የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት

ከውክፔዲያ
አፍሪቃ አንድነት ድርጅት ዓርማ

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (አ.አ.ድ.) (እንግሊዝኛ፡ Organisation of African Unity (OAU))፣ (ፈረንሳይኛ፡ Organization de l'Unité Africaine (OUA))ግንቦት ፲፯ ቀን ፲፱፻፶፭ ዓ/ም አዲስ አበባ ላይ ተመሥርቶ የድርጅቱ መመሪያ ውል (OAU Charter) በ፴፪ቱ መሥራች አገር መሪዎች ጸድቆ ተፈርሟል። የድርጅቱም ጠቅላይ መሥሪያ ቤቱ በአዲስ አበባ እንዲቆይ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ባቀረቡት ግብዣ መሠረት እስካሁን ድረስ እዚያው አዲስ አበባ ላይ ይገኛል። ይህ ድርጅት በ፲፱፻፺፬ ዓ/ም ተደምስሶ የአፍሪካ ኅብረት በሚባለው ድርጅት ተተክቷል።

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በመሰብሰቢያው አዳራሽ የሚገኘው በአሰፋና ሠረቀ የማነብርሃን የተሣለ የ፴፪ቱ መሥራች መሪዎች ምስል።

ለብዙ ሺ ዓመታት ኢትዮጵያ ብቻዋን በአኅጉሩ ውስጥ ከአውሮፓውያኖች የቅኝ ግዛት ቀንበር ውጪ ቆይታ የሙሶሊኒ ፋሺስት ኢጣልያ፲፱፻፳፰ ዓ/ም ወርራት በነበረ ጊዜ አርበኞች ልጆቿ ውድ አገራቸውንና ነጻነታቸውን አሳልፈው ላለመስጠት አምስት ዓመታት ሙሉ ተዋጉ። ንጉሠ ነገሥታቸውም የእዚህን የግፍ ወረራ ለማጋፈጥ በዓለም መንግሥታት ማኅበር መድረክ ላይ ሲቀርቡ፣ ከአፍሪቃ አኅጉር ብቸኛዋ አባል ኢትዮጵያ ማንም አጋዥ አገር አልነበራትም።

ለአኅጉሩ ነጻነት በቅኝ ግዛት ሥርም የነበሩት ሕዝቦች፤ በነጻነትም ላይ የነበሩት አገራት የአውሮፓውያንን መዥገራዊ ልጥፍነት ለማላቀቅ ብዙ ከታገሉ በኋላ በሰሐራዊ አፍሪቃ የካቲት ፳፯ ቀን ፲፱፻፵፱ ዓ/ም ጋና ነጻ ሆነች። ከዚያ አስከትሎ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት እስከተመሠረተ ድረስ በ፲፱፻፶፩ ዓ/ም ጊኒ ነጻ ስትሆን በ ፲፱፻፶፪ ዓ/ም አሥራ አምስት አገራት፤ በ፲፱፻፶፫ ዓ/ም ሦሥት አገራት፤ በ፲፱፻፶፬ ዓ/ም ደግሞ አራት አገራት ነጻነታቸውን ተቀዳጁ።

የአኅጉሩ መሪዎች በዓለም መድረክ ላይ ለበለጠ ተሰሚነት የትብብርን ግንባር ማሳየት እንደነበረባቸው በመገንዘብና ገና ነጻ ላልወጡትም ወንድም አገሮች ሉዐላዊነት መታገል ስለነበረባቸው ዓላማቸውን ግብ ለማድረስ በሁለት ቡድን ተከፍለው ፣ ባንድ በኩል እራሱን “የዘመናዊ ተራማጅ” ብሎ የሚጠራው፣ በጋናው ፕሬዚደንት ክዋሜ ንክሩማ የሚመራው የ “ካዛብላንካ ቡድን” በ ፲፱፻፶፬ ዓ/ም ተመሠረተ። ይሄ ቡድን የአኅጉሩን መንግሥታት በኅብረት ለማዋሃድ ዓላማ የያዘ ሲሆን አባላቱ ጋናአልጄሪያጊኒሞሮኮግብጽማሊ እና ሊቢያ ነበሩ።

ሁለተኛው ቡድን የ”ሞንሮቪያ ቡድን” ሲሆን የተመራው በ ሴኔጋል ፕሬዚደንት ሊዮፖልድ ሴዳር ሴንግሆር ነበር። አባላቱ ሴኔጋልናይጄሪያላይቤሪያ እና ኢትዮጵያ ሲሆኑ የነሱ የኅብረት አስተያየት ደግሞ የዱኛ ኅብረት ሳይሆን ፍላጎታቸው ረጋ ባለ ሁኔታ የዱኛኪን ኅብረት አንድነትን ያስከትላል የሚል ነበር።

መጨረሻ ላይ በኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ከተማ ይፍሩ ታላቅ ጥረትና በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድጋፍ ሁለቱም ወገኖች አዲስ አበባ ላይ እንዲገናኙ በተደረገው ጥሪ መሠረት ተሰባስበው የአፍሪቃ አንድነት ድርጅትን የስምምነት ውል ፴፪ ነጻ ሀገሮች ሲፈርሙ ድርጅቱ ተመሠረተ።

፴፪ቱ መሥራች መሪዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የካዛብላንካ ቡድን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ጋና[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ክዋሜ ንክሩማ

የካቲት ፳፯ ቀን ፲፱፻፵፱ ዓ/ም ነጻነቷን በዶክቶር ክዋሜ ንክሩማ መሪነት ከብሪታንያ የተቀዳጀችው ጋና በዚህ በመጀመሪያው የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት የምሥረታ ስብሰባም የተወከለችው በኒህ ታላቅ መሪ ነበር።

ዶክቶር ንክሩማ የ”ካዛብላንካ ቡድን” መሪ ሲሆኑ በሽከታ ኅብረት (pan-Africanism) የሚባለው ፍልስፍና ምንጭ እንደነበሩ ይገመታል።

ሞሮኮ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ንጉሥ ሀሰን

ሞሮኮእስከ መጋቢት ፳፱ ቀን ፲፱፻፵፰ ዓ/ም ድረስ በፈረንሳይ ሥር ነበረች። ከነጻነት ወዲህ መሪዋ ግርማዊ ዳግማዊ ሀሰን የሞሮኮ ንጉሥ በጋናው ፕሬዚደንት ክዋሜ ንክሩማ የሚመራው የ “ካዛብላንካ ቡድን” በ ፲፱፻፶፬ ዓ/ም በካዛብላንካ ከተማቸው እንዲመሠረትና

በዓላማው እንዲገፋበት ጥረዋል። ወደፊትም በ ሞሮኮ ሥር በምትገኘው ሰሐራዊ የአረብ ዴሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ ነጻነት ምክንያት ከድርጅቱ ጋር በተፈጠረው አለመግባባት አግራቸውን ከአባልነት አስወግደዋል።

አልጄሪያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አህመድ ቤንቤላ

አልጄሪያ የነጻነት ትግል ፲፱፻፵፮ ዓ/ም በጦርነት ሲጀመር የነጻነት አውጪ ግንባር ዓባል የነበሩት አህመድ ቤንቤላ አገሪቱ ነጻነቷን ከፈረንሳይ ሰኔ ፳፮ ቀን ፲፱፻፶፬ ዓ/ም ስትቀዳጅ በመሪነት የፕሬዚደንትነቱን ሥልጣን ጨበጡ።

ግብጽ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ጋማል አብደል ናስር

ጋማል አብደል ናስር ከመጀመሪያው የግብጽ ፕሬዚደንት ሙሐመድ ናጊብ ጋር በ፲፱፻፵፬ ዓ/ም የወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት አካሂደው ንጉሡን ቀዳማዊ ፋሩክን ገለበጡ።

ናሰር የፕሬዚደንትነቱን ሥልጣን በ፲፱፻፵፰ ዓ/ም ሲጨብጡ የአገሪቱ ሁለተኛው ፕሬዚደንት በመሆን እስከ ዕለተ ሞታቸው፣ መስከረም ፲፰ ቀን ፲፱፻፷፫ ዓ/ም ድረስ አገልግለዋል።

ማሊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሞዲቦ ኬይታ

ባማኮ ከተማ ላይ ግንቦት ፳፯ ቀን ፲፱፻፯ ዓ/ም የተወለዱት ሞዲቦ ኬይታ አገራቸው ማሊ ነጻነቷን ከፈረንሳይ ሰኔ ፲፫ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ስትቀዳጅ የፕሬዚደንትነቱን ሥልጣን ጨብጠው እስከ ፲፱፻፷ ዓ/ም አገልግለዋል።

ሊቢያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ንጉሥ ኢድሪስ

ሊቢያ ሉዓላዊ እና ነጻ፣ በሕገ መንግሥት የሚተዳደር የዘውድ ሥርዐተ መንግሥት ታኅሣሥ ፲፬ ቀን ፲፱፻፵፬ ዓ/ም ላይ ስታውጅ በንጉሥ ኢድሪስ መሪነት ነበር። የአፍሪቃ አንድነት ድርጅትም ሲመሠረት አዲስ አበባ ላይ በመሳተፍ ውሉን የፈረሙት እኒሁ ንጉሥ ኢድሪስ ነበሩ።

በኋላ በነሐሴ ፳፮ ቀን ፲፱፻፷፩ ዓ/ም በሀያ ሰባት ዓመቱ ወጣት መኮንን፣ ሙአማር ጋዳፊ የተመራ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ንጉሡን ቱርክ አገር በህክምና ላይ እንዳሉ ከሥልጣን አወረዳቸው። ንጉሥ ኢድሪስ በግንቦት ፲፱፻፸፭ ዓ/ም ካይሮ ላይ አረፉ።

ጊኒ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሴኩ ቱሬ

ጊኒ ነጻነቷን ከፈረንሳይ መስከረም ፳፪ ቀን ፲፱፻፶፩ ዓ/ም ተቀዳጀች። የአገሪቷ የመጀመሪያ ፕሬዚደንት ሴኩ ቱሬ ሲሆኑ በ ፲፱፻፸፮ ዓ/ም እስከሞቱ ድረስ በዚሁ ሥልጣን ቆይተዋል።

የሞንሮቪያ ቡድን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ኢትዮጵያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ቀ. ኃ. ሥ.

ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት : የስብሰባው አስተናጋጅና የተከፋፈሉትን ሁለት ቡድኖች በማስተባበር አንድ ድርጅት እንዲመሠረት ያደረጉ መሪ ሲሆኑ፤ የማኅበሩም የውል

ረቂቅ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትራቸው በአቶ ከተማ ይፍሩ ትጋትና ድካም ተዘጋጅቶ እንዲፈረም አድርገዋል። በአብዝኛው ዓለም አቀፍ አስተያየት “የአፍሪካ አባት” የሚል ስምም አትርፎላቸዋል።


ላይቤሪያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ዊልያም ተብማን

ክቡር ፕሬዚደንት ዶክቶር ዊሊያም ተብማን፦ የላይቤሪያ ፕሬዚደንት እና ሁለተናውን በ ሴኔጋል ፕሬዚደንት ሊዮፖልድ ሴዳር ሴንግሆር የሚመራውን “የሞንሮቪያ ቡድን” መሥራች ሲሆኑ

አገራቸው ደግሞ ሐምሌ ፳ ቀን ፲፰፻፴፱ ዓ/ም በአሜሪካ ነጻ በወጡ የቀድሞ ግሎሌዎች (የግድ ሎሌ) ወይም ‘ባርያዎች’ ከተመሠረተች በኋላ በአፍሪቃ አኅጉር በነጻነት ዕድሜ ከኢትዮጵያ ተከትላ ሁለተኛዋ አገር ናት።

ሴኔጋል[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሊዮፖልድ ሴንግሆር

ሴኔጋል እስከ መጋቢት ፳፮ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም የፈረንሳይ ቅኝ ግዛት ነበረች። በዚያን ዕለት ነጽ ስትወጣ፣ በሥነ ጽሁፍ እና ቅኔ ባለሙያነታቸው የሚታወቁት መሪ እና “የሞንሮቪያ ቡድን” የሚባለውን ሁለተኛውን ቡድን የመሩት ሊዮፖልድ ሴጋር ሴንግሆር ነበሩ።


ናይጄሪያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ታፌዋ ባሌዋ

የቀድሞዋ የብሪታንያ ቅኝ ግዛት ናይጄሪያ መስከረም ፳፩ ቀን ፲፱፻፶፫ ዓ/ም ነጻነቷን ስትቀዳጅ የመጀመሪያውም የመጨረሻውም ጠቅላይ ሚንስትር የነበሩት አል ሃጅ አቡባካ ታፌዋ ባሌዋ ነበሩ። ባሌዋ በአስተማሪነት የሠለጠኑ ሲሆን በሥልጣን ጊዜያቸው ደግሞ ስለአፍሪቃ ራሷን በራሷ የማስተዳደር መብት ብዙ የታገሉ ከመሆናቸውም ባሻገር ለአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ምሥረታ ብዙ ጥረት አድርገዋል። በፈረንሳይኛ እና እንግሊዝኛተናጋሪ አገሮች መሃል ስምምነትና ወዳጅነት እንዲፈጠርም አመቻችተዋል።

መጨረሻ ላይ በአገራቸው በተካሄደ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ጥር ፯ ቀን ፲፱፻፶፰ ዓ/ም ተገደሉ። እሬሳቸውም በተገደሉ በስድስተኛው ቀን በሌጎስ ከተማ መንገድ ዳር ላይ ተጥሎ ተገኘ።

ቡድን ያልለዩ ዓባላት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ዳሆሜ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሁበርት ማጋ

የቀድሞዋ ዳሆሜ (አሁን ቤኒን) ነጻነቷን ሐምሌ ፳፭ ቀን ፲፱፻፶፪ፈረንሳይ ስትቀዳጅ ሁበርት ማጋ የአገሪቱ የመጀመሪያው ፕሬዚደንትነትን ሥልጣን ይዘው ወዲያው በታኅሣሥ ወር ላይ በተካሄደ ምርጫ ጸደቀላቸው።

ቱኒዚያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሀቢብ ቡርጊባ

ቱኒዚያን ሪፑብሊክ መጋቢት ፲፩ ቀን ፲፱፻፵፰ ዓ/ም በነጻነት የመሠረቱትና ከ ሐምሌ ፲፱ ቀን ፲፱፻፵፱ ዓ/ም ጀምሮ ለሠላሳ ዓመታት እስከ ጥቅምት ፴ ቀን ፲፱፻፹ ዓ/ም ድረስ በፕሬዚደንትነት ያገለገሉት ሀቢብ ቡርጊባ ነበሩ።

ካሜሩን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አማዱ አሂጆ

ከነጻነት [[ታኅሣሥ ፳፪] ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ጀምሮ ለሀያ ሁለት ዓመታት እስከ ኅዳር ፳፩ ቀን ፲፱፻፹፪ ዓ/ም አገራቸውን ካሜሩንን በፕሬዚደንትነት የመሩት አማዱ ባባቱራ አሂጆ ነበሩ።


ቻድ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ፍራንስዋ ቶምቦልባይ

አስተማሪና የሠራተኞች ማኅበር ቀስቃሽ የነበሩት ፍራንስዋ ቶምቦልባይ መጀመሪያ በቅኝ ግዛት ሥር የአስተዳደሩ ርዕስ በመሆን ቻድ ነሐሴ ፭ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ከፈረንሳይ ነጻነቷን ስትቀዳጅ የአገሪቱ የመጀመሪያው ፕሬዚደንት ሆኑ። ቶምቦልባይ በተወለዱ በ፶፯ ዓመታቸው ሚያዝያ ፭ቀን ፲፱፻፷፯ ዓ/ም አረፉ።

ቶጎ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሲልቫኑስ ኦሊምፒዮ

የምዕራብ አፍሪቃቶጎፈረንሳይ የቅኝ ግዛትነት ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ነጻ ስትወጣ ሲልቫኑስ ኦሊምፒዮ መጀመሪያ በጠቅላይ ሚኒስትርነት ከዚያም በፕሬዚደንትነት አገልግለዋል። ጥር ፭ ቀን ፲፱፻፶፭ ዓ/ም በተነሳ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት በጥይት ተገደሉ።

ሶማሊያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አብዲራሺድ ሸርማርክ

ሶማልያ ሪፑብሊክ በብሪታንያ ስር በሙሀመድ ሃጂ ኢብራሂም ኤጋል ይተዳደር የነበረውን ክፍልና በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ስም በኢጣልያ ስር በአደን አብዱላ ኦስማን ዳር መሪነት ይተዳደር የነበረውን ክፍል በማዋሃድ ሰኔ ፳፫ ቀን ፲፱፻፶፫ ዓ/ም ተመሠረተ። በቀድሞው የኢጣልያ የቅኝ ግዛት በመንግሥት ሠራተኛነት ሲያገለግሉ የነበሩት ክቡር ዶክቶር አብዲራሺድ አሊ ሸርማርክ የአገሪቱ የመጀመሪያ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኑ።


አይቮሪ ኮስት (ኮት ዲቯር)[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ፌሊክስ ሁፍዌ ቧኝ

ሕዝባቸው ባቆላማጭ መንፈስ “አባባ ሁፍዌ” ይላቸው የነበሩት አንጋፋው ፌሊክስ ሁፍዌ ቧኝ በ፲፰፻፺፯ ዓ/ም ተወለዱ። በፈረንሳይ የሕግ ምክር ቤት አባልነት ከመረጣቸው በፊት በልዩ ልዩ ግዜያት የመንደር ዓለቃ፣ የህክምና ዶክቶር፣ የእርሻ አስተዳዳሪ እና የሠራተኞች ማኅበር ዓለቃ በመሆን አገልግለዋል። በፈረንሳይ መንግሥትም በልዩ ልዩ ክፍሎች በሚኒስትርነት አገልግለዋል።

አገራቸው ከፈረንሳይ ግዛትነት ነሐሴ ፩ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ነጻ ከወጣች በኋላ በፖሊቲካ ዘመናቸው የአፍሪቃ አኅጉርን የቅኝ ግዛትነት ቀንበር ለማስለቀቅ ብዙ የደከሙ ሲሆን አገራቸውንም በፕሬዚደንትንት በመሩባቸው ዘመናት ራዕያዊ ዕቅዶችን በመተመንና የአገሪቱን ዋና ምርቶች የሆኑትን ኮኮ እና ቡና በማዳበር በምዕራብ አፍሪቃ የላቀ እድገትን አስገኝተዋል። ከምዕራባውያን ጋር የነበራቸው መልካም ግንኙነት እና ለኮሙኒስት ዓላማ የነበራቸው ጥላቻ በሌሎች የጎረቤት አገር መሪዎች ላይ የተነሱ የመፈንቅለ መንግሥት ሴራዎችን ይደግፉ ነበር እየተባሉ ይታማሉ።

ኬንያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ጆሞ ኬንያታ

ሲወለዱ የተሰጣቸው ስም “ካማው ዋ ንጌንጊ” ሲሆን በክርስትና ሲጠመቁ “ዮሐንስ ጴጥሮስ” ተብለው ነበር። በኋላ መጠሪያ ስማቸውን ጆሞ ኬንያታ ብለው ሰየሙ። ኬንያታ አገራቸው ኬንያ ለነጻነት በምትታገልበት ጊዜ ከ፲፱፻፵፭ ዓ/ም እስከ ፲፱፻፶፩ ዓ/ም ድረስ የተካሄደውን “ማው ማው” የተባለውን የአርበኝነት ግንባር መርተዋል። በዚህም ምክንይት በብሪታንያ አስተዳደር ታስረው ነበር።

“ምዚ” (አዛውንቱ) ጆሞ ኬንያታ በ፲፱፻፴፰ ዓ/ም ሎንዶን በነበሩ ጊዜ ከጋናክዋሜ ንክሩማ ጋር “የአፍሪቃ አኅጉር የሽከታ ኅብረት” (pan-Africanism) የተባለውን ፍልስፍና መሥርተው ያራምዱ ነበር። ከዘመናት በኋላ አገራቸው ኬንያታኅሣሥ ፪ ቀን ፲፱፻፶፮ ዓ/ም በአፍሪቃ ሠላሣ ሁለተኛዋ ነጻ አገር ሆና ሉዓላዊ ስትሆን፣ ኬንያታ መጀመሪያ በጠቅላይ ሚኒስትርነት ከአንድ ዓመት በኋላ ደግሞ በፕሬዚደንትነት እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ አገልግለዋል።


ኮንጎ ብራዛቪል[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አቤ ፉልበርት ያውሉ

አሁን ኮንጎ ሪፑብሊክ የምትባለው ኮንጎ ብራዛቪል ነሐሴ ፱ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ከፈረንሳይ የቅኝ ግዛት ቀንበር ተላቃ ነጻ ሉዐላዊ አገር ሆነች። በነጻነት ጊዜ አገሪቷን በመሪነት ሥልጣን ይመሩ የነበሩት ቀድሞ የካቶሊክ እምነት ቄስ የነበሩት አቤ ፉልበርት ያውሉ ነበሩ። ያውሉ በ፲፱፻፶፭ ዓ/ም መሪውን ፓርቲያቸውን ብቻ ሕጋዊ ፓርቲ ለማድረግ ሲነሳሱ ሕዝባቸው ይሄንን በመቃወም በነሐሴ ወር ላይ ባካሄደው የሦስት ቀን የተቃውሞ ሁከት ሥልጣናቸውን ለመልቀቅ ተገደዱ።


ጋቦን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ገብርኤል እምባ

የቀድሞዋ የፈረንሳይ የቅኝ ግዛት ጋቦን ነጻነቷን ነሐሴ ፲፩ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም አገኘች። በሽግግሩ ጊዜ በጠቅላይ ሚንስትርነት ከነጻነት በኋላ ደግሞ የአገሪቱ የመጀመሪያው ፕሬዚደንት በመሆን ያገለገሉት ገብርኤል እምባ ነበሩ።

ጋቦን ሽከታ ተዋናይነትን በ ፲፱፻፴፰ ዓ/ም የጀመሩት ፕሬዚደንት እምባ በ፲፱፻፶፮ ዓ/ም በዱኛ ባላጋራቸው ጃን ሂሌይር ኦባም ቀስቃችነት የተነሳውን የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ በፈረንሳይ እርዳታ ካከሸፉ በኋላ በ፲፱፻፶፱ ዓ/ም በፕሬዚደንትነት ተመርጠው ነበር። ዳሩ ግን በነበረባቸው የነቀርሳ በሽታ ምክንያት በኅዳር ወር በሞት ተለዩ።


ማዳጋስካር[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ፊሊበርት ጺራናና

ፊሊበርት ጺራናና በ፲፱፻፬ ዓ/ም የተወለዱ የማዳጋስካር ሽከተኛ ነበሩ። አገራቸውን በመሪነት ሰኔ ፲፱ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ለነጻነት ካበቁ በኋላ በፕሬዚደንትነት እስከ ፲፱፻፷፬ ዓ/ም ድረስ መርተዋል። በመሪነታቸው የ”ማዳጋስካር ሕብረተ-ሰብዓዊ ሽከታ” ("Malagasy socialism") በሚሉት የአስተዳደራቸው መመሪያ ብዙ ስህተቶችን እንደሠሩ ይዘገባል። ሆኖም በአገራቸው ስማቸው የተከበረ፣ እስካሁንም “የነጻነት አባት” የሚል ቅጽል ስም አስጥቷቸዋል።

ፕሬዚደንት ፊሊበርት ጺራናና በሚያዝያ ፰ ቀን ፲፱፻፸ ዓ/ም አረፉ።


ሞሪታንያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሙክታር ኡልድ ዳዳ

ሞሪታንያ ነጻነቷን ኅዳር ፲፱ ቀን ፲፱፻፶፫ ዓ/ም ከፈረንሳይ ተቀዳጀች። ከዚህ ጊዜ ጀምሮ በ፲፱፻፸ ዓ/ም በተካሄደ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት እስከተገለበጡ ድረስ ሞክታር ኡልድ ዳዳ አገራቸውን በፕሬዚደንትነት አገልግለዋል።

ፕሬዚደንት ኡልድ ዳዳ የአንድ ፓርቲ ሽከታን ብቻ ሕጋዊ አድርገው ተቃራኒ በሌለባቸው ሦሥት ምርጫዎች አሸንፌያለሁ ብለዋል። በ፲፱፻፷፫ ዓ/ም የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት (አ. አ. ድ.) ፕሬዚደንት ሆነው ነበር። ጥቅምት ፬ ቀን ፲፱፻፺፮ ዓ/ም አረፉ።

የመካከለኛው አፍሪካ ሪፑብሊክ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ዴቪድ ዳኮ

የመካከለኛው አፍሪካ ሪፑብሊክ የመጀመሪያውና ሦሥተኛው ፕሬዚደንት፣ በ፲፱፻፳፪ ዓ/ም የተወለዱት ዴቪድ ዳኮ ናቸው። ከፕሬዚደንትነቱ ሥልጣን ሁለቴም የወረዱት በወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ሲሆን፤ በአገራቸው ሽከታ ለግማሽ ምዕት ዓመት ተሳትፈዋል።

የመካከለኛው አፍሪካ ሪፑብሊክ ነጻነቷን ነሐሴ ፯ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ስትቀዳጅ፣ ጊዜያዊ ፕሬዚደንት ከሆኑ በኋላ በፈረንሳይ መንግሥት ድጋፍ እስከ ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ፲፱፻፶፯ ዓ/ም ድረስ በፕሬዚደንትነት ሲመሩ ቆይተው ጄኔራል ጃን ቢዴል ቦካሳ (በኋላ ንጉሠ ነገሥት) ስኬታም ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት አካሂደው ዳኮን ከሥልጣን አወረዷቸው።

ከአሥራ አምስት ዓመት አምባ ገነናዊ ግዛት በኋላ ንጉሠ ነገሥት ቦካሳ በፈረንሳይ ምርጥ ወታደሮች ኃይል ከሥልጣን ሲወርዱ ዴቪድ ዳኮ ለሁለተኛ ጊዜ የፕሬዚደንትነቱን ሥልጣን ጨበጡ። ሁለተኛው ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት በመስከረም ፲ ቀን ፲፱፻፸፬ ዓ/ም ተካሂዶ ዳኮን ለሁለተኛና መጨረሻ ጊዜ ከሥልጣን አወረዳቸው።

አፐር ቮልታ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሞሪስ ያሜዎጎ

ሐምሌ ፳፱ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ነጻነቷን ከፈረንሳይ የተቀዳጀችው አፐር ቮልታ (አሁን ቡርኪና ፋሶ) የመጀመሪያ ፕሬዚደንትነትን ሥልጣን የሰጠችው ለሞሪስ ያሜዎጎ ነበር።

ያሜዎጎ የአይቮሪ ኮስትን ፕሬዚደንት ፌሊሽ ሁፌ ቧኝ የቅርብ ወዳጅ እና በዕድሜያቸው እንደታላቅ ወንድም የሚያይዋቸው፣ መካሪያቸው እንደነበሩ ይነገራል። ያሜዎጎ መጀመሪያ በአይቮሪ ኮስት እና በአፐር ቮልታ መሃል የተዋህዶ መንግሥት ለመመሥረት ጥረው ስከታማ ሳይሆን ቀረ። በኋላ ደግሞ ይሄንን ዓላማ ለማራመድ በሴኔጋልማሊዳሆሚ እና አፐር ቮልታ መሃል በአንድ መንግሥት የሚመራ የኅብረት ውህደትን ለማግኘት ይለፉ ነበር። ዳሩ ግን በፕሬዚደንት ቧኝ እና በፈረንሳይ መንግሥት ተቃዋሚነት ይህን አሳብ ለመተው ተገደዋል።

ያሜዎጎ ከሥልጣን እስከወረዱበት ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ፲፱፻፶፰ ዓ/ም ድረስ ከቧኝ ጋር የሁለቱን አገር ሕዝቦች በመንታ ዜግነት ማስተዳደር የሚያስችል አሳብ ያራምዱ ነበር። እሳቸው ከሥልጣን ሲወገዱ ይሄም አሳብ አብሮ ወደቅ።

ሲዬራ ሊዮን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሚልተን ማርጋይ

ሲዬራ ሊዮን የመጀመሪያዋ ጠቅላይ ሚኒስትር “ሰር” (SIR) ሚልተን ማርጋይ አገራቸው የብሪታንያ ቅኝ ግዛት በነበረች ጊዜ የህክምና ዶክቶር በመሆን ከመመረቃቸውም ባሻገር በግዛቱ ላይ በተገዢው ሕዝብ ቁጥጥር ሥር የሆነውን የመጀመሪያ ጋዜጣ ያቋቋሙ ናቸው።

አገሪቷ ነጻነቷን ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፲፱፻፶፫ ዓ/ም ተቀዳጀች። እስከዚያም ጊዜ በቅኝ አስተዳደር ውስጥ በዋና ሚኒስትርነት ሲያገለግሉ የነበሩት እና አገራቸውንም ወደነጻነት የመሩት ማርጋይ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኑ። በዚህ ሥልጣን ላይ እንዳሉ በ፲፱፻፶፮ ዓ/ም በሞት ሲለዩ የተቅላይ ሚኒስትርነቱን ሥልጣን ወንድማቸው ወረሱ።

ታንጋኒካ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ጁልዬስ ኒዬሬሬ

“የምንገነባት አፍሪቃ ሌላው ዓለም አይቷት “ስለሕብረተ ሰብ ያላቸውን ህልም ግብ ያደረሱ ነጻ ሕዝቦችን ማየት ከፈለጋችሁ አፍሪቃ ሂዱ!” የሚሉላት መሆን አለባት። ለመላው የሰው ልጅ ሁሉ የተስፋ አኅጉር ማለት ይቺ ናት።”

መምህር ጁሊዬስ ኒዬሬሬ (፲፱፻፶፪ ዓ/ም)

ጁሊዬስ ካምባራጌ ኒዬሬሬ የብሪታንያን ጭቆና፣ የአገር ውስጥ መከፋፈልን እና የጊዜውን የ”ቀዝቃዛ ጦርነት” ሽከታ ተቋቁመው ኅዳር ፴ ቀን ፲፱፻፶፬ ዓ/ም አገራቸውን ታንጋኒካን በሰላም ወደነጻነት የመሩ ሲሆኑ የአገሪቱ የመጀመሪያው ፕሬዚደንት ነበሩ። ከዚህም ሌላ፣ አብላጫነት በሌላቸው ነጮች የሚተዳደሩትን የደቡባዊ አፍሪቃ አገሮችን የነጻነት ትግል በመደገፍ ግንባር ቀደም ነበሩ።

ኒዬሬሬ በ፲፱፻፲፬ ዓ/ም ተወለዱ። በትምህርት ስጦታ የነበራቸው ምሁር ሲሆኑ በከፍተኛ ትምህርት ከተመረቁ በኋላ በመምህርነት አገልግለዋል። የስዋሂሊ ቋንቋ ለአንድነት ጠቃሚ መሆኑን ለማሳየት የሼክስፒርን “ጁሊዬስ ቄሳር” ወደዚህ የአፍሪቃ ቋንቋ ተርጉመው አሳትመዋል። ኒዬሬሬ፣ ያልተሳካላቸው ትልቅ ህልም የምሥራቅ አፍሪቃን አገሮች በኅብረት መንግሥት ማዋሃድ ቢሆንም ታንጋኒካን እና የዛንዚባርን ደሴት በማዋሃድ አዲሷን ታንዛኒያን በ፲፱፻፶፮ ዓ/ም ስኬታማ አድርገዋል።

በኚህ ታላቅ መሪ የሥልጣን ዘመናት ጠቅላላው ሕዝባቸውን ከሞላ ጎደል የማንበበ እና መጻፍ ችሎታ ሰጥተውታል። ፕሬዚደንት ኒዬሬሬ በጊዜውም ሆነ እስካሁን በአፍሪቃ ሽከታ ተሰምቶም ተደርጎም የማይታወቅ በፈቃዳቸው በ፲፱፻፸፯ ዓ/ም ሥልጣናቸውን ሲለቁ አገራቸው በዴሞክራሲ የዳበረች ሰላምና አንድነትን ያቀፈች አገር ነበረች።

መምህር ጁሊዬስ ኒዬሬሬ ባደርባቸው የደም ነቀርሳ (leukaemia) በሽታ በተወለዱ በ፸፰ ዓመታቸው ጥቅምት ፬ ቀን ፲፱፻፺፪ ዓ/ም ሎንዶን ላይ አረፉ። በ፳፻፩ ዓ/ም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጠቅላላ ስብሰባ “ዓለም አቀፍ የፍትሐዊ ሕብረተ ሰብ ጀግና” ብሎ ሰይሟቸዋል።


ቡሩንዲ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ንጉሥ ምዋምቡትሳ ፬ኛ

ቡሩንዲ የቀድሞ ቅኝ ገዥ የነበረችው አለማኛአንደኛው የዓለም ጦርነት ስትሸነፍ በዚያን ጊዜ የጀርመን ምሥራቅ አፍሪቃ (አሁን ቡሩንዲ እና ርዋንዳ) የሚባለውን ግዛት ጥቅምት ፲ ቀን ፲፱፻፲፯ ዓ/ም ለቤልጅግ መንግሥት አስረከበች።

ቤልጅግ ይችን ግዛት በነጻነት ሰኔ ፳፬ ቀን ፲፱፻፶፬ ዓ/ም ስታስረክብ በመሪነት የተረከቡት ንጉሥ ግርማዊ ምዋሚ ምዋምቡትሳ ፬ኛ ነበሩ። ንጉሡ ለአራት ዓመታት አገራቸውን ካስተዳደሩ በኋላ መጋቢት ፲፭ ቀን ፲፱፻፶፰ ዓ/ም ልጃቸውን እንደራሴ አድርገው ሾመው ኑሯቸውን ስዊስ አገር አደረጉ። ከሦሥት ወራት በኋላ ግን ሐምሌ ፩ ቀን በጄኔራል ሚኮምቤሮ መሪነት ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ተካሂዶ ንጉሥ ምዋሚ ምዋምቡትሳ ፬ኛ ተገለበጡ። ንጉሡ እዚያው መኖሪያቸው አገር ዠኔቭ ከተማ ላይ ሚያዝያ ፳፫ ቀን ፲፱፻፷፱ ዓ/ም አረፉ።

ኡጋንዳ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሚልተን ኦቦቴ

ታኅሣሥ ፲፱ ቀን ፲፱፻፲፰ ዓ/ም የተወለዱት የኡጋንዳ የመጀመሪያ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የመጀመሪያ ፕሬዚደንት አፖሎ ሚልተን ኦቦቴ ለዚህ ሥልጣን የበቁት ከነጻነት በፊት በብሪታንያ የቅኝ አስተዳደር በተካሄደ ምርጫ ከቡጋንዳ የዘውድ ቡድን ጋር የሽከታ ኅብረት በመፍጠር ነበር። ይሄ የሽከታ ኅብረት በኡጋንዳ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ብዙኃን ነትን ሲያገኝ ኦቦቴ ሚያዝያ ፲፯ ቀን ፲፱፻፶፬ ዓ/ም የመጀመሪያው ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኑ።ወዲያው አገሪቷ መስከረም ፳፱ ቀን ፲፱፻፶፭ ዓ/ም ነጻነቷን ተቀዳጀች።

፲፱፻፶፰ ዓ/ም በጠቅላይ ሚንስትር ኦቦቴ እና በቡጋንዳው ንጉሥ ሙቲሳ መሃል የተከሰተውን የሥልጣን ፉክክር ምክንያት በማድረግ ኦቦቴ ሕገ መንግሥቱን ለውጠው በዓመቱ እራሳቸውን ፕሬዚደንት አደረጉ። ሆኖም ጥር ፲፯ ቀን ፲፱፻፷፫ ዓ/ም ፕሬዚደንት ኦቦቴ ሲንጋፖር ላይ ይካሄድ በነበረው የ”ኮመን ዌልዝ” ርዕሰ መንግሥታት ስብሰባ ላይ ሲሳተፉ በጄኔራል ኢዲ አሚን የተመራ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ከሥልጣን አስወገዳቸው። የታንዛንያ ሠራዊት ኢዲ አሚንን ሚያዝያ ፭ ቀን ፲፱፻፸፩ ዓ/ም ከሥልጣን ካወረደ በኋላ ኦቦቴ አገራቸው ተመልሰው ታኅሣሥ ፰ ቀን ፲፱፻፸፫ በሰፊው የትጭበረበረ ምርጫ ለሁለተኛ ጊዜ ፕሬዚደንት ሆኑ። ይሄ ምርጫ እና የኦቦቴ አምባ ገነንነት ያስከተለው የጦርነት ትግል ለሁለተኛው የወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ምክንያት ሆኖ ሐምሌ ፳ ቀን ፲፱፻፸፯ ዓ/ም ለሁለተኛና ለመጨረሻ ጊዜ ሥልጣናቸውን ለቀው ተሰደዱ። ሚልተን ኦቦቴ ባደረባቸው የኩላሊት በሽታ በደቡብ አፍሪቃ ከተማ ጆሃንስበርግ ላይ በተወለዱ በ ፹ ዓመታቸው መስከረም ፴ ቀን ፲፱፻፺፰ ዓ/ም አረፉ።

ሱዳን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ኢብራሂም አቡድ

ሱዳን ነጻነቷን ከብሪታንያ የተቀዳጀችው ታኅሣሥ ፳፪ቀን ፲፱፻፵፰ ዓ/ም ነው። ማርሻል ፋሪቅ ኢብራሂም አቡድ ጥቅምት ፲፮ ቀን ፲፰፻፺፫ ዓ/ም በቀይ ባሕር አጠገብ ሞሐመድ ጋል በተባለች ሥፍራ ተወለዱ። ካርቱም በሚገኘው የ’ጎርዶን መታሰቢያ ኮሌጅ” እና በብሪታንያ በምሕንድስና የተመረቁት አቡድ፣ በውትድርና ምክትል መቶ ዓለቃ ሆነው በግብጽ ሠራዊት ውስጥ አገልግለዋል።

ወደ ሽከታ ዓለም ከመዛወራቸው በፊት በጦር መሐንዲስነት እና በተለያዩ ወታደራዊ ሥልጣኖች ተመድበው ይሠሩ ነበር። የሱዳንንም ጠቅላላ ሠራዊት አዛዥ በመሆን የመጀመሪያው ሱዳናዊ ነበሩ። በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ኢጣልያን ከአፍሪቃ ለማስወገድ በተካሄዱት ጦርነቶች ላይ በሊቢያ እና በኢትዮጵያ ግዛቶች ውስጥ ተሰልፈው በታላቅ ጀብድ እንደተዋጉ ተመዝግቦላቸዋል። [1]

፲፱፻፶ ዓ/ም የሱዳንን ርዕሰ ብሔር ሥልጣን የጨበጡት አቡድ፣ የደቡብ ሱዳንን የመገንጠል ዓላማ ወኮሎቹን በማሰር፣ በመግደል ወይም በማሰደድ እና በመላ አገሪቱም ላይ የእስላምን የሻሪያ ሕግ በመጠቀም፣ አገሪቱን ወደ አረባዊው ዓለም በመምራትና የውጭ የክርስትና ኃይማኖት ሰባኪዎችን በማባረር እንዲሁም በደቡብ ሱዳን የነበሩትን አብያተ ክርስቲያናት በመዝጋት የሕዝባቸውን ሰብዓዊ መብት የጨቆኑ መሪ ነበሩ። አቡድ በ፲፱፻፷፬ ዓ/ም በፈቃዳቸው ሥልጣናቸውን ለቀው ለብዙ ዓመታት በስደተኝነት ብሪታንያ ኖረዋል። በመጨረሻ ዘመናቸው ወደአገራቸው ተመልሰው ጳጉሜ ፫ ቀን ፲፱፻፸፭ ዓ/ም፣ በተወለዱ በ፹፪ ዓመታቸው ካርቱም ላይ አረፉ።


ኒጄር[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሀማኒ ዲዮሪ

ኒጄር የውጭ ጉዳይ ሚንስትር እና ፕሬዚደንት ሀማኒ ዲዮሪ ሱዱሬ በሚባል የምዕራብ ኒዤር ክፍል በ1908 ዓ/ም ተወለዱ።

በትምህርት ከተመረቁ በኋላ በ[ናያሚ]]፣ ማራዲ እና ፓሪስ ውስጥ በአስተማሪነትም በትምህርት ቤት አስተዳዳሪነትም አገልግለዋል። ከዚህም ሌላ የኒዤር ተራማጅ ቡድን ከመሠረቱት አንዱ ናቸው።

፲፱፻፶ ዓ/ም ቅኝ ገዢዋ ፈረንሳይ ኒዤር እራሷን እንድታስተዳድር ተፈቀደ። ዲዮሪ ፕሬዚደንት ሆነው ነጻነት [ሐምሌ ፳፯]] ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ሲታወጅ የአዲሷ ሪፑብሊክ ፕሬዚደንት ሆኑ። ሀማኒ ዲዮሪ እና መንግሥታቸው በአኅጉሩ በአስታራቂነት ቢመሰገኑም እንኳ በአገር ውስጥ ግን በሙሰኝነት ይወነጀላሉ። በመጨረሻው በሌፍተናንት ኮሎኔል ሴይኒ ኩንቼ የተመራ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ሚያዝያ ፯ ቀን ፲፱፻፷፮ ዓ/ም ዲዮሪን ከሥልጣን አውርዶ ለስደስት ዓመታት በእስር ተቆጣጠራቸው። ሲፈቱም በቁም እስር እስከ ፲፱፻፸፱ ዓ/ም ቆይተው ኑሯቸውን በስደት ሞሮኮ ላይ መሥርተው ሲኖሩ ሚያዝያ ፲፭ ቀን ፲፱፻፹፩ ዓ/ም በተወለዱ በ ፸፪ ዓመታቸው እዚያው ሞሮኮ ውስጥ አረፉ።


ኮንጎ ሊዮፖልድቪል[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ዮሴፍ ካዛቩቡ

ኮንጎ ደሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ መጀመሪያ ፕሬዚደንት ዮሰፍ ካዛቩቡ ነበሩ። በወጣትነት ዘመናቸው በአስተማሪነት እና በሒሳብ ተቆጣጣሪነት ሠርተዋል። በ፲፱፻፴፰ ዓ/ም የሙግት ማኅበር አባል ሲሆኑ የሽከታ ሕይወታቸው ተጀምሮ ቀስ በቀስ ዝናቸው እየታወቀ እስከ ነጻነት ዘመን ቆዩ። በሽከታ ዓለም ካዛቩቡን ስኬታማ ያደረጓቸው በተፈጥሮ ጠባያቸው አሰላሳይነታቸውና በጥፋት ጊዜ ሌሎችን የማጋፈጥ ችሎታቸው ናቸው። በ ፲፱፻፶፪ ዓ/ም መግቢያ ወራት በቀድሞዋ ኮንጎ ሊዮፖልድቪል (አሁን ኮንጎ ዴሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ) በተከሰተው የሕዝብ ሽብር እና ሁከት መነሻነት፣ የቅኝ ገዥዎቿ የቤልጂግ ባለ ሥልጣናት አገሪቱን በስድስት ወራት እንደሚለቁና ነጻነቷን እንደሚሰጧት ጥር ፲፰ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም አስታወቁ። በዚህ መሠረት አገሪቷ ሰኔ ፳፫ ቀን ፲፱፻፶፪ ዓ/ም ስሟን ወደኮንጎ ዴሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ ለውጣ ነጻ ወጣች።

ወዲያው የሕዝብ ምርጫ ተካሂዶ በጠቅላይ ሚንስትርነት ብሔራዊው ፓትሪስ ሉሙምባን ሲመረጡ በፕሬዚደንትነት ደግሞ የምዕራባውያን ደጋፊ የነበሩት ዮሴፍ ካዛቩቡ ተመረጡ። ይሄ በሆነ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ የሕዝብ ሽብር ሲነሳ በተፈጥሮ ሀብት ባለጸጋ የሆነችው የካታንጋ ግዛት በሞይስ ቾምቤ መሪነት ከሪፑብሊኩ ተገነጠለች። የአገሪቱን ጸጥታ ለማስከበርና በሁለቱ ወገኖች (ሉሙምባ እና ካዛቩቡ) የተከሰተውን ጦርነት ለማብረድ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሀያ ሺ ወታደሮች ላከ። በታኅሣሥ ወር አሜሪካ ካዛቩቡን በመደገፍ የላኩት መሣሪያና የ “ሲ አይ ኤ” (CIA) ሰላዮች ከካዛቩቡ ጋር በመረዳዳት ሉሙምባን ገድለው የካዛቩቡን ሥልጣን አጠናከሩ።

ካዛቩቡ ኅዳር ፲፮ ቀን ፲፱፻፶፰ ዓ/ም፣ እስከዚያ ድረስ ታማኝ በነበረው መኮንን፣ ኮሎነል ሞቡቱ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ከሥልጣን ተወገዱ። በፕሬዚደንትነት ዘመናቸው ለአገራቸውና ሕዝባቸው እድገትና ለውጥ እምብዛም አመጡ የሚባልላቸው ነገር ባይኖርም በዚያ በነጻነት ማግስት በተከሰተው ጭፍጨፋ እና ሁከት ጊዜ በአሰላሳይነታቸው እራሳቸውን የአንድነት አርማ አስደርገው ማሳያታቸው ይጠቀሳል። ዮሴፍ ካዛቩቡ መጋቢት ፲፭ ቀን ፲፱፻፷፩ ዓ/ም አረፉ።

ማላዊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ዶክቶር ካሙዙ ባንዳ

ሄስቲንግስ ካሙዙ ባንዳ ግንቦት ፯ ቀን ፲፰፻፺ ዓ/ም ተወለዱ። ባንዳ አገራቸውን ማላዊን ለሰላሳ ዓመታት ያስተዳደሩ ሲሆን በትምህርታቸው ጤና ጥበቃ አጥንተው በእንግሊዝ አገር ውስጥ በሕክምና ዶክቶርነት በሊቨርፑል፣ ኒውካስትል እና ሃርልስደን ሲያገለግሉ በታካሚዎቻቸው ዘንድ በጣም ተወዳጅ እንደነበሩ ይዘገባል።

ባንዳ ለ፵፫ ዓመታት በስደት ከኖሩ በኋላ ያኔ በቅኝ ግዛትነት ሥር ወደነበረችው አገራቸው ኒያሳላንድ (አሁን ማላዊ) ሲመለሱ የአገራቸውን ቋንቋ ረስተው፣ ሁኔታቸው ሁሉ ከአውሮፓውያን የበለጡ አውሮፓዊ ነበሩ። ይሄም ሁኔታ ለሽከታ ዓላማቸው እንቅፋት ሳይሆንባቸው አልቀረም። አማካሪም ሲያስፈልጋቸው የበለጠውን ዕምነት የጫኑባቸው የለመዷቸው የብሪታንያ ዜጎችን ነበር። ሆኖም በምሁርነታቸው እና የእንግሊዞች ተደጋፊ በመሆናቸው መጀመሪያ የኒያሳላንድ ጠቅላይ ሚንስትር ሆነው ተሾሙ።

ኒያሳላንድ በአዲስ ስሟ ማላዊ ተብላ ሰኔ ፳፱ ቀን ፲፱፻፶፮ ዓ/ም ነጻነቷን ከተቀዳጀች በኋላ በተካሄደው የሕዝብ ምርጫ በትልቅ ድምጽ ብዛት ለፕሬዚደንትነት ሲመረጡ የአምባ ገነንነት ባህሪያቸው ይፋ እየሆነ መጣ። በሁሉም የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች “እንግዋዚ” (Ngwazi) ወይም “ድል አድራጊ” እየተባሉ እንዲጠሩ አዘዙ። ከጥቂት ዓመታትም በኋላ “የዘላለም ፕሬዚደንት” ነኝ አሉ።

ለ፴ ዓመታት በፈላጭ ቆራጭነት ማላዊን ከገዙ በኋላ በምዕራባውያን ለጋሽ አገሮች ተጽዕኖ ማላዊ የአንድ ፓርቲ አገር ወይስ የብዙኀን ፓርቲዎች ትሁን የሚል “ውሳኔ ሕዝብ” አካሂደው በተገኘው ውጤት መሠረት በግንቦት ወር ፲፱፻፹፮ ዓ/ም የፕሬዚደንት ምርጫ ተደርጎ ባንዳ በመሸነፋቸው ሥልጣን ለቀቁ። ካሙዙ ሄስቲንግስ ባንዳ በተወለዱ በ፻ ዓመታቸው በደቡብ አፍሪቃ ከተማ ጆሃንስበርግ ላይ ኅዳር ፲፮ ቀን ፲፱፻፺ ዓ/ም አረፉ።

የ አ. አ. ድ. ዓላማዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት (አ. አ. ድ.) ሲመሠረት ሁለት ዐቢይ ዓላማዎችን ተመርኩዞ ነበር። እነኚህም፦

  • ለአኅጉሩ የሽከታና የዱኛኪን እርምጃዎች ወሳኝ ጉዳይ የነበረው ጉዳይ ድርጅቱ የአኅጉሩን አንድነትና ትብብር ለማራመድና የጋራ ልሣን እንዲሆን።


  • ሁለተኛው ዓላማ ደግሞ በዚያን ጊዜ ከቅኝነት ቀንበር ያልወጡ ብዙ የአፍሪቃ አገሮች ስለነበሩ የእነሱን ነጻነት ዐቢይ ዓላማ አድርጎ መታገል ሲሆን፤ ማኅበረተኞቹ እንደቀድሞው በውጭ ኃያላን ቁጥጥር ሥር እንዳይሆኑ በዓለም ዓቀፍ የሽከታ ጉዳዮች አባላቱ ገለልተኞች እንዲሆኑ ነው።

ከነኚህ ዐቢይ ዓላማዎች ሌላ፣ ማኅበሩ

  • ሁሉም አፍሪቃውያን ሰብዓዊ መብታቸው የተከበር እንዲሆን
  • የሁሉም አፍሪቃውያን የኑሮ ደረጃ የተሻሻለ እንዲሆን
  • የእርስ በእርስ ግጭቶችንና አለመግባባት በኃይል ሳይሆን በሰላማዊና ሚዛናዊ ሽምግልና መፍታት

የተስማማባቸውና የያዛቸው ዓላማዎች ነበሩ።

ሆኖም በርስ በርስ ውስጣዊ ጉዳዮች ላይ ጣልቃ ገብነትነት የማይፈልግ ማኅበርም በመሆኑ እና በሽምግልና የማይፈቱ ቅራኔዎች በተፈጠሩም ጊዜ ሰላምን የሚያስክብርበት መሣሪያ የሌለው ጥርስ የለሽ መንጋጋ ብቻ የነበር ድርጅት በመሆኑ የአኅጉሩ ሕዝቦች የጓጉበትን የሰብዓዊ መብት መከበርም ሆነ እንደናይጄሪያ እና አንጎላ ላይ የተካሄዱትንም ብሔራዊ እልቂቶች ለመግታት ያልቻለ ድርጅት ነበር። ስለዚህም በአብዛኛ አፍሪቃውያኖች እና በሰፊውም ዓለም አስተያየት ይሄ ድርጅት ውጤተ ቢስ የወሬ ማኅበር በመባል በይፋ ይተች ነበር።

የድርጅቱ ዋና ጸሐፊዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት በ፲፱፻፶፭ ዓ/ም ተመሥርቶ የአፍሪቃ ሕብረት ሐምሌ ፪ ቀን ፲፱፻፺፬ ዓ/ም እስከተካው ድረስ በየጊዜው ከአባል አገራት የተመረጡ ዘጠኝ ቋሚ ዋና ጸሐፊዎች አገልግለውታል። በድርጅቱ መመሪያ ውል (OAU Charter) መሠረት ዋና ጸሐፊው ለአራት ዓመታት እንዲያገለግል ይመረጣል።

የመጀመሪያው ዋና ጸሐፊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አቶ ክፍሌ ወዳጆ

ድርጅቱ አዲስ አበባ ላይ በተመሠረተ ጊዜ ለስብሰባው ጸሐፊ ሆነው ያገለገሉት በጊዜው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትኢትዮጵያ ልዑካን መሪ የነበሩት ዶክቶር ተስፋዬ ገብረ እዝጊ ነበሩ። በዚያው ስብሰባ ላይ ቋሚ ዋና ጸሐፊ እስኪገኝ ድረስ ተመርጠው ከ ግንቦት ፲፯ ቀን ፲፱፻፶፭ ዓ/ም እስከ ሐምሌ ፲፬ ቀን ፲፱፻፶፮ ዓ/ም ድረስ ያገለገሉት ኢትዮጵያዊው አቶ ክፍሌ ወዳጆ ነበሩ።

ሁለተኛው ዋና ጸሐፊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ዲያሎ ቴሊ

ከድርጅቱ ምሥረታ በኋላ ዋና ጽሕፈት ቤቱ የሚቋቋምበትን ከተማ ለመምረጥ ያስከተለውን እሽቅድምድም እና ፉክክር ለማክሸፍና አዲስ አበባን ለማስመረጥ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር የነበሩት አቶ ከተማ ይፍሩጊኒው መሪ ሴኩ ቱሬ ጋር ባደረጉት ውል መሠረት፤ ጊኒአዲስ አበባን መመረጥ ልትደግፍ፣ ኢትዮጵያ ደግሞ ለድርጅቱ ዋና ጸሐፊነት የጊኒውን ተወላጅ ቡባካር ዲያሎ ቴሊን ለማሳጨት እና ለማስመረጥ እንደተስማሙ የአቶ ከተማ ልጅ መኮንን ከተማ The Creation of the OAU በሚል ርዕስ ላይ አስፍረውታል።[2]

ቴሊ ከ ሐምሌ ፲፬ ቀን ፲፱፻፶፮ ዓ/ም ጀምሮ እስከ ሰኔ ፰ ቀን ፲፱፻፷፬ ዓ/ም ድረስ ሁለት ጊዜ ተመርጠው በድርጅቱ ዋና ጸሀፊነት አገልግለዋል። ዲያሎ ቴሊ በሴኩ ቱሬ ትዕዛዝ ታስረው የካቲት ፳፪ ቀን ፲፱፻፷፱ ዓ/ም በረሀብ ሞተዋል።


ሦሥተኛው ዋና ጸሐፊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

እንዞ ኤካንጋኪ

ሰኔ ፰ ቀን ፲፱፻፷፬ ዓ/ም ሥራቸውን የጀመሩት ሦሥተኛው ጸሐፊ የካሜሩን ተወላጁ እንዞ ኤካንጋኪ ነበሩ። በአለማኛ የተማሩት ኤካንጋኪ ከአገራቸው ነጻነት በኋላ በውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትርነትና የሥራ ሚኒስትር ሆነው ካለገሉ በኋላ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ዋና ጸሐፊ ሆነው ተመረጡ።

የተመረጡበትን የሥልጣን ጊዜ ሳይጨርሱ በሁለት ዓመቱ ድርጅቱ በአኅጉሩ ውስጥ የተፈጥሮ ነዳጅ ምርምር እንዲያካሂድ ከመረጠው የ”ሎንሮ” (Lonrho Group) ድርጅት ሙስና ተቀብለዋል ተብለው ሲታሙ ሰኔ ፱ ቀን ፲፱፻፷፮ ዓ/ም ሥልጣናቸውን በፈቃዳቸው ለቀቁ። [3]


አራተኛው ዋና ጸሐፊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ዊሊያም እቴኪ

የካሜሩኑ ዜጋ እንዞ ኤካንጋኪ ሥልጣናቸውን ሲለቁ የካሜሩን ፕሬዚደንት አህማዱ አሂጆ የአገራቸውን ሰው ዊሊያም ኦሬሊዬን እቴኪ እምቡሙዋን በተተኪነት አጭተው አቀረቡ። በሶማሊያ ዋና ከተማ ሞቃዲሹ ላይ በተካሄደው የመሪዎች ስብሰባ ላይ የቀረቡት የሶማሌ እና የዛምቢያ እጩዎች የሚያስፈልገውን ከሦሥት ሁለት እጅ የድምጽ ድጋፍ ባለማግኘታቸው ስብሰባው በሦሥተኛ አማራጭነት እቴኪን በሙሉ ድምጽ መረጠ።

ዊሊያም እቴኪ እስከ ሐምሌ ፲፬ ቀን ፲፱፻፸ ዓ/ም አገልግለዋል።


አምስተኛው ዋና ጸሐፊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ኤደም ኮጆ

ሐምሌ ፲፬ ቀን ፲፱፻፸ ዓ/ም እስከ ሰኔ ፭ ቀን ፲፱፻፸፭ ዓ/ም ድረስ ያገለገሉት አምስተኛው ዋና ጸሐፊ በሱዳን ዋና ከተማ ካርቱም ላይ በተካሄደው የመሪዎች ስብሰባ ላይ የተመረጡት የቶጎው ተወላጅ፣ ኤድዋርድ ኮጆ (ኤደም ኮጆ) ናቸው።

በኮጆ የሥልጣን ዘመን በሞሮኮ አስተዳደር ሥር ያለችው የሰሐራዊ የአረብ ዴሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ ጉዳይ እና እሷንም በተመለከተ የሳቸው አቋም የድርጅቱን አባላት አቃቅሮ ነበር። ኮጆ የካቲት ፳፩ ቀን ፲፱፻፸፬ ዓ/ም በተካሄደ ስብሰባ ላይ የዚችን ግዛት ልዑካን እንደ አባል መቀመጫ እንዲይዙ ማድረጋቸውን በመቃወም ሞሮኮ እና እሷን የሚደግፉ አገራት የድርጅቱ ስብሰባዎች ላይ ላለመሳተፍ ወስነው ነበር። በዚህ ጉዳይ የተነሳ የሴኔጋል ፕሬዚደንት አብዱ ዲዩፍ ኮጆን “ነገር አማሳይ/በጥባጭ” ብለዋቸዋል።


ስድስተኛው ዋና ጸሐፊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ፒተር ኦኑ

ሰኔ ፭ ቀን ፲፱፻፸፭ ዓ/ም የዋና ጸሐፊነቱን ሥልጣን በስድስተኛነት ተራ የተረከቡት ናይጄሪያዊው ዶክቶር ፒተር ኦኑ ናቸው። ዶክቶር ኦኑ ለሁለት ዓመታት ብቻ አገልግለው ሐምሌ ፲፫ ቀን ፲፱፻፸፯ ዓ/ም ለቀቁ።


ሰባተኛው ዋና ጸሐፊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ኢዴ ኡማሩ

ከዶክቶር ኦኑ በተከታይነት ሰባተኛ ዋና ጸሐፊ ሆነው ሐምሌ ፲፫ ቀን ፲፱፻፸፯ ዓ/ም የተሾሙት የኒጄር ተወላጁ ኢዴ ኡማሩ ናቸው።

ዳካር እና በፓሪስ ከፍተኛ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁት ኡማሩ፣ በአገራቸው በጋዜጠኝነት፣ አምባሳዶርነት እና የውጭ ጉዳይ ሚንስትርነት የሠሩ ሲሆን በ፲፱፻፷፰ ዓ/ም አገራቸው ላይ ከተካሄደውመፈንቅለ መንግሥት በኋላ ለወታደራዊ ርዕሰ መንግሥቱ ሴይኒ ኩንቼ የቅርብ አማካሪ ሆነውም ሠርተዋል።

ኡማሩ የመጀመሪያውን የጸሐፊነት አራት ዓመታት መስከረም ፱ ቀን ፲፱፻፹፪ ዓ/ም ሲያጠናቅቁ ለሁለተኛ ጊዜ እንዲያገለግሉ ታጭተው ነበር። ዳር ግን በውድድሩ የታንዛንያው ሳሊም አህመድ ሳሊም አሸንፈው ሥልጣኑን ተቀበሉ።

ስምንተኛው ዋና ጸሐፊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሳሊም አህመድ ሳሊም

ስምንተኛው ተረኛ ዋና ጸሐፊ ዛንዚባር ደሠት ላይ የተወለዱት የታንዛንያው ዜጋ ሳሊም አህመድ ሳሊም ሲሆኑ፣ ሥልጣኑን ከ ኤዲ ኡማሩ መስከረም ፱ ቀን ፲፱፻፹፪ ዓ/ም ተቀበሉ።

ጥር ፲፭ ቀን ፲፱፻፴፬ ዓ/ም የተወለዱት ሳሊም አገራቸውን በዲፕሎማትነት ለብዙ ዘመናት ያገለገሉ ሲሆን በውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት፤ በመከላከያ ሚንስትርነት፤ በምክትል እና ጠቅላይ ሚንስትርነትም አገልግለዋል። ሳሊም የጋዜጣ ዋና አዘጋጅና የዛንዚባር ጋዜጠኞች ማኅበር ዋና ጸሐፊም ነበሩ።

ሳሊም አህመድ ሳሊም እስከ መስከረም ፯ ቀን ፲፱፻፺፬ ዓ/ም ድረስ ካገለገሉ በኋላ ሥልጣናቸውን አስረክበዋል።

ዘጠነኛውና የመጨረሻው ዋና ጸሐፊ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አማራ ኤሲ

ሐምሌ ፪ ቀን ፲፱፻፺፫ ዓ/ም በዛምቢያ ዋና ከተማ ሉሳካ ላይ የተካሄደው የድርጅቱ ስብሰባ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅትን በአንድ ዓመት ውስጥ በአፍሪቃ ኅብረት ለመተካት የተስማማበትን ዓላማ ግብ የሚያደርስ ዋና ጸሐፊ ሲመርጥ ዘጠነኛውና የመጨረሻው ዋና ጸሐፊ ሆነው የተመረጡት የኮት ዲቯር ተወላጁ አማራ ኤሲ ናቸው።

አማራ ኤሲ ሥልጣኑን መስከረም ፯ ቀን ፲፱፻፺፬ ዓ/ም ተረክበው፣ የአፍሪቃ ኅብረት እስከተመሠረተበት ሐምሌ ፪ ቀን ፲፱፻፺፬ ዓ/ም ድረስ ካገለገሉ በኋላ ለአዲሱ የአፍሪቃ ኅብረት ኮሚሲዮንም ጊዜያዊ ሊቀ መንበር ሆነው ተሹመው ነበር።

ማነጻጸሪያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ BY-GONE PEOPLE WHO LEFT A HISTORY OF STRIFE፣ UNIVERSITY OF PENNSYLVANIA - AFRICAN STUDIES CENTER፣ Sudan Newsletter Vol. III No. 3
  2. ^ መኮንን ከተማ ፣ The Creation of the OAU ገጽ 6
  3. ^ Walter Wilson Nana፣ Nzo Ekangaki Buried፣ Tuesday, 28 June 2005

ዋቢ ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  • (እንግሊዝኛ) Official Website of the Sierra Leon Peoples Party

http://www.slpp.ws/browse.asp?page=438 Archived ጃንዩዌሪ 4, 2009 at the Wayback Machine

  • (እንግሊዝኛ) The Columbia Encyclopedia, Sixth Edition | 2008 |

http://www.encyclopedia.com/topic/Sir_Milton_Margai.aspx

  • (እንግሊዝኛ) The Nyerere Educational Resource Center

http://www.nyererecenter.org/cms/julius-k-nyerere Archived ጁላይ 21, 2011 at the Wayback Machine

  • (እንግሊዝኛ) Obituaries፡ Julius Nyerere The Guardian, Friday 15 October 1999

http://www.guardian.co.uk/news/1999/oct/15/guardianobituaries

  • (እንግሊዝኛ) Imperial Ethiopian Government, "The African Summit Conference." (April 1963), “Biographies of the Founding Fathers”
  • (እንግሊዝኛ) Richard Dowden፣ Independent Print Limited ፣ Obituary: Dr Hastings Banda፣ Thursday, 27 November 1997
  • (እንግሊዝኛ) Britannica Concise Encyclopedia: Joseph Kasavubu

http://www.answers.com/topic/joseph-kasa-vubu