ኢትዮጵያ

ከውክፔዲያ
(ከኢትዮጵያዊ የተዛወረ)
ዘልለው ለመሔድ፦ የማውጫ ቁልፎች, ፍለጋ

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ

የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ የኢትዮጵያ አርማ
ሰንደቅ ዓላማ አርማ
ብሔራዊ መዝሙር ወደፊት ገስግሺ ውድ እናት ኢትዮጵያ
የኢትዮጵያመገኛ
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ቀለም
ዋና ከተማ አዲስ አበባ
ብሔራዊ ቋንቋዎች አማርኛ
መንግሥት
ፕሬዝዳንት

ጠቅላይ ሚኒስትር
ፌዴራላዊ ሪፐብሊክ
መ/አለቃግርማ ወልደ ጊዮርጊስ
ኃይለማርያም ደሳለኝ
የመሬት ስፋት
አጠቃላይ (ካሬ ኪ.ሜ.)
ውሀ (%)
 
1,104,300 (27ኛ)
0.7
የሕዝብ ብዛት
የ፳፻ ዓ.ም. ግምት
የ፲፱፻፺፱ ዓ.ም. ቆጠራ
 
79,221,000 (15ኛ)
73,918,505
ገንዘብ ብር
ሰዓት ክልል UTC +3
የስልክ መግቢያ 251
ከፍተኛ ደረጃ ከባቢ .et

ኢትዮጵያ ወይም በይፋ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢ.ፌ.ዲ.ሪ.)አፍሪካ ቀንድ የምትገኝ የረጅም ዘመን ታሪክ ያላት ሀገር ናት። በአፍሪካ ነፃነታቸውን ጠብቀው ለመኖር ከቻሉ ሁለት አገሮች አንዷ ነች። በህዝብ ብዛት ከአፍሪካ ኢትዮጵያ ሁለተኛ ስትሆን፣ በቆዳ ስፋት ደግሞ አስረኛ ናት። ርዕሰ ከተማአዲስ አበባ ናት።

አብዛኛዎቹ የአፍሪካ ሀገሮች ዕድሜያቸው ከአንድ ምዕተ ዓመት የሚያንስ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ግን ከጥንት ጊዜ ጀምሮ በንጉሠ ነገሥታት እና ንግሥተ ነግሥታት የተመራች ሀገር ናት። የሰለሞናዊው ሥርወ-መንግሥት የአመጣጡን ዘር እስከ አስረኛው ዓመተ ዓለም ድረስ ይቆጥራል። ኢትዮጵያ የሰው ልጅ ከጥንት ጊዜ ጀምሮ የኖረባት ቦታ እንደሆነች ብዙ የሳይንሳዊ መረጃ ተግኝቷል። በበርሊን ጉባኤ በኩል የአውሮፓ ሀያላት ሀገሮች አፍሪካን ሲከፋፍሏት፣ ኢትዮጵያ ነፃነቷን ጠብቃለች። የሊግ ኦፍ ኔሽንስ አባል ከነበሩት ሶስት የአፍሪካ ሀገሮች አንዷ ነበረች። ከአጭር የኢጣልያ ወረራ ጊዜ በኋላም ከየተባበሩት መንግሥታት መሥራቾች አንዷ ናት። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ብዙ የአፍሪካ ሀገራት ነፃነታቸውን ሲያገኙ፣ ሰንደቅ አላማቸውን በኢትዮጵያ ቀለሞች ማለትም በአረንጓዴቢጫቀይ ላይ ነው የመሠረቱት። አዲስ አበባ ደግሞ ለየተለያዩ በአፍሪካ ላይ ላተኮሩ አለም አቀፍ ድርጅቶች መቀመጫ ሆነች።

የዛሬዋ ኢትዮጵያ የትልቅ የግዛት ለውጥ ውጤት ናት። ከሰሜን ግዛቱዋ በጣም የተቀነሰ ሲሆን በደቡብ በኩል ደግሞ ተስፋፍቷል። በ፲፱፻፷፯ ዓ.ም.፣ ግርማዊ ቀዳማዊ ዓፄ ኃይለ ሥላሴ ከሥልጣን ሲወርዱ፣ የእርስ በርስ ጦርነት በሀገሩ ተባባሰ። ከዚህ ጊዜ በኋላ ኢትዮጵያ በተለያዩ የመንግሥት አይነቶች ተዳድራለች። ዛሬ አዲስ አበባ የአፍሪካ ሕብረት እና የተባበሩት መንግሥታት የኢኮኖሚክ ኮሚሽን ለአፍሪካ መቀመጫ ናት። የኢትዮጵያ የመከላከያ ሰራዊት ከአፍሪካ ሀያል ሰራዊቶች አንዱ ነው። ኢትዮጵያ በአፍሪካ የራሷ ፊደል ያላት ብቸኛ ሀገርም ናት።

ኢትዮጵያ ተፈጥሮ ያደላት ሀገር ናት። ከአፍሪካ ትልልቅ ተራራዎች እንዲሁም ከዓለም ከባህር ጠለል በታች በጣም ጥልቅ ከሆኑ ቦታዎች አንዳንዶቹ ይገኙባታል። ሶፍ ዑመር ከአፍሪካ ዋሻዎች ትልቁ ሲሆን፣ ዳሎል ከዓለም በጣም ሙቅ ቦታዎች አንዱ ነው። ወደ ሰማንኒያ የሚቆጠሩ ብሔሮችና ብሔረሰቦች ዛሬ በኢትዮጵያ ይገኛሉ። ከነዚህም ኦሮሞአማራ በብዛት ትልቆቹ ናቸው። ኢትዮጵያ ከአንድ ድንጋይ ተፈልፍለው በተሰሩ ቤተ ክርስትያኖቹዋ እና በኦሎምፒክወርቅ ሜዳልያ አሸናፊ አትሌቶቹዋ ትታወቃለች። የቡና ፍሬ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገኘው በኢትዮጵያ ሲሆን ሀገሪቱዋ በቡናና ማር አምራችነት በአፍሪካ ቅድሚያ ትይዛለች።

ኢትዮጵያ ከዓለም ሶስቱ ትልቅ የአብርሃም ሀይማኖቶች ጋር ታሪካዊ ግንኙነት አላት። ክርስትናን በአራተኛው ምዕተ ዓመት ተቀብላለች። ከሕዝቡ አንድ ሶስተኛው እስላም ነው። የመጀመሪያው የእስላም ሂጅራ ወደ ኢትዮጵያ ነው የተከናወነው። ነጋሽ በአፍሪካ የመጀመሪያው የእስላም መቀመጫ ናት። እስከ ፲፱፻፸ዎቹ ድረስ ብዙ ቤተ እስራኤሎች በኢትዮጵያ ይኖሩ ነበር። የራስ ተፈሪ እንቅስቃሴ ኢትዮጵያን በትልቅ ክብር ነው የሚያያት።

ግርማዊ ቀዳማዊ ዓፄ ኃይለ ሥላሴ ከስልጣን ከወረዱ በኋላ ድህነት በኢትዮጵያ በጣም ተስፋፍቶ ነበር። ሰማኒያ አምስት ከመቶ በላይ የሚሆነው የናይል ወንዝ ውሀ ከሀገሩ የሚመጣ ቢሆንም በ፲፱፻፸ዎቹ በተከሰቱ ድርቆች በብዙ የሚቆጠሩ ሰዎች ሞተዋል። ነገር ግን ቀስ በቀስ ሀገሩዋ እያገገመች ነው። ዛሬ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በአፍሪካ ውስጥ በፍጥነት ከሚያድጉት አንዱ ነው።

ማውጫ

ስያሜ [ለማስተካከል]

ኢትዮጵያ የሚለው ቃል አመጣጥ በተለያዩ የታሪክ ምሁራን የተለያየ ገለፃ ሲኖረው በጣም ተአማኒነት ካገኙት አንዱ አይቲዮፒያ (የግሪክ ቃል) የሚለው ቃል ነው።

ኢትዮጵያ ድሮ ለውጭ አገራት አቢሲኒያ በሚል መጠሪያ ትታወቅ ነበር፤ ይህም ስያሜ የመጣ ከሀበሻ ነበር።

ኢትዮጵያ የሚለው ስም ጥንታዊነት የሚታወቅ ከግሪክ ጸሐፍት ነው። ከሁሉ ቀድሞ የሆነው ግሪክ ባለቅኔ ሆሜር (800 ዓክልበ. ያሕል) ይጠቅሰዋል። በግሪክ አጠቃቀም ከሳህራ በረሃ በስተደቡብ ላለው የአፍሪካ አህጉር ክፍል በሙሉ ሲገልጽ፣ በተለይ ለኩሽ በሚነካ ትርጉሞች ይገኛል። ፕሊኒ እንደሚለው፣ ቃሉ የመጣ አይቲዮፕስ ከተባለ ግለሠብ ነበር። እንዲሁም በኢትዮጵያ መጽሐፍት ልማድ የሀገሩ ስም የኩሽ ልጅ ኢትዮጲስ ሞክሼ ነው። ሆኖም በአቅራቢያው እንደ መንግሥት ስም መጀመርያ የተመዘገበው ዘመን የአክሱም ንጉሥ ኤዛና ዘመነ መንግሥት (4ኛው ክፍለ ዘመን ዓ.ም.) ነበር።

17ኛው ክፍለ ዘመን ዓ.ም. የአውሮፓ ሊቃውንት በጻፉት ሃልዮ ዘንድ፣ «አይቲዮፒያ» የሚለው ስም የመጣ ከግሪኩ ቃላት «አይቶ» (አቃጥላለሁ) እና «ኦፕስ» (ፊት) ነበር። ይህ አስተሳሰብ እስካሁን ድረስ በምዕራብ ሊቃውንት ተቀባይነት አለው።

ታሪክ [ለማስተካከል]

ቅድመ ታሪክ [ለማስተካከል]

ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ የሰው ልጅ ከነበረባችው ቦታዎች አንዷ መሆኗ ትታወቃለች። የሰው ፍልሰት ጥናቶች፣ የቅሪተ አካል ጥናቶችና ሌሎች የሳይንሳዊ ዘዴዎች ይህን ያረጋግጣሉ። ድንቅነሽ የምትባለው በአፋር ክልል ውስጥ የተገኘችው አጽም በአለም በዕድሜ ሁለተኛ ጥንታዊ ናት። ከ3.2 ሚሊዮን ዓመታት በፊት በኢትዮጵያ እንደኖረች ይገመታል። ሌሎችም ታዋቂ አጽሞች በኢትዮጵያ ተገኝተዋል።

የመጀመሪያዎቹ መንግስታት [ለማስተካከል]

በ፰፻ ዓመተ ዓለም አካባቢ ደአማት የሚባል መንግስት በሰሜን ኢትዮጵያና ኤርትራ ተቋቋመ። በሰሜን ኢትዮጵያ የምትገኘው የሀ የደአማት ዋና ከተማ ነበረች። በየመን የሚኖሩት ሳባውያን በደአማት ላይ ተፅዕኖ እንደነበራቸው የሚታመን ሲሆን ይህ ተፅዕኖ ምን ያህል እንደሆነ ግን በእርግጥ አይታወቅም። ወደ ፬፻ ዓመተ ዓለም አካባቢ የደአማት መንግስት ከስልጣን ሲወድቅ በትናንሽ መንግስቶች ተተካ። ከነዚህ ትናንሽ መንግስቶች አንዱ አክሱም ሲሆን አካባቢውን እንደገና በአንድነት ለመግዛት ችሎ ነበር።

የአክሱማውያን ስፈን በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ጠንካራ መንግሥታዊ ማኅበረሰብ ነበር። በፋርስሮማ እና ቻይና ይገኙ ከነበሩ ታላላቅ መንግሥታት በወደረኛነት የሚቆጠር ትልቅ ኅይል ነበር። በ4ኛው ምእተ ዓመት አክሱም ወደ ክርስትና ተለወጠ። በ6ኛው ምእት ዓመት የአክሱማውያን ግዛታዊ ቁጥጥር የዛሬዋን የመን ግዛት ይጨምር ነበር። ግን በ7ኛው እና በ፰ኛው አምኣት የአክሱም ሥልጣኔ በእስልምና መነሣት እና መስፋፋት ተዳክሞ ለውድቀት በቃ። ተከታዩ የዛጔ ሥርወ-መንግሥት ልክ በድንገት እንደተነሳ በድንገት ሲያበቃ፣ ይኵኖ አምላክ ሥልጣን በ ፲፪፻፷፪ ዓ.ም. ጨበጡ፤ እንዲያም ሲል የሰለሞናዊው ሥርወ-መንግሥትን መለሱ።

ከአውሮፓ ጋር የታደሰ ግንኙነት [ለማስተካከል]

የንጉሠ ነገሥት ፋሲለደስ ቤተ መንግሥት

በ፲፭ኛው ምዕተ ዓመት መጀመሪያ ኢትዮጵያ ከአክሱም ጊዜ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ከአውሮፓ ጋር ግንኙነት ጀመረች። ከእንግሊዝ ንጉሥ ሄነሪ አራተኛ ወደ የአቢሲኒያ ንጉሠ ነገሥት የተላከ ደብዳቤ እስከ ዛሬ ድረስ አለ። በ1428 እ.ኤ.አ. አፄ ይስሐቅ ወደ የአራጎን ንጉሥ አልፎንዞ አምስተኛ ሁለት መልክተኞች ልከው ነበር። ግን የመጀመራያው ያልተኳረጠ ግንኙነት በአፄ ልብነ ድንግል ስር ከፖርቱጋል ጋር ከ1508 እ.ኤ.አ. ጀምሮ ነው የተካሄደው።

ኢትዮጵያ በአህመድ ግራኝ ስትጠቃ፣ ፖርቱጋል አራት መቶ ወታደሮችና የጦር መሳሪያ በመላክ ኢትዮጵያን ረድታለች። አፄ ሱስንዮስ በፖርቱጋልና እስፓንያ ተጽዕኖ እና ተጨማሪ እርዳታ ከመፈለጋቸው የተነሳ ወደ የሮማ ካቶሊክ ክርስትና ተለወጡ፤ የኢትዮጵያ ይፋ ሀይማኖትንም አደረገቱት። ይህ ውሳኔ ወደ ግዙፍ ተቃውሞና ጦርነት አመራ። በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች ከሞቱ በኋላ፣ የአፄ ሱስንዮስ ልጅ አፄ ፋሲለደስ በ1632 እ.ኤ.አ. ኢትዮጵያ ወደ አርቶዶክስ ክርስትና መመለሷን አወጁ። አውሮፓውያኖቹንም ከኢትዮጵያ አስወጡ።

ዘመነ መሳፍንት [ለማስተካከል]

አፄ ቴዎድሮስ በአንበሶች ተከበው

ከ1755 እስከ 1855 እ.ኤ.አ. ኢትዮጵያ እንደገና ከአለም ጉዳዮች ተገላ ነበር። ይህ ጊዜ «ዘመነ መሳፍንት» ይባላል ምክኒያቱም የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥቶች በራስ ሚካኬል ስሁል፣ ራስ ወልደ ሥላሴ፣ ራስ ጉግሳ እና በመሳሰሉት ቁጥጥር ስር ነበሩ። ራስ ጉግሳ በ17ኛው ክፍለ ዘመን ጎንደርን በመምራታቸው የቤተ መንግሥቱን ቋንቋ ከአማርኛ ወደ ኦሮምኛ ለውጠው ነበር።

የኢትዮጵያ ግለልኘነት ያበቃው ከእንግሊዝ ጋር ግንኙነት ስትጀምር ነው። ኢትዮጵያ እንደገና የተዋሀደችው እንዲሁም የዘውዱ ስልጣን የተጠናከረው በ1855 እ.ኤ.አ. በአፄ ቴዎድሮስ ምክኒያት ነው። የሰሜን አሮሞዎችና ትግሬዎች አመፅና የግብፆች ተደጋጋሚ ድንበር መጣስ የአፄ ቴዎድሮስ ስልጣን እንዲዳከም አደረጉት። በመጨረሻም ከእንግሊዝ ጋር በነበረው ጦርነት እስረኛ አልሆንም ብለው አፄ ቴዎድሮስ እራሳቸውን አጠፉ። በ1868 እ.ኤ.አ. ኢትዮጵያና ግብፅ ጉራ በሚባለው ቦታ ተዋጉ። በአፄ ዮሐንስ አራተኛ የተመሩት የሰሜን ኢትዮጵያ ሀይሎች ድል ተቀናጁ።

በ1889 እና በ1890ዎቹ እ.ኤ.አ. መጀመሪያ፣ የሸዋ ንጉሥ ሳህለ ሥላሴ ከዚያም ዳግማዊ አፄምኒልክ በራስ ጎበና እርዳታ አማካኝነት ሀገሯን ወደ ደቡብና ምሥራቅ ማስፋፋት ጀመሩ። ከአህመድ ግራኝ ወረራ በኋላ በኢትዮጵያ ቁጥጥር ስር ያልነበሩ፣ ሌሎች ደግሞ በማንኛው ጊዜ በኢትዮጵይ ቁጥጥር ስር ያልነበሩ ቦታዎች በዳግማዊ አፄ ምኒልክ አገዛዝ ጊዜ በኢትዮጵያ ስር ሆኑ። ከዚህ ጊዜ በኋላ የኢትዮጵያ ድንበር ብዙ አልተለወጠም። ከ1888 እስከ 1892 እ.ኤ.አ. ድረስ የነበረው የሰፋ ድርቅ ከኢትዮጵያ ህዝብ በአንድ ሶስተኛ የሚገመተውን ቀጥፎአል።

የአውሮፓ ሽሚያ ለአፍሪካ [ለማስተካከል]

በ1880ዎቹ እ.ኤ.አ. የአውሮፓ መንግሥቶች በበርሊን ጉባኤ ተስማምተው አፍሪካን በቅኝ ገዢነት መከፋፈል ጀመሩ። በኢትዮጵያ እና ጣልያን መካከል የነበሩ የዚያ ዘመን ውዝግቦች ወደ አድዋ ጦርነት1888 ዓ.ም. አመሩ። በጦርነቱ የጣልያን ትልቅ ዘመናዊ ጦር በኢትዮጵያ ጦር ትልቅ ሽንፈት የደረሰበት መሆኑ ዓለምን አስደነቀ።

የግርማዊ ቀዳማዊ ዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን [ለማስተካከል]

ግርማዊ ቀዳማዊ ዓፄ ኃይለ ሥላሴ

በ20ኛው ምእት ሁለተኛው ሩብ ቀዳማዊ፡ኃይለ፡ሥላሴ ኢትዮጵያን ከልጅ ኢያሱ በኋላ መምራት ጀመሩ። ዓፄ ኃይለ ሥላሴ ለአፍሪካ ሕብረት መቋቋም ትልቅ ሚና ተጫውተዋል።

የኢትዮጵያ ነጻነት በጣልያን ወረራ ከ1936 እስከ 1941 እ.ኤ.አ. ድረስ ተቋርጦ ነበር። በዚህ ጥቃት ጊዜ ዓፄ ኃይለ ሥላሴ በ1935 እ.ኤ.አ. በሊግ ኦፍ ኔሽንስ ፊት የሚታወስ ንግግር በአማርኛ አደረጉ። ይህ ንግግር በዓለም ታዋቂ አደረጋቸው እንዲሁም በ1935 እ.ኤ.አ. በታይም መጽሄት «የዓመቱ ሰው» አስባላቸው። ጣልያን ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ውስጥ መሳተፍ ስትጀምር፣ እንግሊዝ ከኢትዮጵያዊ ተዋጊዎች ጋር ኢትዮጵያን ነጻ አወጣች። ግን እስከ 1943 እ.ኤ.አ. ድረስ አንዳንድ ጣልያኖች በደፈጣ ያለ ስኬት ይዋጉ ነበር። በ1942 እ.ኤ.አ. ዓፄ ኃይለ ሥላሴ ባርነት እንደተከለከለ አወጁ።

ዓፄ ኃይለ ሥላሴ ጀግና ሆነው ቢታዩም፣ የ1973 እ.ኤ.አ. ዓለምአቀፍ የነዳጅ ቀውስ፣ የምግብ ዕጥረትና የድንበር ጦርነቶች ተቃውሞ አስነሱ። ከዚያም በ1974 እ.ኤ.አ. በሶቪየት ሕብረት የተደገፈውና በመንግስቱ ኃይለ ማርያም የተመራው ደርግ (ደርግ ማለት ኮሚቴ ማለት ነው) ዓፄ ኀይለ ሥላሴን ከስልጣን አስወረደ።

ኮምዩኒዝም [ለማስተካከል]

የተለያዩ መፈንቅለ መንግሥቶች፣ የሰፋ ድርቀትና ስደተኞች የደርግ ሥርዓት ትልቅ ችግሮች ነበሩ። በ1977 እ.ኤ.አ. ሶማሊያ ኦጋዴንን በመውረሯ የኦጋዴን ጦርነት ተነሳ። በሶቪየት ሕብረት፣ ኩባደቡብ የመንምስራቅ ጀርመንሰሜን ኮሪያ የመሳሪያ እርዳታ እንዲሁም ወደ 15 ሺህ በሚቆጠሩ የኩባ ወታደሮች ድጋፍ አማካኝነት ደርግ ኦጋዴንን እንደገና መቆጣጠር ቻለ።

በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች በቀይ ሽብር፣ የግዴታ ስደት፣ ወይም ረሀብ ሞተዋል። መንግስቱ ቀይ ሽብር ያካሄደው በተቀዋሚዎች በተፈጸመው ነጭ ሽብር መልስ እንደሆነ ጠቅሷል። በ2006 እ.ኤ.አ. መንግስቱ ኅይለ ማርያም በሌሉበት የሞት ቅጣት ተፈርዶባቸዋል።

በ1980ዎቹ መጀመሪያ የተከሰቱ ድርቀቶች ምክኒያት ስምንት ሚሊዮን የሚሆን ሕዝብ ሲራብ፣ አንድ ሚሊዮን ደግሞ ሞተዋል። ተቃውሞ በትግራይና ኤርትራ ክልሎች ተስፋፋ። በ1989 እ.ኤ.አ. ሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ ከሌሎች እንቅስቃሴዎች ጋር በመቀናጀት የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባርን መሠረተ። የሶቪየት ሕብረትም ለኢትዮጵያ የምታደርገውን ድጋፍ መቀነስ ጀመረች። የኢኮኖሚ ችግሮች ተከሰቱ፣ እንዲሁም የኢትዮጵያ የመከላከያ ሰራዊት ተዳከመ።

በሜይ 1991 እ.ኤ.አ. የኢ.ህ.አ.ዴ .ግ. ጦር ወደ አዲስ አበባ አመራ። የመንግስት ሀይሎች ምንም አይነት የውጭ እርዳታ ስላላገኙ፣ የኢ.ህ.አ.ዴ .ግ.ን ጥቃቶች መቋቋም አልቻሉም። መንግስቱ ኅይለ ማርያም ወደ ዚምባብዌ ሄደው እስከ ዛሬ ድረስ በዛችው ሀገር ይኖራሉ። ኢ.ህ.አ.ዴ .ግ. 87 አባላት ያሉት የሽግግር መንግሥት መሠረተ። በጁን 1992 እ.ኤ.አ. የኦሮሞ ነጻነት ግንባር፣ እንዲሁም በማርች 1993 እ.ኤ.አ. የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ኅብረት የሽግግር መንግሥቱን ለቀው ወጡ። በ1994 እ.ኤ.አ. ሁለት የሕግ አውጪ ምክር ቤቶችንና የፍትሕ ስርዓትን የሚደነግግ አዲስ ሕገ መንግሥት ተፃፈ። የመጀመሪያው ምርጫ በሜይ 1995 እ.ኤ.አ. ተካሄደ። አቶ መለስ ዜናዊ ጠቅላይ ሚኒስትር እንዲሁም ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ፕሬዝዳንት ሆነው ተመረጡ።

በቅርብ ጊዜ [ለማስተካከል]

በ1993 እ.ኤ.አ. በተካሄደውና የተባበሩት መንግሥታት በታዘበው ሕዝበ ድምፅ፣ ከ99 ከመቶ በላይ የሚሆነው የኤርትራ ሕዝብና በውጭ ሀገር የነበሩ ኤርትራውያን ከኢትዮጵያ መገንጠልን መርጠዋል። በሜይ 24፣ 1993 እ.ኤ.አ. ኤርትራ ከኢትዮጵያ ነፃነቷን አወጀች።

በሜይ 1998 እ.ኤ.አ. የድንበር ውዝግብ እስከ ጁን 2000 እ.ኤ.አ. ወደቀጠለው የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት አምርቶአል። ይህ ጦርነት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚን ጎድቶአል። በሜይ 15፣ 2005 እ.ኤ.አ. አጠቃላይ ምርጫ ቢካሄድም ተቃዋሚዎች ማጭበርበር እንደነበረ ወንጅለዋል። በአጠቃላይ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ከ200 በላይ የፓርላማ መቀመጫዎችን አሸንፈዋል። ግን አንዳንድ የቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ ፓርቲ አባሎች ከምርጫው በኋላ ከነበረው ረብሻ ጋር በተያያዘ ታስረው ነበር።

መልክዓምድር [ለማስተካከል]

ኢትዮጵያ በሰሜን ምስራቅ አፍሪካ ከ3-14 ዲግሪ ሰሜን እና ከ33-48 ዲግሪ ምሥራቅ የምትገኝ አገር ስትሆን የቆዳ ስፋቱዋም 1,127,127 ካሬ ኪ.ሜ. ነው። በሰሜን ከኤርትራ፣ በምዕራብ ከሱዳንደቡብ ሱዳን፣ በደቡብ ከኬኒያ፣ እንዲሁም በምሥራቅ ከጅቡቲ እና ከሶማሊያ ጋር ትዋሰናለች። የኢትዮጵያ አብዛኛው ግዛት በተራሮች እና አንባዎች የተሞላ ሲሆን፣ ታላቁ የምሥራቅ አፍሪካ ስምጥ ሸለቆ እነዚህኑ ከፍተኛ ቦታዎች ከሰሜን ምሥራቅ ወደ ደቡብ ምዕራብ በመጋደም ለሁለት ይከፍላቸዋል። በስምጥ ሸለቆው ዙሪያም በረሃማ የሆኑ ዝቅተኛ ቦታዎች ይገኛሉ። ይሄን መሰሉ የመልክዓ-ምድር ልዩነት አገሪቷ የተለያዩ የአየር ንብረት፣ የአፈር፣ የዕፅዋት እና የሕዝብ አሰፋፈር ገጽታዎች እንዲኖሯት አስችሏታል። በከፍታና በመልክዓምድራዊ አቀማመጥ የተነሣ በኢትዮጵያ ውስጥ ሦስት ዐይነት የአየር-ንብረት ክልሎች ይገኛሉ። እነሱም፦

  • ደጋ - ከፍታቸው ከባሕር ጠለል 2400 ሜትር የሚጀምር እና የሙቀት መጠናቸው ከ16 ዲግሪ ሴ.ግ የማይበልጥ፣
  • ወይናደጋ - ከፍታቸው ከባሐር ጠለል ከ1500 እስከ 2400 ሜትር፣ ሙቀታቸውም ከ16 ዲግሪ ሴ.ግ እስከ 30 ዲግሪ ሴ.ግ የሚደርስ፣ እና
  • ቆላ - ከባህር ጠለል በታች ጀምሮ እስከ 1500 ሜትር ከፍታ ያላቸው፣ የሙቀት መጠናቸውም ከ30 ዲግሪ ሴ.ግ እስከ 50 ዲግሪ ሴ.ግ የሚደርስ አካባቢዎች ናቸው።

ዋናው የዝናብ ወቅት ከሰኔ አጋማሽ እስከ መስከረም አጋማሽ ሲሆን፣ ከሱ ቀደም ብሎ አልፎ አልፎ የሚጥል የበልግ ዝናብ በየካቲት እና በመጋቢት ይከሰታል። የተቀሩት ወራት በአብዛኛው ደረቅ ናቸው።

አስተዳደራዊ ክልሎች [ለማስተካከል]

ከ1996 እ.ኤ.አ. በፊት ኢትዮጵያ በ13 ክልሎች ተከፍላ ነበር። በአሁኑ ወቅት በኢትዮጽያ ውስጥ 9 አስተዳደራዊ ክልሎች ይገኛሉ። አወቃቀራቸውም በህገ-መንግስቱ በተደነገገው መሰረት «በህዝብ አሰፋፈር፤ ቋንቋ፤ ማንነት እና ፈቃድ ላይ» ተመስርቶ ሲሆን ክልሎቹም ፦

ሕዝብ [ለማስተካከል]

ኢትዮጵያ ከ80 በላይ የሚሆኑ ብሄረሰቦች የሚገኙባት «የብሄረሰቦች ሙዚየም» ልትሰኝ የቻለች ሀገር ነች። ትልልቆቹ ብሄረሰቦች የኦሮሞ፣ የአማራ፣ እና የትግራይ እንደሁም የሶማሌ ሲሆኑ እነዚሁ ብሄረሰቦች ከጠቅላላው የአገሪቱዋ ሕዝብ ቁጥር ክ3/4ኛ በላይ የሚሆነውን ይይዛሉ። በሃይማኖት በኩልም ሁለቱ ትልልቅ ሃይማኖቶች ክርስትና እና እስልምና በስፋት የሚተዋልባት አገር ናት። የእስልምና እምነት ተከታዮች ከ25-30%፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታዮች ከ60-65% እንዲሁም የፕሮቴስታንት እምነት ተከታዮች ወደ 10% የሚሆነውን ይይዛሉ።

ቋንቋዎች [ለማስተካከል]

በኢትዮጵያ ውስጥ ከ80 በላይ ብሄር ብሄረሰቦች የሚኖሩ ሲሆን በቋንቋም በኩል ከ80 በላይ የሚሆኑ ቋንቋዎች የሚነገሩባት ሀገር ናት፡፡ በአሁኑ ወቅት በእብዛኛው ኢትዮጵያውያን የሚነገሩት ቋንቋዎች አማርኛ እና ኦሮምኛ ሲሆኑ፤ አማርኛ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍል ያሉ ነዋሪዎች የመማሪያ፤ የመገበያያ እንዲሁም የስራ ቋንቋ ሆኖ የቆየ በመሆኑ በአሁኑ ወቅት የስራ ቋንቋ ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ የሚነገሩት ቋንቋዎች ወደ አራት ዋና ዋና የቋንቋ ክፍሎች ሊካተቱ ይችላሉ። እነዚሁም

ኩሻዊ ከሚባሉት ቋንቋዎች ዋና ዋናዎቹ አፋን ኦሮሞሶማልኛአፋርኛሲዳምኛሃዲያኛ እና ከምባትኛ ሲሆኑ ከአባይ-ሰሃራዊ የቋንቋ ምድብ የሚካተቱት በርታኛኩናማኛጉሙዝኛሙርሲኛ እና የመሳሰሉት ናቸው። እንደ ወላይትኛጋሞኛከፋኛሃመርኛ የመሳሰሉት የኦሞአዊ ቋንቋ ዘሮች ሲሆኑ አማርኛ፣ ትግርኛጉራጊኛስልጢኛሀደሪኛ እና መሰል ቋንቋዎች ከሴማዊ ቋንቋዎች ይመደባሉ።
የሴሚቲክ ምንጭ ያላቸው እንደ ትግርኛ ና አማርኛ ያሉት ቋንቋዎች የራሱ የሆነ የተለየ የፊደል ስርአት ያላቸው ሲሆን ይህም ኢትዮጵያን ከአፍሪቃ ብቸኛዋ ባለ ጥንት ፊደል ሀገር ያደርጋታል። እነኚህ የሴሚቲክ ምንጭ ያላችው ቋንቋዎች ግዕዝ የተባለ በአሁኑ ወቅት ከቤተክርስትያን ውጭ ለዕለት ተዕለት ግልጋሎት ላይ የማይውል ግንድ ዘር አላቸው።


ባህል እና ሀይማኖት [ለማስተካከል]

ዋና መጣጥፍ፦ የኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር

የህዝብ በዓላት
ቀን የበዓሉ ስም የበዓሉ ስም በእንግሊዝኛ አስተያየት
መስከረም ፩ እንቁጣጣሽ Ethiopian New Year  
መስከረም ፲፯ መስቀል Finding of the True Cross  
ጥቅምት ፳፬ ኢድ አል ፈጥር End of Ramadan ይለዋወጣል፣ ይህ ቀን ለ1998 ዓ.ም. ነው
ታህሳስ ፳፱ ገና Christmas  
ጥር ፪ ኢድ አል አደሃ Eid ul-Adha (Feast of the Sacrifice) ይለዋወጣል፣ ይህ ቀን ለ1998 ዓ.ም.ነው
ጥር ፲፩ ጥምቀት Epiphany  
የካቲት ፳፫ የአድዋ ድል መታሰቢያ በዓል Battle of Adowa Commemoration Day  
ሚያዚያ ፬ መውሊድ (የነብዩ መሃመድ የልደት ቀን) Birthday of The Prophet Muhammad ይለዋወጣል፣ ይህ ቀን ለ1998 ዓ.ም. ነው
ሚያዚያ ፲፫ ስቅለት Good Friday (Crucifixion) ይለዋወጣል፣ ይህ ቀን ለ1998 ዓ.ም. ነው
ሚያዚያ ፲፭ ትንሳዔ (ፋሲካ) Easter ይለዋወጣል፣ ይህ ቀን ለ1998 ዓ.ም. ነው
ሚያዚያ ፳፯ የጀግኖች አርበኞች መታሰቢያ ቀን Patriots' Day  
ግንቦት ፳ ደርግ የወደቀበት ቀን End of the Derg Regime  
Commons-logo.svg
በ"Wikimedia Commons"
(የጋራ ፎቶዎች ምንጭ)
ስለ ኢትዮጵያ የሚገኛኙ
ተጨማሪ ፋይሎች አሉ።


ኢትዮጵያ

ታሪካዊ ቦታዎች - አክሱም | ላሊበላ | ጎንደር | ነጋሽ | ሐረር | ደብረ-ዳሞ | አዲስ አበባ
አስተዳደራዊ ክልሎች - ትግራይ | አፋር | አማራ | ኦሮሚያ | ሶማሌ | ቤንሻንጉል-ጉምዝ | ደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች | ጋምቤላ | ሐረሪ | አዲስ አበባ | ድሬዳዋ
ቋንቋዎች - አማርኛ | ግዕዝ | ኦሮምኛ | ትግርኛ | ጉራጊኛ | ሶማሊኛ | አፋርኛ | ሲዳምኛ | ሃዲያኛ | ከምባትኛ | ወላይትኛ | ጋሞኛ | ከፋኛ | ሃመርኛ | ስልጢኛ | ሀደሪኛ
መልክዓ-ምድር - አባይ | አዋሽ | ራስ-ዳሽን | ሶፍ-ዑመር | ጣና | ደንከል | ላንጋኖ | አቢያታ | ሻላ
ከተሞች - የኢትዮጵያ ከተሞች