ደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል

ከውክፔዲያ
ደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል
ክልል
የደቡብ ክልልን በቀይ የሚያሳይ የኢትዮጵያ ካርታ
አገር ኢትዮጵያ
ርዕሰ ከተማ አዋሳ
የቦታ ስፋት
   • አጠቃላይ 105,887.18[1]
የሕዝብ ብዛት
   • አጠቃላይ 17,359,008[1]
ድረ ገጽ http://www.snnprs.gov.et/

የደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች (የድሮ ክልሎች 7,8,9,10,11) በኢትዮጵያ ከሚገኙ አስራአንድ ክልሎች አንዱ ነው። 105,887.18 ካሬ ኪ.ሜ. ቦታ የሚሸፍን ሲሆን[1] በምዕራብ በጋምቤላ፣ በደቡብ ምዕራብ ከደቡብ ሱዳን፣ ሰሜን ምሥራቅና ደቡብ ምሥራቅ በኦሮሚያ፣ በደቡብ ከኬንያ ጋር ይዋሰናል።[2] የክልሉ ዋና ከተማ ሃዋሳ ሲሆን ሌሎች ትልቅ ከተማዎች ወልቂጤ፣ ጉብርየ፣ አርባ ምንጭሆሳዕናቡታጂራክብረመንግሥትያቤሎአላባአገረሠላምአለታዎንዶቦዲቲወንዶዲላይርጋለምጂንካሶዶቦንጋሚዛን ተፈሪ ናቸው።

ክልሉ በ፲፫ ዞኖችና ፰ ልዩ ወረዳዎች በ፳፪ የከተማ አስተዳደሮች የተደራጀ ሲሆን በ፲፱፻፺፱ ዓ.ም. በተደረገው የሕዝብና ቤት ቆጠራ መሠረት 15,042,531 ሕዝብ የሚገኝበት ሲሆን ይህም ከአገሪቱ ጠቅላላ ሕዝብ 20.4% ይሸፍናል።[2] ከዚህ በተጨማሪ በክልሉ ፶፮ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የሚኖሩ ሲሆን የእነዚህም ቋንቋዎች በአፍሮ እስያዊ (ኩሻዊ፣ ኦሞአዊ እና ሴማዊ ንዑስ ክፍሎችን ጨምሮ) እና ናይሎ ሳህራዊ የቋንቋ ቤተሰቦች ይመደባሉ።[2]

መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል በኢትዮጵያ ካርታ ውስጥ ከ34° 88′ እስከ 39°14′ ምሥራቅ ኬንትሮስና ከ4°43′ እስከ 8° 58′ ሰሜን ኬክሮስ መካከል ይገኛል።[2]

ክልሉ 4207 ሜትር ከፍታ ካለው የጋሞ ጐፋው ጉጌ ተራራ እስከ 376 ሜትር ከባህር ጠለል በላይ ከፍታ ያለው የደቡብ ኦሞው ጨልባና ቱርካና ኃይቅ አካባቢ ያለው ዝቅተኛ ቦታን ጨምሮ በርካታ የተለያየ መልክዐ ምድራዊ አቀማመጥን ይዟል።[2] በሐሩር፣ በቆላ፣ ወይናደጋና ደጋ የአየር ንብረትን የተከፋፈለ ሲሆን ለእርሻ ከብት እርባታ ምቹ የሆነና በደንም የተሸፈነ ክልል ነው።[2] የአዋሣ የአባያ፣ ጫሞ፣ጨው ባህርና ቱርካና የመሳሰሉ ኃይቆች ኦሞ፣ጐጀብና ብላቴ ወንዞች ባለቤትና ከገናሌ-ዳዋ ከባሮ-አኮቦ፣ ከኦሞ-ግቤ፣ በአጠቃላይ 32% የሚደርሱ ተፋሰሶችንም ይጋራል።[2] የአጆራ፣ሎጊታና ጋቺት ፏፏቴዎች የነጭ ሣር፣ኦሞ ማዜና የማጐና የጨበራ ጩጩራ ብሔራዊ ፓርኮች የሚገኙበት ነው።[2]

አስተዳደራዊ መዋቅር[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል መንግሥት የተዋቀረው በሕግ አውጭው፣ ሕግ አስፈፃሚውና የዳኝነት (ሕግ ተርጓሚ) አካላት ነው። ከሌሎች ክልሎች በተለየ መልኩ የክልሉ ፖርላማ በሁለት ምክር ቤቶች ተዋቅሯል።[3] እነዚህም የክልሉ ምክር ቤትና የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ናቸው። የህግ አስፈፃሚው የመስተዳድር ምክር ቤት በርዕሰ መስተዳድሩ የሚመራ ሲሆን የዳኝነት አካል በጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዝዳንት ይመራል።[3] የሁሉም አካላት አወቃቀር ከብሔረሰቦች ም/ቤት በስተቀር በተዋረድ በክልሉ ውስጥ በሚገኙ ፲፫ ዞኖች፣ ፰ ልዩ ወረዳዎች በጠቅላላ የልዩ ወረዳዎችን ጨምሮ በ፻፴፬ ወረዳዎችና ፴፱፻፲፮ ቀበሌዎች ድረስ በተመሣሣይ ሁኔታ ተዋቅሯል።[3]

ተፈጥሯዊ ቦታዎችና ታሪካዊ ቅርሶች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በጥናት ከተደረሰባቸው ታሪካዊ ቦታዎችና ቅርሶች ግንባር ቀደሙ በክልሉ በሁሉም ቦታ ተሠራጭቶ የሚገኝ ትክል ድንጋይ ሲሆን በአጠቃላይ ከ፲ሺህ በላይ እንደሆነ ይገመታል።[3] ከእነዚህ ውስጥ አንድ ላይ ጥቅጥቅ ብለው በተለያዩ ሥነ ቅርጽና መልክ የተደረደሩትና የተተከሉት በጉራጌ ዞን የሚገኘው ጢያ በ1980 እ.ኤ.አ. በዩኔስኮ በዓለም ቅርስነት ተመዝግቧል።[3] በክልሉ በርካታ ዋሻዎች ሲገኙ ከእነዚህ ውስጥ ሞቼ ቦራጐአክርሳ ዋሻ /ወላይታ/ እና በጌዴኦ የሚገኙ የተቦረቦሩ ፭ የሥነ ድንጋይ ዋሻዎችና ቱቱ ፈላ ትክል ድንጋይ ግንባር ቀደሞቹ ናቸው።[3]

በሌላ በኩል በክልሉ በዓለም አቀፍ ደረጃ የታወቁ የፓሊዮ አንትሮፖሎጂ አርኪዮሎዲጂ ቦታዎች ይገኛሉ።[3] ከእነዚህ ውስጥ የታችኛው ኦሞ ሸለቆ አካባቢ /ሸንጋራ፣ ኡስኖ፣ ኪብሽና ሙርሲ አወቃቀሮ

ች (formation) የታወቀ ነው።[3] የታችኛው ኦሞ ሸለቆ በ1980 እ.ኤ.አ. በዓለም አቀፍ ቅርስነት የዩኔስኮ መዝገብ ዝርዝር ገብቷል። ኮንሶ አካባቢ፤ ፋጀጅና ወይጦ አጭቀሬ በደቡብ ኦሞ ቡርጂ ቁሊቾ በቡርጂ ሌሎቹ የፓሊዮ አንትሮፖሎጂ ቦታዎች ይገኛሉ።[3]

በደቡብ ከሚገኙ ብሔሮች ስም እና ቋንቋዎች ዝርዝር[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ይህ ዝርዝር የተሟላ አይደለም

ሸኮ

በሴሜን ኦሞ የሚገኝ መንገድ

ኢኮኖሚ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የደቡብ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ዋነኛ የኢኮኖሚ መሠረት ግብርና ነው።[4] ዋና ዋና ምርቶችም በቆሎ፣ ስንዴ፣ ጤፍ፣ ጥራጥሬ፣ ድንች፣ እንሰት፣ ፍራፍሬዎችና የቅባት ሰብሎች ናቸው።[4] ዋነኛው ምርት በእህል ራስን ለመቻል የሚያስችሉ ሲሆኑ ጐን ለጐን ገበያ ተኮር የሆኑ ቡና፣ ሻይ ቅጠል፣ ጐማ ተክል ወዘተ እንዲሁም ማንጐ፣ አኘል፣ አቦካዶ፣ አናናስ፣ ፓፓያና ሙዝ በስፋት ይመረታል።[4] የቁም ከብቶች ወተትና የወተት ተዋፅኦም ይገኛል።[4]

ከግብርና በተጨማሪም በንግድና ኢንዱስትሪ ዘርፍ በግንባታ፣ እንጨትና ብረታ ብረት፣ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት የተደራጁ ማኀበራት ይገኛሉ።[4]

ማኅበራዊ ጉዳዮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በ፲፱፻፺፱ ዓ.ም. የክልሉ አጠቃላይ ንፁህ የመጠጥ ውኃ ሽፋን 58% ደርሷል። ከዚህ ውስጥ የገጠሩ ሽፋን 57% ሲሆን በከተማ 66% እንዲሁም የተጠቃሚው ሕዝብ ብዛት 8.7 ሚሊዮን ድረስ እንደደረሰ መረጃዎች ያመለክታሉ።[4]

በክልሉ ያሉ ትምህርት ተቋማት ብዛት (ከ1ኛ እስከ 8ኛ ክፍል) 3,625፣ (ከ9ኛ እስከ 12ኛ ክፍል) 144፣ የመሰናዶ (ከ9-12) 44 ነው። በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ደረጃም 64 የመንግሥትና የግል ቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛዎች፣ ኮሌጆች /16ቱ አዋሣ ከተማ ውስጥ የሚገኙ/ እንዲሁም 5 ዩኒቨርሲቲዎች ይገኛሉ። አጠቃላይ የትምህርት ተሣትፎ በ፲፱፻፺፱ ዓ.ም. መረጃ መሠረት 97.9% የደረሰ ሲሆን የሴቶች ተሣትፎ ወደ 84% አድጓል። የተማሪ መምህር ጥምርታ (1-4 ክፍል) 1፡66፣(5-8) 1፡60፣ (9-10) 1፡82፣ (1-12) 1፡42 ነው።[4]

የ፲፱፻፺፱ ዓ.ም. የጤና ቢሮ መረጃ መሠረት በክልሉ 2,287 ጤና ኬላዎች 161 ጤና ጣቢያዎችና 16 ሆስፒታሎች ይገኛሉ። በአጠቃላይ የጤና ተሣትፎ ሽፋን 75% ደርሷል። መገናኛን በተመለከተ 2 ፖስታ ቤቶች፣ 2 ዋና ቅርንጫፍ ፖስታ ቤቶችና 44 ወኪል ፖስታ ቤቶች ሲገኙ ከ133 ከተሞች በላይ የዲጂታል አውቶማቲክና የሳተላይት ስልኮችን ይጠቀማሉ። በ፲፱፻፺፱ ዓ.ም. መረጃ መሠረት በክልሉ የሚገኙ 130 የሚደርሱ ከተሞች የኤሌክትሪክ መብራት ያገኛሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አብዛኛዎቹ የ24 ሰዓት አገልግሎት የሚሰጡ ሲሆን እጅግ በጣም ጥቂቶቹ በዲዚል ሞተር የሚንቀሣቀሱ የ12 ሰዓት አገልግሎት የሚሰጡ ናቸው፡፡[4]

ሬድዮ፣ ቴሌቭዥንና ጋዜጣን በተመለከተ ሁለት የአካባቢ ሬድዮ ጣቢያዎች /«ፉራ ትምህርት ማሠራጫ ጣቢያ» እና «ወላይታ ሶዶ»/ እና በቅርቡ የተቋቋመው የደቡብ ድምፅ ሬድዮ ጣቢያ (FM 100.9) አዋሣ ይገኙበታል። ጋዜጦችን በሚመለከት «የደቡብ ንጋት» የተባለው የደቡብ ክልላዊ መንግሥት ጋዜጣ፣ በአዋሣ ከተማ ሽግግር አስተዳደር በአማርኛ የሚታተም «ዜና አዋሣ»፣ «ሚረር 3» የተባለ የግል ጋዜጣና በአርባ ምንጭ ከተማ የሚታተም «ትፍላሜ» የተባለውና በክልሉ ባህልና ማስታወቂያ የሚታተም «ማህደረ ደቡብ» የተባሉ ጋዜጦችና መጽሔቶች የሚታተሙ ሲሆን በየመ/ቤቱ የሚወጡ በርካታ ዓመታዊ መጽሔቶችም ይገኙበታል። በክልሉ መንግሥት እየተዘጋጀ በየቀኑ ከሰኞ እስከ እሁድ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ የሚተላለፍ የአንድ ሰዓት የቴሌቢዥን ኘሮግራም ይገኛል።[4]

ማመዛገቢያዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ "፳፻፬ ዓ.ም. ብሔራዊ ስታቲስቲክስ". ማዕከላዊ ስታቲስቲክስ ኤጀንሲ. Archived from the original on 2015-09-23. በሰኔ ፳፪ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም. የተወሰደ.
  2. ^ የደ/ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት አጠቃላይ ገጽታ
  3. ^ "Archive copy". Archived from the original on 2017-10-04. በ2014-06-28 የተወሰደ.
  4. ^ ማኀበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎች


ኢትዮጵያ

ታሪካዊ ቦታዎች - አክሱም | ላሊበላ | ጎንደር | ነጋሽ | ሐረር | ደብረ-ዳሞ | አዲስ አበባ
አስተዳደራዊ ክልሎች - ትግራይ | አፋር | አማራ | ኦሮሚያ | ሶማሌ | ቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል | ደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች | ጋምቤላ | ሐረሪ | አዲስ አበባ | ድሬዳዋ
ቋንቋዎች - አማርኛ | ግዕዝ | ኦሮምኛ | ትግርኛ | ጉራጊኛ | ሶማሊኛ | አፋርኛ | ሲዳምኛ | ሃዲያኛ | ከምባትኛ | ወላይትኛ | ጋሞኛ | ከፋኛ | ሃመርኛ | ስልጢኛ | ሀደሪኛ
መልክዓ-ምድር - አባይ | አዋሽ | ራስ-ዳሽን | ሶፍ-ዑመር | ጣና | ደንከል | ላንጋኖ | አቢያታ | ሻላ
ከተሞች - የኢትዮጵያ ከተሞች