካህናቱ ደግሞ ትክክለኛነት ምስክር ነው በሚል ተተርጉሟል። ስለዚህ ብርሃን መውረድ የንጉሡ ዜና መዋዕልም ያትታል። በዚህ ሳቢያ ንጉሡ የሥፍራውን ስም ደብረ ብርሃን /የብርሃን አምባ/ በማለት ሰይመውታል።

ይህ መንግስቱ ያመነበት ነግር ነው በብዙዎች ዘንድ የሚታመነው እውነታ ግን በዚያ ግዜ የነበሩ ደቂቀ እስጢፋኖሳውያን እውነተኛውን ኃይማኖት አንክድም ለስዕል አንሰግድን ማለታቸው ነበር ንጉሱን ያስቆጣው

በዚህም ምክንያት ነበር ንጉሱ እስጢፋኖሳውያን እስከ እንገታቸው እንዲቀበሩና በላያቸው የፈረስ ሰራዊት ሄዶባቸው በአሰቃቂ ሁኔታ እንዲገደሉ ያዘዘው.

ከዚህም የተነሳ የመጣው መብረቅ የመሰለ አስፈሪ ብርሀን

የመጣው የእግዚእብሔር ቁጣ ነበር እንጂ ደስታው አልነበም።

ዓፄ ዘርአ ያዕቆብ ከንግሥና ዘመናቸው ፲፬ ዓመታት የሚሆነውን በደብረ ብርሃን ከተማ እንዳሳለፉና አብዛኛዎቹን የሃይማኖትና የፍልስፍና ድርሰቶቻቸውን የፃፉት በዚሁ ከተማ መሆኑ ይነገራል። በዘመኑም ደብረ ብርሃን ከፍተኛ የትምህርት ማዕከል የነበረች ሲሆን በንጉሡ ትእዛዝ በርካታ የሃይማኖት መፃሕፍት የትርጉም ሥራ ተከናውኖባታል።

በዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት የኣዲስ ኣበባ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ሲጣበቡ ለሸዋ ጠቅላይ ግዛት ተማሪዎች እንዲያገልግል ኃይለ ማርያም ማሞ ፪ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ደብረ ብርሃን ተሠራ። ለመጀሪያዎቹ ስድስት ዓመታት ለተማሪዎቹም መጀመሪያ በየወሩ ፳ ብር በኋላም ፲፭ ብር እየተፈልላቸው ነበር የተማሩት። ከምሩቃኖቹም መካከል ዶ/ር ኣበራ ሞላ ታላቅ ወንድማቸው ዶክተር በቀለ ሞላና ታናሽ ወንድማቸው ጌታቸው ሞላ ይገኙበታል።

ማጣቀሻዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ ማዕከላዊ የስታትስቲክስ ባለስልጣን Archived ኦገስት 13, 2007 at the Wayback Machine, population.pdf
  2. ^ Butler, Rhett A., 2005 population estimates for cities in Ethiopia

ምንጭ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  • የአማራ ብሔራዊ ክልል፤ ባህል፣ ቱሪዝምና ማስታወቂያ ቢሮ፤ “የአማራ ክልል የቱሪስት መስህብ ሃብቶች (አጭር ቅኝት)”፤ አርቲስቲክ ማተሚያ ድርጅት (፲፱፻፺፩ ዓ/ም)